1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ኢትዮጵያዊትዋ ሙዚቀኛ በግዙፉ የአዉሮጳ ፊስቲቫል

ሐሙስ፣ ሰኔ 11 2007

በአዉሮጳ ግዙፍ እንደሆን የሚነገርለት በጀርመን ቩልዝቡርግ ከተማ የሚካሄደዉ የአፍሪቃ ፊስቲቫል ከአፍሪቃ ብሎም ከተለያዩ የዓለም ክፍሎች የተሰባሰቡ ሙዚቀኞች ሙዚቃቸዉን አሳይተዉበታል ባህል ልምድን ተቀያይረዉበታል። በጀርመኑ ቩልዝቡርግ ከተማ የአፍሪቃ ፊስቲቫል ላይ የመድረኩ ዋና ተጋባዥ የነበረች ኢትዮጵያዊት ሙዚቀኛ እንግዳ አድርገናል።

https://p.dw.com/p/1FjGt
Africa Festival Würzburg 2013
ምስል picture-alliance/dpa/D. Karmann

ኢትዮጵያዊትዋ ሙዚቀኛ በግዙፉ የአዉሮጳ ፊስቲቫል


ዘንድሮ ለ27 ኛ ጊዜ በጀርመን ቩልዝቡርግ ከተማ በተካሄደዉ ዓመታዊዉ የአፍሪቃ ፊስቲቫል ከ 80 ሺህ በላይ እድምተኞች ተገኝተዋል። እንደ አዘጋጆቹ ወደ 100 ሺ የሚሆን እድምተኛ ዝግጅቱን ይታደማል ተብሎ ነበር የተጠበቀዉ። የዛሬ ሁለት ሳምንት ግድም በተካሄደዉ የአራት ቀናቱ የአፍሪቃ ባህላዊ ድግሥ እለት ቩልስ ከተማ ላይ ከፍተኛ ሙቀት በመከሰቱ የተገኘዉ እንግዳ አነስ ማለቱ ነዉ የተዘገበዉ። ወደ ሰማንያሺ ያህል እድምተኛ። በአዉሮጳ የአፍሪቃ ባህል፤ ሥነ ጥበብና ሙዚቃ የሚታይበት ይህ ግዙፍ መድረክ ዘንድሮ ሕንድ ዉቅያኖስ ላይ ስለምትገኘዉ ስለ ዛንዚባር ደሴት ሙዚቃና ላይ ነበር ትኩረቱን ያደረገዉ። በመድረኩ ከተጋበዙት መካከል ኢትዮጵያዊትዋ ሙዚቀኛ ምንይሹ ክፍሌ ከደቡብ አፍሪቃ ሙዚቀኛ ሊራና ከዛንዚባር ሙዚቀኛ ማቶና እንዲሁም ሙዚቀኛ ሺሻኒ ከናሚቢያ ይገኙበታል።

Die Sängerin Minyeshu aus Äthiopien
ሙዚቀኛ ምንይሹ ክፍሌምስል DW/A. Gensbittel


«ይህ የኔ ምልክት የኔ ማንነትነዉ በእንጊሊዘኛ አልያም በሌላ ቋንቋ ማዜም ቀላል ነዉ። ግን ይህን ሊያደርጉ የሚችሉ በርካታ ሙዚቀኞች አሉ። እኔ እንደማዜመዉ አይነት ዘፈን ግን ዝዚህ ማንም አይዘፍንም»
የምትለዉ በቮልዝቡርጉ ግዙፍ የአፍሪቃዉያን ሙዚቃ መድረክ ላይ ቀርባ ተደናቂነትን ያተረፈችዉ ከያኒ ምንይሹ ክፍሌ ናት። በየዓመቱ በሚዘጋጀዉ በዚህ መድረክ ስትሳተፍ ለሶስተኛ ጊዜም ነዉ።

Die Sängerin Shishani aus Namibia
ምስል DW/S. Mnette


«ሶስቱም ግዜ የተዋጣ ስራ ነበር ስትል አጫዉታናለች። ብዜ አበሻም በድግሱ ላይ ነበር። በዚህም ምክንያት እናትና አባት የመጡ ያህl ነዉ የተደሰትኩት።»
ሙዚቀኛ ምንይሹ በቩልዝቡርጉ የአፍሪቃ ፊስቲቫል ላይ ስትቀርብ የኢትዮጵያን ባህላዊ ዉዝዋዜና የአማርና ሙዚቃን የምታስደምጥ የኢትዮጵያ አንባሳደር ሲሉ የተለያዩ የብዙኃን መገናኛዎች ዘግበዉላታል። ግን አማርኛ ሙዚቃ በፈረንጆቹ ጆሮ ያለ ሃሳብ ይንቆረቆር ይሆን? ሙዚቀኛ ምንይሹ አዎ ባይናት።


« አማርኛ ብቻ ሳይሆን ጉራጌኛ ትግርኛ ኦሮምኛም አዜማለሁ። ፈረንጆቹ ሙዚቃን የሚማሩት ከልጅነታቸዉ ስለሆነ ስለሙዚቃ ጠንቅቀዉ ያዉቃሉ። ሙዚቃ እኮ የዓለም ህዝቦች ቋንቋም ነዉ። በሙዚቃዬ ዉስት አራቱን የኢትዮጵያ ባህላዊ ቅኝቶች አንባሰል፤ አንቺ ሆዩ፤ ባቲና፤ ትዝታ ቅላጼን ስለማካትት ግጥሙን ብቻ ሳይሆን የሚያደምጡት በአጠቃላይ ሙሉዉን ሙዚቃ ቅላቼዉን ሁሉ ነዉ በዝያ ምክንያት ሲደሰቱ እንደዉም ሲጨፍሩ ሁሉ ታያለሽ»
ኔዘርላንድ ነዋሪ የሆነችዉ ኢትዮጵያዊት ሙዚቀኛ ምንይሹ ክፍሌ አዉሮጳ መኖር ከጀመረች 19 ዓመት እንደሆናት ትናገራለች ሙሉ ጊዜዋንም የምታሳልፈዉ በሙዚቃ ስራ ላይ ነዉ።

Die Sängerin Marema aus dem Senegal
ምስል DW/A. Gensbittel


በጀርመን ቩልዝቡርግ ከተማ በሚካሄደዉ ዓመታዊ የአፍሪቃ ፊስቲቫል ላይ በጎርጎረሳዉያኑ 2004 ,2009 እና ዘንድሮ ተካፋይ የነበረችዉ ሙዚቀኛ ምንይሹ ክፍሌ በኔዘርላንድ ነዋሪ ስትሆን የኢትዮጵያ ቅኝትን የያዙት ሙዚቃዎችዋን በፖፕ ብሉዝ እና ጃዝ ሙዚቃ ቅላፄ ጋር በማጣመር የራስዋን አይነት ልዩ የሙዚቃ ዓይነት በማቅረብዋ በአዉሮጳ የሙዚቃ አፍቃሪ ዘንድ ታዋቂነትን ማግኘትዋ ተነግሮላታል።


ከኢትዮጵያ፣ ከማሊ፣ ከሱዳን፣ ከዲሞክራቲክ ኮንጎ፣ ከኔዘርላንድ፣ ከአሜሪካ እና ከሌሎች አውሮጳ ሃገሮች በተውጣጡ ሙዚቀኞች ታጅባ የኢትዮጵያ ሙዚቃ በሌላውም የዓለም ክፍል ተደማጭነትን እንዲያገኝ የምትጥረዉ ሙዚቀኛ ምንይሹ ክፍሌ ሙዚቃ የዓለም ህዝቦች ቋንቋ መሆኑ መሆኑን ሳትናገር አላለፈችም። በኔዘርላንድ፣ በጀርመን፣ በቤልጂየምና በሌሎች አዉሮጳ ሃገራት ታዋቂነትን ያተረፈችዉ ምንይሹ፤ ሙዚቃዋን ባቀረበችበት መድረክ ሁሉ የሃገርዋን የተለያዩ ባህሎች ቋንቋና ሌሎች ገፅታዎችን ማስተዋወቁዋን ሙዚቃዋን የሚያደምጡ አዉሮጳዉያንም ይመሰክሩላታል።

Deutschland 27. Africa Festival Würzburg
ምስል DW/S. Mnette


በድሬዳዋ ከተማ ተወልዳ አድጋ በ17 ዓመቷ ብሄራዊ ትያትርን ተቀላቅላ ከዝያም በአዉሮጳ ዉስጥ የ19 ዓመት ቆይታዋና የሙዚቃ ሕይወትዋ፤ ሰላም ለህጻናት፣ ስለ ደጉ ሸማኔ፤ ስለ ዉኃ፤ ብሎም ስለታዋቂዉ የኢትዮጵያ ቡናና መገኛዉን ከፋን በሙዚቃዋ አወድሳለች አስተዋዉቃለች። በአማርኛ በጉራጊኛ፣ በሲዳሚኛ፣ በወላይትኛ፣ በኦሮሚኛ እና በሌሎች የኢትዮጵያ ቋንቋዎች እያዜመች ኢትዮጵያ የብዙ ብሄር ብሄረሰቦች መኖርያ፤ የተለያዩ ዉብ ባህሎች መገኛ መሆንዋን በግዙፍ መድረኮች ከታዋቂ የዓለም ሙዚቀኞች ጎን ተሰልፋ ለኢትዮጵያ አዚማለች በዜማም አስተዋዉቃለች። ከዚህ ልምዷ በመነሳት ሁላችንም በሞያችን በአቅማችን ማድረግ፤ እኛነታችን ማስተዋወቅ አለብን ስትል ምክርዋን አስተላልፋለች።
ሙሉዉን ቅንብር የድምፅ ማድመጫ ማዕቀፉን በመቻን ይከታተሉ።

አዜብ ታደሰ
አርያም ተክሌ