ካይሮ፣ ተቃውሞ በፕሬዚዳንት ሙርሲ ላይ፤
ዓርብ፣ ኅዳር 14 2005ማስታወቂያ
የግብፅ ፕሬዚዳንት ሙሐመድ ሙርሲ፣ የሥልጣን አካላትን በመላ በማጠቃለል፣ ሥልጣናቸውን ይበልጥ በማጠናቀራቸው፤ ከህዝቡ ዘንድ ብርቱ ተቃውሞ ማስከተሉ ተነገረ። የተቃውሞ ሠልፈኞች፤ የእስላም ወንድማማች ማኅበር የተሰኘውን የፕሬዚዳንቱን ፓርቲ በዛ ያሉ ጽ/ቤቶች፣ በእስክንድሪያ፤ ፖርት ሰዒድና ሱዌዝ ማቃጠላቸው ተገልጿል። ካይሮ መዳረሻ ላይ አንድ የፓርቲው ጽ/ቤት ሊቃጠል ሲል ተግትቷል። በተለያዩ ጠ/ግዛቶች፤ በተቃዋሚዎችና በእስላማውያን አካራሪዎች መካከል ግጭት መፈጠሩ ታውቋል። በካይሮ ታህሪር አደባባይ የተሰበሰቡ ሰልፈኞች፤ ሙርሲ መፈንቅለ መንግሥት ነው ያደረጉት በማለት ዘልፈዋቸዋል። በፕሬዚዳንቱ ጽ/ቤትና በበሉክሶር ከተማ የሙርሲ ደጋፊዎች አደባባይ በመውጣት ለርእሰ-ብሔሩ ያላቸውን ድጋፍ ገልጸዋል።ሳሜህ አሹር የተባሉት የተቃውሞው ወገን ፖለቲከኛ እንዲህ ብለዋል።---
«ይህ ሙሉ በሙሉ፤ ሥልጣን ላይ እንዲወጡ ባበቋቸው የአብዮቱ ሚዛናዊ ኃይሎች ላይ የተሠነዘረ ጥቃት ነው። የፕሬዚዳንቱ እርምጃ ፣ ይፋ የመንግሥት የሥልጣን አካላትን በመላ በቁጥጥር ሥር የሚያውል ነው። ይህ ደግሞ ፣ ከሆስኒ ሙባረክ የባሱ አምባገነን እንዲሆኑ ያደርጋቸዋል።»
ተክሌ የኋላ
ሂሩት መለሰ