1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ኢስታንቡል፤ ቱርክ የስደተኞች ማጎሪያ አልሆንም አለች

ሰኞ፣ ጥቅምት 8 2008

ቱርክ ስደተኞች ወደ አዉሮጳ ኅብረት ሃገራት እንዳይገቡ እንድታግድ የቀረበላትን ሃሳብ እንደማትቀበለዉ አስታወቀች። ፕሬዚደንት ራሲፕ ጣይብ ኤርዶኻን ሀገራቸዉ «ማጎሪያ ጣቢያ» እንዳልሆነችና ስደተኞችንም በቋሚነት ለማስተናገድ እንደማትችል ዛሬ አስታዉቀዋል።

https://p.dw.com/p/1GqbH
Türkei Istanbul Besuch Merkel mit Erdogan
ምስል Getty Images/G. Bergmann/Bundesregierung

[No title]

ስደተኞችን በሚመለከት ከጀርመን መራሂተ መንግሥት አንጌላ ሜርክል ጋር ከተነጋገሩ ከአንድ ቀን በኋላ ኤርዶኻን በቴሌቪዥን የቀጥታ ስርጭት ባደረጉት ቃለመጠይቅ፤ ገንዘብ ስጡን እና ስደተኞቹን እዚሁ እናስቀራለን የሚል መግባቢያ አንቀበልም ነዉ ያሉት። ከሜርክል ጋር በተነጋገሩበት ጊዜም ቱርክ የስደተኞች ማጎሪያ ጣቢያ ትሆናለች ብሎ ማንም መጠበቅ እንደማይኖርበት ግልፅ ማድረጋቸዉንም በይፋ ተናግረዋል። ያም ቢሆን ግን ሕገ-ወጥ ስደተኞች በአግባቡ በቁጥጥር ሥር መሆን እንደሚኖርባቸዉ መስማማታቸዉንም ኤርዶኻን ገልጸዋል። የስደተኞችን ጎርፍ ለመግታት የአዉሮጳ ኅብረት ቱርክን በማሳተፍ አሳካዋለሁ ያለዉ እቅድ መስመር መያዙን ያመለከቱት ሜርክል በበኩላቸዉ፤

«ሕገ-ወጥ ፍልሰትን መመለስ መግታት ከፈለግን፤ ይህን ለማድረግም ተስማምተናል። ከዚያ በኋላ ለሕጋዊ ፍልሰት ምን አይነት እድል እንዳለ ማሰብ ይኖርብናል» ብለዋል።

Pressekonferenz Merkel Davutoglu
ምስል Reuters/M. Sezer

የአዉሮጳ ኅብረት ቱርክ ስደተኞችን ባሉበት እንድታቆይ 3 ቢሊዮን ዩሮም ለመስጠትአቅዷል። ኤርዶኻን ግን ከዚህም ሊጨምር እንደሚችል አመልክተዋል።

የአውሮጳ ህብረት ስደተኞች ወደአባል ሃገራቱ እንዳይገቡ የቱርክን ትብብር ጠይቋል። ቱርክም በምላሹ መሟላት አለባቸው ያለቻቸውን ሶስት ጥያቄዎች አቅርባለች። በህብረቱ እና በቱርክ መካከል ሊኖር የሚችለው ትብብር ምን እንደሚመስል ወደፊት የሚታይ ይሆናል።

የጀርመን መራሒተ መንግሥት አንጌላ ሜርክል ስለዚሁ በተለይ የርስበርሱን ጦርነት የሚሸሹትን ሶርያውያን ስደተኞችን ባካባቢያቸው ማስተናገድ ስለሚቻልበት ጉዳይ በቱርክ መዲና አንካራ ትናንት ከቱርክ ፕሬዚደንት ረቼፕ ጣይብ ኤርዶኻን ጋር መክረዋል። የመራሒተ መንግሥቷ የቱርክ ጉብኝት ባሁኑ ጊዜ በመደረጉ በሃገር ውስጥ ትችት ቢፈራረቅበትም፣ ከፍተኛ ትርጉም ሊኖረው እንደሚችልም ነው የተሰማው።

ሸዋዬ ለገሠ/ይልማ ኃይለ ሚካኤል

አርያም ተክሌ

አዜብ ታደሰ