ኢትዮጵያ: ምርጫ 2007
ሰኞ፣ ግንቦት 17 2007ማስታወቂያ
ከተለያዩ አካባቢዎች በደረሰን ዘገባ መሠረት የድምፅ አሰጣጡ ሂደት ሠላማዊ ነበር።ይሁንና፣ የተቃዋሚ ፓርቲ ባለሥልጣናት እንደሚሉት በአንዳንድ የድምፅ መስጪያ ጣቢያዎች የፓርቲዎቻቸዉ እጩዎች፤ ታዛቢዎች፤ ደጋፊዎችና መራጩ ሕዝብ ራሱ በፀጥታ ሐይላት እየተጉላሉ ነዉ። የሠማያዊ ፓርቲ ምክትል ሊቀመንበር አቶ ሥለሺ ፈይሳ እስከ ቀትር በኋላ የነበረዉን የድምፅ አሰጣጥ ሒደት «በጫና እና በዉጥረት» የተሞላ ብለዉታል። 547 መቀመጫዎች ላሉት ብሔራዊ ምክር ቤት እና ለየመስተዳድሮቹ ምክር ቤቶች 60 ያሕል የፖለቲካ ፓርቲዎችን የወከሉ እና አስራ-አንድ የግል ተወዳዳሪዎች በድምሩ ሥድስት ሺሕ ያሕል ዕጩዎች ይፎካከራሉ።
ከዚሕ ቀደም ኢትዮያ ዉስጥ የተደረጉ ምርጫዎችን ሲታዘቡ የነበሩት የአዉሮጳ ሕብረት እና የካርተር ማዕከልን የመሳሰሉ ተቋማት የዘንድሮዉን ምርጫ አይታዘቡም።ምርጫዉን የሚታዘቡት የሐገር ዉስጥ ማሕበራትና የአፍሪቃ ሕብረት ተወካዮች ናቸዉ።ከአምስት ዓመት በፊት በተደረገዉ ምርጫ የብሔራዊዉን ምርክር ቤት 99,6 ከመቶ መቀመጫዎች የተቆጣጠረዉ ኢሕአዴግ በዘንድሮዉም ምርጫ ብዙዎቹን መቀመጫዎች እንደሚጠቀልል በሰፊዉ እየተነገረ ነዉ። ስለምርጫ 2007 ዓም ወኪሎቻችን ከአዲስ አበባ፣ ከሀዲያ፣ ከዋሽንግተን፣ ከለንደን የተለያዩ ዘገባዎች ልከውልናል።
ነጋሽ መሀመድ
አርያም ተክሌ