1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ከወልዲያ ግጭት አዳር በኋላ

ሰኞ፣ ኅዳር 25 2010

በግጭቱም ንብተቶች እንደወደሙ እና የሰው ህይወትም እንደጠፋ የአይን እማኞች ለዶይቸ ቬለ ተናግረዋል። ከግጭቱ አንድ ቀን በኋላ በከተማዋ ከፍተኛ ቁጥጥር እንዳለ የዓይን እማኞች ዛሬ ለዶይቸ ቬለ ተናግረዋል። 

https://p.dw.com/p/2ok4T
Karte Äthiopien Amhara, Tigray, Oromia Englisch

በእግር ኳስ ቡድኖች ደጋፊዎች መካከል ግጭት የተለመደ ቢሆንም እሁድ ዕለት በወልዲያ የተስተዋለው የብሔር ግጭት እንደሚመስል ነው በአካባቢው የሚኖሩ የአይን እማኞች ለዶይቸ ቬለ የገለፁት። ድምፃቸው አየር ላይ እንዳይውል የጠየቁን አንድ የአካባቢው ነዋሪ እንደነገሩን ባለቤቶቹ የትግራይ ህዝብ ናቸው የተባሉ ፎቆች መስታወቶች ተሰባብረዋል። የትግራይ ሰው ነው የተባለም አንድ መኪናም ተቃጥሏል። ትናንትና ምሽት አካባቢ በሰባት መኪኖች ብዙ ተጠርጣሪዎች ታስረው ሲወደሱ በአይኔ ተመልክቻለሁ ያሉን እኚሁ የወልድያ ነዋሪ ሁለት ሰዎች መገደላቸውን እና ዛሬ ቀብር መፈፀሙንም ነግረውናል። ዛሬ ደግሞ እንደ አቢሲንያ እና አርሴማ ያሉ ሆቴሎች እና የወልዲያ ዮንቨርስቲ በፀጥታ ኃይላት ተከበው ተስተውለዋል።  

የደረሰውን ጉዳት ትናንት ማምሻውን እና ዛሬ ጠዋት ዞር ዞር እያሉ የታዘቡት ሌላው የአይን እማኝ እንደነገሩንም የወደሙት ንብረቶች እየተመረጡ ይመስላል። « ብዙ ንብረት ወድሟል። ቡቲኮች ጭምር መናኻሪያ አካባቢ ተቃጥለዋል።መኪኖች ባሉበት ተሰባብረዋል።  ባለሀብቶቹ ብዙዎቹ ትግራዮች ናቸው።»የአይን እማኙ በከተማዋ የኢንተርኔት አገልግሎቱ በግጭቱ ወቅት ተቋርጦ እንደነበር ዛሬ ግን አገልግሎቱ እንደቀጠለ ገልጸውልናል።

Africa Cup Zuschauer Äthiopien vs Sambia
የኢትዮጵያ ብሔራራዊ እግር ኳስ ቡድን ደጋፊዎች ከዛምቢያ ጋር በተደረጋ ግጥሚያ ላይ እኢአ 2013ምስል DW

እስከ ዛሬ ምሳ ሰዓት ድረስ ውጪ እንደነበሩ የነገሩን ሌላው የአይን እማኝ ዛሬ ሁኔታዎች የተረጋጉ ይመስላሉ ይላሉ። « ውጥረቶች አሉ። በየአካባቢው ፖሊስ እና አድማ በታኝ አለ ከዚያ ውጪ ግን የተረጋጋ ሁኔታ ነው ያለው።

የተረጋጋ ሁኔታ ነው ያለው ለማለት የሚከብዳቸው ሌላው የአይን እማኝ « በተለያዩ አካባቢዎች ሰላም አስከባሪዎች በስፍራው ስላሉ እና ህብረተሰቡን ስለሚያስፈራሩ ህብረተሰቡ ሀሳቡን ለመግለፅ ጭቆና ተደርጎበታል። እንጂ ህብረተሰቡ ተረጋግቶ አይደለም ያለው።» እኚህም የአይን እማኝ እንደገለፁልን ዛሬ ረፋዱ ላይ ወልዲያ ውስጥ በህብረተሰቡ እና በሰላም አስከባሪዎች  መካከል ግጭት ተካሂዷል። « በሰላም አስከባሪዎች ላይ ድንጋይ ውርወራ ነበር። ዛሬ አደባባይ የወጡ ሰዎች ነበሩ። ኃላ ላይ ግን የቀዘቀዘበት ሁኔታ ነበር። ህዝቡ ስለ ድርጅቱ ያለውን ጥላቻ እየገለፀ ነበር የሚገኘው።»

የአይን እማኞች እንደገለፁልን ፖሊስ ትናንት ህዝቡን ለመበተን አስለቃሽ ጪስ ረጭቷል።በግጭቱ በትክክል ስለወደመ ንብረትም ይሁን ጠፍቷል የተባለው የሰው ሕይወት እስካሁን ከሚመለከታቸው አካላት ለማረጋገጥ አልቻልንም።

 ልደት አበበ

ነጋሽ መሀመድ