ሞባይል ባንኪንግ
ዓርብ፣ የካቲት 24 2009የሞባይል ባንኪንግ አላማ የተንቀሳቃሽ ስልክን በመጠቀም ከየትኛውም ቦታ ሆኖ የባንክ አገልግሎት ማግኘት ነው። የባንክ ሂሳብን ወጪ ገቢ ማየት ወይም ገንዘብ መላክና መቀበል ያስችላል። በተለይ ከባንክ ራቅ ያለ ቦታ ለሚኖሩ እና ባንክ ሄደው መሰለፍ ለማይፈልጉ ሰዎች እጅግ ጊዜ ቆጣቢ ነው።
ወልደኪዳን ዳለቻ ከአዲስ አበባ፤ ስራቸው የባህር ትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ድርጅት ስለሆነ ብዙውን ጊዜ በጉዞ ላይ ናቸው። ከየትም ቦታ ሆነው ሂሳባቸውን ማየት አስፈላጊ ሆኖ ሲገኝም ሞባይል ባንኪንግ ተጠቅመው ገንዘብ መላክ መቻላቸውን እና እጅግ ጠቃሚ ሆኖ እንዳገኙት ገልጸውልናል። እንዲሁ የአዲስ አበባ ነዋሪ የሆነው ፋሲል ለቴክኖሎጂው ምን ያህል ቅርብ እንደሆነ ገልፆልናል። የ 31 ዓመቱ መሀመድ የደቡብ ወሎ ነዋሪ ነው። በአካባቢው አንድ ባንክ ይገኛል። ካለፈው አንድ አመት ጀምሮ ግን ወደ ባንክ የሚሄደው ጥሬ ገንዘብ ሲፈልግ ብቻ ነው። የቀረውን ከቤቱ ነው የሚጨርሰው። ይሁንና መሀመድ ለሌላ ሰው ገንዘብ ለመላክ አልቻለም።
ገነቱ ካሳሁን፤ ከሁለት ዓመት በፊት ከዮንቨርስቲ በስራ አመራር ትምህርት ተመርቆ በአሁኑ ሰዓት በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የደንበኞች አገልግሎት መኮንን ሆኖ ያገለግላል። የሞባይል እና ቪዛ ካርድ መጠቀም ለሚፈልጉ ደንበኞችም አገልግሎቱን ያስተዋውቃል። እንደ እሱ ገለፃ ብዙዎች ይለፈኝ ይላሉ። ለመሆኑ
ቴክኖሎጂው እንዳለ እያወቁ ሰዎች ለምን መጠቀሙን አልደፈሩም? አንድ የዝግጅታችን ተከታታይ ለምሳሌ ገንዘው ወደ ሌላ ሰው ልኬ አላውቅም ይህም የሆነበት ምክንያት በጠላፊዎች መሀል እንዳይቀር ስጋቱ ስላለኝ ነው። ብለውናል። ይህ ብቻ አይደለም በኔትዎርክ ችግር የተነሳ ፤ ገንዘቡን ወዲያው ማየት አለመቻል፣ ጨርሶም አገልግሎቱን ማግኘት ያልቻሉ በርካታ ተጠቃሚዎች አሉ። ከዚህ አልፎም ከሚያስፈልገው ገንዘብ በላይ ተቆራጭ የሚሆንበት ጊዜ አለ።
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ የባንክ ሂሳብ የሌላቸውን ሰዎች በሞባይል ባንኪንግ ተጠቃሚ ለማድረግ የሚያስችል መመሪያውን ከአራት ዓመት በፊት ነበር ስራ ላይ ያዋለው። ይህንን አገልግሎት መስጠት ከጀመሩ ቀደምት ባንኮች የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ አንዱ ነው። ሲጀምር በአጭር የፁሁፍ መልዕክት ወይም በ«SMS» የነበረ ሲሆን በአሁኑ ጊዜ አገልግሎቱን ለዚህ የተዘጋጀውን አፕሊኬሽን በመጫን በቀላሉ መጠቀም ይቻላል።
ይሁንና ገነቱ እንደሚገልፀው ያለዘመናዊ ስልኮችም ተጠቃሚ መሆን ይቻላል። ዋናው የእንግሊዘኛ ቋንቋ ችሎታ ወሳኝ ነው። እንደ ገነቱ ከሆነ በሞባይል ባንኪንግ እስከ 200 000 ብር ድረስ በቀን ማንቀሳቀስ ይቻላል። የኢ -ባንኪንግ ወይም የኢንተርኔት ባንኪንግ ተጠቃሚ ለሆኑ ደግሞ ከ200 000 ብር በላይ ማንቀሳቀስ ይችላሉ። ቁጥሩ እንደየባንኩ ሊለያይ ይችላል። ሁሉም ግን ለአደጋ እንዳይጋለጡ የይለፍ ቁጥራቸውን በጥንቃቄ መያዝ ይጠበቅባቸዋል። ከጊዜው ጋር መሄድ ፈልገው ባንክ ሄደው የተመዘገቡ እና እስካሁን አገልግሎቱን ማግኘት አልቻልንም ያሉንም ነበሩ።
እስካሁን ተጠቃሚዎች ያላቸው አማራጭ ፤ ሂሳባቸውን መመልከት፣ ገንዘብ መላክ ወይም መቀበል፤ የመሣሰሉት ናቸው። ከዚህ ውጪ በሞባይል ባንኪንግ የመክፈል ልምዱ እና ተቀባይነቱ ምን ይመስላል?
የሞባይል ባንኪንግ አጠቃቀምን በአጭሩ የዳሰሰው የወጣቶች ዓለም ዝግጅታችንን ማድመጥ ከፈለጉ ሙሉ ዘገባውን በድምፅ ያገኙታል።
ልደት አበበ
አዜብ ታደሰ