እግር ኳስና ሰብአዊ መብት፣
ሐሙስ፣ ሰኔ 7 2004ሀገር ጥሩ ማስታወቂያ ነው። ውድድሮቹ፣ ቱሪዝምን ያነቃቃሉ። ታዋቂ ፖለቲከኞችም፣ አስተናጋጂውን ሀገር በመጎብኘት ክብር እንደሚሰጡ የሚታበል አይደለም። «እግር ኳስና ሰብአዊ መብት» በሚል ርእስ በክሪስቲና ሩታ የተሰናዳውን ዘገባ እንሆ--
ታላላቅ የአስፖርት ውድድሮችን በማዘጋጀት የሚገኘውን መታወቅ የተገነዘቡ መንግሥታት፤ በተለይ ፈላጭ ቆራጮቹ ፣ ለአስተናጋጂነት ቀድመው ነው ማመልከቻ የሚያስገቡት። በጀርመን ሀገር የዓለም አቀፉ የሰብአዊ መብት ተሟጋች ድርጅት HRW ቅርንጫፍ ኀላፊ Wenzel Michalski እንደሚሉት ማራኪና ተወዳጅ የእስፖርት ውድድር ማስተናገድ፣ የተባለሻ ገጽን እንደሚያሳምርላቸው ነው ፈላጭ ቆራጭ መሪዎች የሚያምኑት። የአውሮፓ እግር ኳስ ዋንጫ ውድድር ለፕሮፖጋንዳ መጠቀሚያ ሆኗልም ባይ ናቸው፤ ሚኻልስኪ! ። ተቺዎች የሚነቅፉት ሀገር ፣ ዓለም በመላ፤ የአገሬውም ህዝብ-- «እንደሚባለው አይደለም» ብለው ለማሳየትም ነው በእንዲህ ዓይነቱ የእስፖርት ድግስ ለመጠቀም የሚሹት። ህዝባቸው ደስተኛ መሆኑን ፤ዓለም በመላም፤ ለሀገራቸውና ለመንግሥታቸው ክብር ለመስጠት መምጣቱን ያሳዩበታል። እንደሚባለውም፣ «ህዝቡም ተቃውሞን ትቶ በታላቁ የአስፖርት ውድድር ላይ ያተኩራል»።
Wenzel Michalski----
«ፈላጭ ቆራጭ መሪዎች፤ ታላላቅ ማራኪ የእስፖርት ውድድሮች፣ በአገሮቻቸው ሲካሄድ ስማቸውን ለማደስ ያህል ነው የሚጠቀሙበት። ለህዝቡ ጨዋታ ይኸውልህ ይሉታል። በመጠኑም ዳቦ ያቀርቡለትና ለተቃውሞ እንዳይነሳሳ ይደረጋል።»
ፈላጭ ቆራጭ መሪዎች ታላላቅ የእስፖርት ውድድሮችን ማዘጋጀታቸው አዲስ ነገር አይደለም። በኮሎኝ የእስፖርት ከፍተኛ ተቋም፣ የእስፖርት ታሪክ ባለሙያ አንስጋር ሞትዝበርገር፣ እ ጎ አ በ 1988 በሴውል ደቡብ ኮሪያ የተካሄደውን የኦሊምፒክ እስፖርት ውድድር፣ በ 1978 በአርጀንቲና የተዘጋጀውን የዓለም የእግር ኳስ ዋንጫ ውድድር፣ በ
1 968 በሜክሲኮ ከተማ ፣ የተማሪዎች ንቅናቄ በኃይል እርምጃ ከታረቀ በኋላ የተካሄደውን የኦሊምፒክ እስፖርት ውድድር፣ ከብዙዎች ጥቂቶችን መጥቀስ ይቻላል ይላሉ። በ 1936፤ በርሊን ውስጥ የኦሊምፒክ እስፖርት ውድድር በማስተናገድ ናዚዎች፤ ተጨባጩን የጀርመን ሁኔታ ለማዘናጋት እንደተጠቀመበትም ይገልጻሉ።
« ውድድሮቹ፣ ሰልፍ የታየባቸው ትርዒቶች ነበሩ ያኔ የናዚዎቹ አምባገነን መንግሥት፣ የተዘጋጀውን ትልቅ የእስፖርት ውድድር፣ በጀርመን ሠፍኖ የነበረውን አምባገነናዊ ሥርዓት ለማዘናጋት ተጠቅሞበታል።»
ሞትዝበርገር ከዚህ ጋር በማያያዝ፣ በ 2007 ( እ ጎ አ)ዩክሬይን ፣ በፕሬዚዳንት ቪክቶር ዩሽቼንኮና ጠ/ሚናንስትር ዩልያ ቲሞሼንኮ አመራር በነበረችበትና የአውሮፓው ኅብረት አባል መሆን በሚያስችል ፍኖት መራመድ እንደምትችል በብሩኅ ተስፋ ይነገር በነበረበት ወቅት ነበረ፤ የአሁኑን የአውሮፓ የእግር ኳስ ዋንጫ ውድድር እንድታዘጋጅ ዕድሉ የተሰጣት። ትልቅ ውድድር ለማስተናገድ አንድ አገር በቂ እስታዲየሞች ያሉትና፣ መሠረተ- ልማቱም ከሞላ ጎደል የሠመረ ሊሆን ይገባል።
በዓለም አቀፉ የኦሊምፒክ ኮሚቴ፣ (IOC) በዓለም የእግር ኳስ ፌደሬሽን(FIFA) እንዲሁም በአውሮፓ ሃገራት የእግር ኳስ ማኅበር (UEFA)፣ ለአንድ ሀገር የማስተናገድ ዕድል የሚሰጥበት መመሪያ፤ ውስብስብና ግልጽነትም የሚታይበት አይደለም። ማረጋገጫ ሲቀርብ አልታየም እንጂ፣ የድምፅ ድጋፍ በገንዘብ ስለሚገዛበት ሁኔታ በየጊዜው ነው የሚነገረው። IOC እና FIFA ፈላጭ ቆራጭ መንግሥታት የመማዘጋጀት ዕድል እንዲሰጣቸው የሚያደርጉት በአስፖርቱ ዝግጅት ሳቢያ በተዘዋዋሪ መንገድም ቢሆን፣ ለሰብአዊ መብት አጠባበቅ መሻሻል አስተዋጽዖ ያደርጋል እያሉ ነው። Wenzel Michalski ን የመሳሰሉ የ HRW ሰዎች ፣ ምናልባት አወንታዊ ተጽእኖ ሊያሳርፍ ይችላል የሚል እምነት ነው ያላቸው።
«እነዚህን መሰል ታላላቅ ትርዓቶች ሲካሄዱ የመንግሥት ያልሆኑ ድርጅቶች( NGOs)ወይም ጥብቅ ክትትል የማያደርጉ ዓለም አቀፍ ፖለቲከኞች የሰብአዊ መብት ጥሰት ትኩረትእንዲደረግበት አጋጣሚውን ሊጠቀሙበት ይችላሉ፤ በተለይ በአንዳንድ አገሮች፣ በእንዲህ ዓይነቱ አጋጣሚ ካልሆነ እምብዛም ስለሚያደርጉት አይዘገብም፤ ሲዘገብም ፤ ሰዎች እውነት መስሎ አይሰማቸውም።»
እ ጎ አ በ 2008 ቻይና የኦሊምፒክ እስፖርትን ባዘጋጀችበት ዋዜማ የቲቤት ጉዳይ በዓለም ዙሪያ የብዙዎችን ትኩረት እንዳገኘ ሁሉ፤ አሁንም በዩክሬይን የእሥረኛዋ ፖለቲከኛ ዩልያ ቲሞሼንኮ ይዞታ ፤ ልዩ ግምት ሳይሰጠው አልቀረም።
ኦሊምፒክ ፣በ 2008 ፣ በቤይጂንግ፤ በ 1936 በበርሊን፣ የዓለም የእግር ኳስ ዋንጫ ውድድርም ፣ በ 1978 ፣ በቦይነስ አይረስ፤ አርጀንቲና መካሄዱ በፀፀት እንጂ፣ እሰዬው እየተባለ አይደለም የሚታወሰው ።
ተክሌ የኋላ
ነጋሽ መሐመድ