1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

እግር ኳስ እና ወጣት አፍሪቃዉያን በጀርመን

ሐሙስ፣ ጥቅምት 4 2008

አብዛኞቹ ከመካከለኛዉ ምሥራቅ ጦርነት እና ግጭት የሸሹ ቁጥራቸዉ በርከት ያለ ተሰዳጆች ጀርመን እየገቡ ነዉ። የጀርመን መንግሥት እስከፊታችን ታኅሳስ ወር ማለቂያ ድረስ 800,000 ጥገኝነት ፈላጊዎች ወደግዛቱ እንደሚገቡ ይጠብቃል።

https://p.dw.com/p/1Gp0B
Afrikanische Flüchtlinge in Köln Simon Knappe und Asylant
ምስል DW/A.-Bakarr Jalloh

[No title]

ቁጥሩ ሊጨምርም ይችላል። አዲስ ለመጡት ጀርመን ግር የሚል ስፍራ እና ከኅብረተሰቡ ለመዋሐድም አዳጋች ሊሆን ይችላል። ኮሎኝ ከተማ ዉስጥ ጀርመናዉያን ወጣቶች አፍሪቃዉያን የዕድሜ አቻዎቻቸዉ ከእነሱ ጋር እግር ኳስ እንዲጫወቱ በመጋበዝ ለመርዳት እየሞከሩ ነዉ። እግር ኳስ ዓለም አቀፍ ቋንቋ ነዉ ይሉታል አድናቂዎቹ። በጀርመኗ ኮኖኝ ከተማ የተለያዩ የአፍሪቃ ቋንቋዎች ይነገራሉ። «Refugees Welcome»የተሰኘዉ ቡድን እንደሶርያ እና አፍጋኒስታን ካሉ ግጭት ጦርነት ከጠናባቸዉ ሃገራት የተሰደዱ ሰዎችን ለመርዳት በግለሰብ ጀርመናዉያን የተቋቋመ ስብስብ ነዉ። ባለፈዉ ነሐሴ ወር ማለቂያ ገደማ ከተመሠረት አንስቶም በርካታ አፍሪቃዉያን ጥገኝነት ፈላጊዎች ጥቅም እያገኙበት ነዉ። ጀርመናዉያኑ ወጣቶች ኮሎኝ ዉስጥ ባቋቋሙት የእግር ኳስ ቡድን አማካኝነት አፍሪቃዉን ጥገኝነት ፈላጊዎቹ ከሀገሬዉ ዜጎች ጋር እንዲገናኙ እና እንዲግባቡ መንገድ ከፍተዋል። በመደበኛዉ የጀርመን ማኅበረሰብ እንዲህ ዓይነቱ የመገናኛ መድረክ ብዙ ጊዜ የሚገኝ ዓይነት አይደለም። መርሃግብሩን ካመቻቹት አንዱ ፍራንክ ሽትራስበርገር እንዲህ ይላል።

«እግር ኳስ ስለምወድ ይህ ለእኔ በጣም ጠቃሚ ነዉ፤ እግር ኳስ የምጫወተዉ በክለብ አይደለም። በፊትም እጫወት ነበር ግን በግል ዝንባሌ ብቻ ነዉ። እናም እወደዋለሁ፤ ከእነሱም ጋር በየሳምንቱ መጫወትና ግንኙነት መፍጠሩን ወድጄዋለሁ። ብዙ ትማራለህ፣ ብዙ ትስቃለህ፣ አንዳንዴም እርዳታ ልትሰጥ ትችላለህ እናም ያንን አደርጋለሁ።»

Afrikanische Flüchtlinge in Köln Fußball
ምስል DW/A.-Bakarr Jalloh

ሽትራስበርገር ከወጣት አፍሪቃዉያኑ ጋር አብሮ ከመጫወት ያለፈ ብዙም ላያደርግ ይችላል። የጀርመን የከተማ ህይወትን እንዲላመዱም ይዟቸዉ ይወጣል። አንዳንዴም በእግር ኳስ ሜዳዉ ላይ በጨዋታ ጊዜ አለመግባባት ሊያጋጥም እንደሚችል የሚናገረዉ ደግሞ ማርኩስ ሮት ነዉ።

«አምስት ለአምስት ተከፋፍለን መጫወት ፈልገን ነበር ነገር ግን አንድ ትርፍ ሰዉ እኛ ጋር ገባ።»

ለመሆኑ እንዴት መጫወት እንደፈለጋችሁ ተረድቶ ይሆን የሚል ጥያቄ ቀረበለት ለሮት፤ ቀጠለ።

«አልተረዳም። መጀመሪያ ከቢጫ ለባሹ ቡድን ጋር ነበር። መዉጣት እንዳለበት አስቦ ወጣ። ተመልሶ እንደገና ሳይፈቀድለት ገባ። እናም የእኔ ቡድን አባላት ቁጥር ስድስት ሆነ፤ ለዚህ ነዉ እኔ የወጣሁት።»

እንዲህ ባለዉ የተለያየ ባህል ያላቸዉ ወገኖች በሚሳተፉበት መርሃግብር መግባባት እንዲፈጠር ከሚያደርጉት ቋንቋ አንዱ እንቅፋት እንደሚችል የኮሎኝ ከተማ ኗሪ የሆነዉ ሲሞን ክናፐ ያስረዳል።

«ሁሉም ተመሳሳይ ሆነ ቋንቋ እንግሊዝኛ፣ ወይም ፈረንሳይና ወይም ፒጂን ወይም ኪሮ አለያም ጀርመንኛ አይናገርም። እናም አንዳንዳንድ ጊዜ እንዲህ ባለዉ ሰፊ የመጫወቻ ሜዳ ላይ አንዱ ሌላዉን ለመረዳት ያስቸግረዋል።»

በአንድ የስደተኞች መኖሪያ ቤት በጋራ የሚኖሩት ጋናዉያኑ ፕሪንስ እና ጊልበርትም ሆኑ ኤርትሪያዊዉ ሙሉጌታ ከሀገሬዉ ወጣቶች ጋር የሚያገናኛቸዉ የእግር ኳስ ጨዋታ የጀርመንኛ ቋንቋ መማሪያ መድረካቸዉም እንደሆነ ነዉ የሚናገሩት። በጥገኝነት በሚኖሩበት የጋራ ሕይወትም አንዱ ሌላኛዉ የመጣበት ሀገር ሳይመራመር ተዋድደዉ መኖር መቻላቸዉንም ፕሪስ ያስረዳል።

«እርስበስ እንዋደዳለን እንዲሁም እንፋቀራለን። አንድ ቤት ዉስጥ ነዉ የምንኖረዉ። ስለዚህ ማንኛዉ ኤርትራዊ ማንኛዉ ናይጀሪያዉ እንደሆነም አናዉቅም። ከሀገሬዉ ወጣቶች ጋር መዋላችን ቋንቋዉን በቶሎ እንድንማር ይረዳናል። አንድ ሁለት ሲሉ፤ እንደምነህ? ኑሮ እንዴት ይዞሃል ሲሉ? እና የመሳሰሉትን እንሰማለን፤ እናም ከእነሱ አንዳንድ ነገሮችን መማር ይቻላል።»

Afrikanische Flüchtlinge in Köln Prince Porträt
ምስል DW/A.-Bakarr Jalloh

28ዓመቱ ፕሪንስ እነዚህን ጀርመናዉያን ወጣቶች ከማግኘቱ በፊት እንግዳ በሆነባት ሀገር አካባቢዉን ለመላመድ ከብዶኝ ነበር ነዉ የሚለዉ።

«ቀላል አይደለም። ለእንደእኔ ያለ ወጣት ወንድ ልጅ በየዕለቱ ቀኑን ሙሉ ቤት ዉስጥ ተዘግቶ መዋል ቀላል አይደለም። በልቶ መተኛት ብቻ። አሁን ከጓደኞቹ ጋር ወጥቼ ዞር ዞር እያለሁ፤ እCAወታለሁ፤ እስቃለሁ፤ ነፃነቴንም ለማግኘት የማላደርገዉ ነገር አይኖርም። ደስተኛ ለሞሆን እሞክራለሁ፤ ገንዘብ ለማግኘትም እጥራለሁ ሆኖም ግን ሥራ አግኝቶ መሥራቱ ቀላል አልሆነም።»

ጋናዊዉ ፕሪንስ ሜዲትራኒያን ባህርን አቋርጦ ጣሊያን፤ ከዚያም ጀርመን ከገባ አንድ ዓመት ሆነዉ። 15 ስኩየር ሜትር በሆነችዉ ትንሿ መኖሪያ ክፍሉን ከሌሎች ሶስት ጓደኞቿ ጋር ተጋርቶ ነዉ የሚኖረዉ። አብዛኛዉን ጊዜያቸዉን ካርታ በመጫወት ክፍላቸዉ ዉስጥ ቢያሳልፉም በየሳምንቱ ረቡዕ ከጀርመኖቹ እኩዮቻቸዉ ጋር ተገናኝተዉ ኳስ የሚጫወቱባት ልዩ ቀናቸዉ ናት።

አቡ ባከር ጃሎ /ሸዋዬ ለገሠ

አርያም ተክሌ