ኢትዮ-አርመናዉያንና አርመኖች የተጨፈጨፉበት 100ኛ ዓመት
ሐሙስ፣ ሚያዝያ 22 2007በኢትዮጵያ የብሄራዊ ትያትር የመጀመርያዉ የሙዚቃ አስተማሪ ልጅ ቫርኬዝ ነርሲስ ናልባንድያን ባለፈዉ ሳምንት የቱርክ የዖትማን ስርወ መንግሥት በአርመኖች ላይ ከፍተኛ ጭፍጨፋ የፈፀመበትን 100 ኛ ዓመት መታሰቢያ በማስመልከት የተናገሩትን ነበር ።
የዖትማን ቱርክ ገዥዎች በመጀመርያዉ የዓለም ጦርነት ወቅት 1,5 ሚሊዮን የሚገመቱ አርመኖችን ወይም የአርመን ዝርያ ያላቸዉን ሰዎች መግደል ማስገደላቸዉ ለታሪክ ተመዝግቧል። ይህን ለማሰብ ባለፈዉ ሳምንት በተለያዩ ሃገራት በተዘጋጀዉ ሥነ ስርዓት ላይ የተካፈሉ አርመኖች የያኔዉ ግድያ « የዘር ፍጅት » ነዉ ሲሉ አዉግዘዉታል። የዛሬ 100 ዓመት በአርመኖች ላይ የተፈፀመዉን ይህን የግፍ ጥቃት የሮማ ካቶሊካዊት ቤተክርስትያን ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፋራንሲስ ፤ የጀርመኑ ፕሬዚዳንት ዮአኺም ጋዉክ እንዲሁም አንዳንድ የዓለም ታዋቂ ፖለቲከኞችም ድርጊቱን « የዘር ፍጅት » ሲሉ ፈርጀዉታል። ይህን በማለታቸዉም ከቱርክ ታላቅ ነቀፊታ ነዉ የደረሰባቸዉ።
በአርሜንያና በዓለም ዙርያ የሚኖሩ የአርመን ዜጎች ከ 100 ዓመት በፊት፤ በአንደኛው የዓለም ጦርነት 1,5 ሚሊዮን አርመኖች በዖቶማን ቱርክ መንግሥት ወታደሮች የተገደሉበት የመታሰብያ ሥነ-ስርዓት ሲያስቡ፤ በኢትዮጵያ የሚኖሩ አርመናዉያን ዘንድም በደማቅ ዝግጅት ታስቦ ነዉ የለዉ። በኢትዮጵያ የሚኖሩ አርመናዉያን ማኅበር ሊቀመንበር ቫርኬዝ ነርሲስ ናልባንድያን ስለ መቶኛ ዓመቱ ሰማዕታት መታሰብያ ከመናገሬ በፊት አሸባሪዉ ቡድን IS በኢትዮጵያዉያን ላይ ስለፈፀመዉ አሰቃቂ ጥቃት ኃዘናችንን እንገልፃለን ሲሉ ነበር ቃለ ምልልሱን የጀመሩት።
የአሸባሪዉን የ IS አሰቃቂ ጥቃት ተከትሎ የአርሜንያ ቤተ ክርስትያን ለኢትዮጵያ ቤተ-ክርስትያን የሐዘን መግለጫ ማስተላለፏ ይታወቃል።
ቫርኬዝ ነርሲስ ናልባንድያን በመቀጠል የቱርኩ የዖትማን ስርወ መንግሥት በአርመኖች ላይ ከፍተኛ ጭፍጨፋ የፈፀመበትን 100 ኛ ዓመት ኢትዮጵያ አዲስ አበባ ላይ የነበረዉን የመታሰብያ ሥነ-ስርዓት በከፍተኛ ድምቀት የተካሄደና የመንግሥት ተወካዮች የተካፈሉበት እንደነበር ተናግረዋል።
መኖርያቸዉን በኢትዮጵያ ያደረጉ አርመናዉያን በአዲስ አበባ ከተማ ዉስጥ ብቻ እንደሚገኙና በቁጥር ከመቶ እስከ 120 እንደሚሆኑ የገለፁት በኢትዮጵያ የአርመን ማኅበረሰብ ሊቀመንበር ቫርኬዝ ነርሲስ ናልባንድያን፤ በኢትዮጵያ የአርመናዉያን እንቅስቃሴና ተሳትፎ እንደቀነሰ ገልፀዋል።
በርካታ ኢትዮጵያዉያን አርመኖች ወደ ኢትዮጵያ መምጣት የጀመሩበትን ጊዜ በዉል አያዉቁም ያሉት ቫርኬዝ ነርሲስ ናልባንድያን ኢትዮጵያና አርመን ከሦስተኛዉ ክፍለ ዘመን ጀምሮ የጠበቀ ግንኙነት እንዳላቸዉ በዝርዝር አስረድተዋል።
የአባቴ አጎት ኬቮርክ ናልባንድያን አርባ ልጆች ከሚባሉትና ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ወደ ኢትዮጵያ ካመጡዋቸው ልጆች ጋር የሙዚቃ ጓዱ መሪ በመሆን 1924 ዓ,ም ወደ ኢትዮጵያ መጡ ያሉት ቫርኬዝ ናልባንድያን አባታቸዉ በ1930ዎቹ የአርመን ቤተክርስትያን መዘምራንን እንዳስጀመሩም ገልፀዋል።
የዖትማን ሥርወ መንግሥት በአርመን ላይ ያደረሰዉን ጥቃት 100 ኛ ዓመት በማስመልከት የጀርመኑ ርዕሰ ብሔር ዮአሂም ጋዉክ በርሊን ላይ በተደረገዉ ሥነ-ስርዓት ባደረጉት ንግግር፤
«በአርመኖች ላይ የደረሰዉ እጣ ጭፍጨፋ የዘር ማጽዳት የማሳደድንና የጅምላ ግጅት፤ በ 20ኛዉ ክፍለ ዘመን የደረሰ አስደንጋጭ ታሪካዊ ክስተት ምሳሌ ነዉ።»
ጀርመንን ጨምሮ አንዳንድ አዉሮጳ ሃገራት የሚኖሩ አርመናዉያን በዖትማን ግዛት የአርመን ዜጎች ላይ የደረሰዉ ጥቃት «የዘር ፍጅት» መሆኑ ይገለጽ ይታመን ሲሉ በተለያዩ ከተሞች ትዕይንተ ህዝብ አካሂደዋል። ቱርክ በአርመኖች ላይ የተፈፀመዉን ግድያ «ዘር ማጥፋት» የሚሉ ወገኖችን አጥብቃ ትቃወማለች።የቱርክን ተቃዉሞና ዉግዘት ፍራቻ በርካታ መንግሥታት ግድያዉን ዘር ማጥፋት ብለዉ ለመፈረጅ እያቅማሙ መሆኑም ተዘግቦአል። የኢትዮጵያ መንግሥት የዖትማንን ጭፍጨፋ የዘር ፍጅት ብሎ አልተቀበለም ያሉት በኢትዮጵያ የአርመን ማኅበረሰብ ሊቀመንበር፤ ጉዳዩ ስለመፈፀሙ በኛ በኩል ጥርጥር የለዉም አሁን ግን ነገሩ የፖለቲካና የቃላት ጨዋታ ሆኖ ነዉ።
የቱርኩ የዖትማን ስርወ መንግሥት በአርመኖች ላይ ከፍተኛ ግድያ የፈፀመበትን 100 ኛ ዓመት በማሰብ «Eurovision Song Contest» በመባል የሚታወቀዉ በአዉሮጳ ሃገራት መካከል የሚካሄደዉ የሙዚቃ ዉድድር ላይ አርሜኒያ በተለያዩ ክፍለ ዓለማት የሚኖሩ ስድስት ሙዚቀኞችን በማሰባሰብ በዉድድር መድረኩ ላይ ዝግጅቷን አጠናቃለች። ትዉልደ አርሜንያዊዉ ኢትዮጵያዊ ቫሄ ቲልቢያን አፍሪቃን ኢትዮጵያን ብሎም አርሜንያን ወክሎ መድረኩ ላይ እንደሚሳተፍ መግለፃችን የሚታወስ ነዉ። ሙሉዉን ቅንብር የድምፅ ማድመጫ ማዕቀፉን በመጫን ይከታተሉ።
አዜብ ታደሰ
ሸዋዩ ለገሠ