እልባታ ያልተገኘለት የዩክሬይን ውዝግብ
ማክሰኞ፣ ሚያዝያ 21 2006ማስታወቂያ
አንድ የ«ኔቶ» ዲፕሎማት እንደተናገሩት ከሆነ ድርጅቱ እስካሁን ድረስ የሩስያ ጦር ማፈግፈግን በተመለከተ ምንም አይነት መረጃ የለንም ብለዋል። የሩስያው የመከላከያ ሚንስትር ሰርጌይ ሾይጉ በጎረቤት ሀገር ዩክሬይን ድንበር የሰፈረው ጦራቸው ማፈግፈጉን ቀደም ሲል ጠቅሰው ነበር። የዩክሬይን የሽግግር መንግሥት ፕሬዚዳንት አሌክሳንደር ቱርቺኖቭ በበኩላቸው የሩስያን ጦር አስመልክተው ሲናገሩ እንዲህ ብለዋል። «የሩስያ ፌዴሬሽን በሀገራችን ላይ የከፈተችው ያልተደበቀው አደገኛና ስግብግብ ዘመቻ አሁንም እንደቀጠለ ነው። የሩስያ ዓላማ ዩክሬይን እንድትወድም ነው። ሀገራችን ሙሉ ለሙሉ ትርምስ ውስጥ ገብታ ወደ አውሮጳ ኅብረት እንዳንቀላቀል ለማድረግ ነው የሚጥሩት።» ይህ በእንዲህ እንዳለ፤ ሠላም የራቃት የምሥራቅ ዩክሬይን ግዛት ውስጥ መፍቀሬ-ሩስያ ታጣቂዎች ይዘው ያቆዩዋቸው በአውሮጳ የደኅንነትና ትብብር ድርጅት በእንግሊዘኛ ምኅፃሩ «ኦኤስሲኢ» ወታደራዊ ታዛቢዎችን አሁንም እንዳልተፈቱ ተገልጿል። የስሎቭያንስክ ከንቲባ ቭያቼስላቭ ፖኖማሪዮቭ እስረኞቹ ነፃ መውጣት የአውሮጳ ኅብረት ማዕቀብ መነሳት ላይ የተመሰረተ ነው ብለዋል።
ማንተጋፍቶት ስለሺ
ተክሌ የኋላ