1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ኢትዮጵያዊው ወጣት በስነ-ህዋ ጥናት

ዓርብ፣ ግንቦት 21 2001

ብዙ ኢትዮጵያውያን እንዳልተሰማሩበት በሚነገረው የስነ-ህዋ (cosmology) የትምህርት ዘርፍ የማስትሬት ዲግሪውን ሊይዝ ቀናት ብቻ ነው የቀሩት። ወጣቱ ከሁለት ወራት በኋላ ደግሞ የPhd ጥናቱን ያካሂዳል። ከስምንት በላይ ቋንቋዎች ተናጋሪም ነው።

https://p.dw.com/p/I0Co
በዓለማችን በርካታ ቋንቋዎችን ማወቁ ተጠቃሚ ያደርጋል
በዓለማችን በርካታ ቋንቋዎችን ማወቁ ተጠቃሚ ያደርጋል

የዛሬው እንግዳችን የሃያ አምስት ዓመቱ ወጣት አማረ አበበ ይባላል። ለትምህርት ደቡብ አፍሪቃ ኬፕታውን ከተማ ውስጥ ይገኛል። ወጣቱ የመጀመሪያ ዲግሪውን ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በየቁስ አካልና የሀይል ጥናት (Physics) የትምህርት ዘርፍ ነው ያገኘው። ብዙ ኢትዮጵያውያን እንዳልተሰማሩበት በሚነገረው የስነ-ህዋ (cosmology) የትምህርት ዘርፍ የማስትሬት ዲግሪውን ሊይዝ ቀናት ብቻ ነው የቀሩት። ወጣቱ ከሁለት ወራት በኋላ ደግሞ የPhd ጥናቱን ያካሂዳል። ከስምንት በላይ ቋንቋዎች ተናጋሪም ነው።

ወጣት አማረ የተለያዩ ቋንቋዎችን ለማወቅ ፍላጎቱ የተጫረው የስምንተኛ ክፍል ተማሪ ሳለ ድንገት ቤተ-መጸሐፍት ውስጥ ባጋጠመው ነገር ነው። ያኔ በልደታ ካቶሊክ ካቴድራል ትምህርት ቤት ቤተ-መጸሐፍት ውስጥ አይኑ ስር የገባውንና ፈጽሞ በማያውቀው የፈረንሳይኛ ቋንቋ የተፃፈውን አንድ መፀሐፍ ያነሳል። እንዲሁ ማንበብ ይጀምራል። ሁኔታው ያስደስተውና ራሱን በራሱ ማስተማር ይጀምራል። እዛው ቤተ-መፀሐፍት ውስጥ በሌላ ግዜ ደግሞ በስጳንኛ ቋንቋ የተፃፈ ሌላ መፀሐፍ ያገኝና እንደለመደው አንስቶ ያገላብጠዋል። ከዚያም ጣልያንኛ፣ ፈረንሳይኛ፣ ጀርመንኛ እያለ ይቀጥላል።

በእርግጥም በተለያዩ ቋንቋዎች የተፃፉ በርካታ መፀሐፍት ከተለያዩ ሐገራት ለተለያዩ ዩኒቨርሲቲዎች ይላካሉ። ለአብነት ያህል፥ በጀርመንኛ፣ በጣልያንኛ እና በፈረንሳይኛ ቋንቋዎች የተፃፉ በርካታ የጥናትና የምርምር ውጤቶች እንዲሁም የተለያዩ መፀሐፍት ማንም ላይደፍራቸው በሚመስል መልኩ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ቤተ-መፀሐፍት ውስጥ ከጥግ እስከ ጥግ ተደርድረው የሚታዩበትን ሁኔታ ማስተዋል ይቻላል። መፀሐፍቱ የተፃፉባቸውን ቋንቋቸውን የሚያውቅላቸው በርካታ አንባቢ ባለማግኘታችውም ውቅያኖስ አቋርጠው እዛ የመከሰታቸው ነገር የትካዜ ድባብ ውስጥ ሳይከታችው የቀረም አይመስልም።


እንግዲህ አድማጮች፥ ከስምንት በላይ የውጭ ሐገራት ቋንቋዎችን አቀላጥፎ ከሚናገረውና ብዙም ኢትዮጵያውያን ሲሰማሩበት በማይታየው የስነ-ህዋ ትምህርት በደቡብ አፍሪቃ ትምህርቱን ለመከታተል ከተዘጋጀው የሃያ
አምስት ዓመቱ ወጣት አማረ አበበ ጋር ያደረግነው ቆይታ በዚህ ይጠናቀቃል።

ማንተጋፍቶት ስለሺ