1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

አፍጋኒስታን ከ9/11 በኋላ

ማክሰኞ፣ ነሐሴ 3 2003

በአዉሮጳዉያኑ 2001ዓ,ም ታሊባን ከስልጣን ሲወገድ 600,000 ነበር የካቡል ኗሪዎች ቁጥር። አሁን በዋና ከተማዋ ከአራት እስከ አምስት ሚሊዮን ኗሪ ተጨናንቀዉ ይኖሩባታል።

https://p.dw.com/p/RcIB
ካቡልምስል DW

በተለይ በርካታ የእርዳታ ድርጅቶች ጽህፈት ቤቶች በብዛት በሚገኙባቸዉ አካባቢዎች የልማት ሂደቱ የሚታይ ሲሆን በዚህ የአገሪቱ መሪ ብቻ ሳይሆኑ በዋና ከተማዋ ምዕራባዊ ክፍል የካርተ ሴህ አካባቢ ኗሪዎችም ይስማማሉ። እዚህም እዚያም ይቀጠቀጣል፤ ይቆረጣል። አካባቢዉ ዛሬ ሲመለከቱት ግንባታ ላይ ነዉ። በየቦታዉ የሚታየዉ ያዉ ተግባር ነዉ። ይህ ደግሞ ለካቡል አንድ ጥሩ ዜና ነዉ። «ግንባታ ባለበት፤ መዋዕለ ንዋይ ፍሰት አለ፤ ያ ደግሞ ተስፋ ነዉ።» ይላል የታክሲ አሽከርካሪዉ ሚርዋይስ።

Flash-Galerie Afghanistan Bollywood in Kabul Satelittenschüssel
ምስል AP

ካርተ ሴህ አንድ ወቅት በካቡል መካከለኛ ደረጃ ላይ የሚገኙ ሰዎች መኖሪያ ነበረች። ባለቤቶቹ ከመሰደዳቸዉ በፊት አካባቢዉ አብዛኞቹ ከጭቃ በተሰሩ አነስተኛ ጎጆዎች የተሞላ ነበር። ጦርነቱና የከተማዉ ኗሪዎች ቁጥር መጨመር ደግሞ የኑሮ ደረጃዉ መካከለኛ የሚባለዉን ሕዝብ ወደዋና ከተማዋ ማዕከል ገፋዉ። አሁን ዱባይ ዉስጥ እንዳሉት አለያም የፓኪስታን ነጋዴዎችን ቪላ የመሳሰሉ በወርቅ ቅብ ያጌጡ ቋሚዎች በተዘጉ መኖሪያ ቤቶች ተገጥግጠዋል። ከፔለ ኤ ሶርከ ማለትም ከቀዩ ድልድይ አጠገብ፤ የምንዱባኑ መንደር ከካርተ ሴህ ገጥሟል። በዚያ ላይ የብሄር ስብጥር ህብሩ ግሩም ሆኖ ይታያል ። ቡርቃ የሚለብሱ ሴቶች እዚህ እጅግም አይታዩም። ዋና ጎዳናዉ ብቻ በአስፋት በመሠራቱ በመጋቢ መንገዶች የሚጓዙ አልፎሂያጅ ትላልቅ ተሽከርካሪዎች መንገደኛዉን አዋራ እያትጎለጎሉ ያለብሳሉ።

Buddhastatuen in Bamiyan Flash-Galerie Taliban Krieger
ምስል AP

ታሊባን ገንዘብ አስገድዶ ይቀበላል

በባዛሩ ላይ የተገኘ እያንዳንዱ ነጋዴ የየራሱ ታሪክ አለዉ። «ሃጂ ሙራድ አሊ እባላለሁ» አሉ አንድ አጠር ያሉ የሃይማኖት ኮፍያ የደፉ ሰዉ። «32 ጊዜ በታሊባን ስቃይ ተፈፅሞብኛል።» አነስተኛ ዳቦ ቤት አላቸዉ። ባቅላባ፤ ብስኩትና ሌሎች ጣፋጮች ይሸጡባታል። ላለፉት 10ዓመት የንግድ ቤታቸዉ እዚሁ ናት። «ታሊባኖች ገና አንድ አዲስ ልብስ ለብሰህ ስትታይ ይመጡብሃል። አሁን ሃብታም የጦር አዛዥ መስለሃል ብለዉ በሰንሰለት ግርፊያ ይጀምራሉ።» በርካታ ሰዎችን እንዲህ እያሳቃዩ በአንፃሩ እነሱ ይዝናናሉ። ይህን የሚያደርጉትም ገንዘብ ፍለጋ ነዉ። ከኮመዲኖ መሳቢያ ዉስጥ ሙራዲ አሊ አንድ የተሰበረ መቆለፊያ አወጡ፤ የተሰበረዉን ለይተዉ እያሳዩ፤ «ከሁለት ሳምንታት በፊት ቤቴ ተዘረፈ፤ ፖሊሶች መጡ፤ ሆኖም እኔን በመርዳት ፋንታ ገንዘብ እንድሰጣቸዉ ፈለጉ።» አሉ። እንደዉም ዛሬ ዛሬ ወደእነሱ መሄድ እንደማያስፈልግ ነዉ አሊ የተረዱት። «ከፖሊስ ብትከራከር ያስሩሃል። ስለዚህ እኔ አፌን ዘግቼ ነዉ የምኖረዉ አለበለዚያ በመስኮት ጭላንጭል ብርሃን በሚገባባት እስር ቤት መጣል ይጠብቀኛል።»

የምክር ቤት አባላት ባለጸጎች ናቸዉ

እንደሩሲያዊ ካቡል ተመልሳ መኖር ችላለች። ሶንያ፤ የሞስኮዋ ወጣት ከአፍጋኒስታናዊዉ ባለቤቷ ሳንጃር በካርተ ሴህ መኖሪያዋን አድርጋለች። ሁለቱ እሱ ፖላንድ ነጻ የትምህርት እድል አግኝቶ ይማር በነበረበት ወቅት ነዉ የተዋወቁት። አሁን በምክር ቤት አባላት መኖሪያ አቅራቢያ ይኖራሉ። «ጎረቤቶቻችን የመንግስት ባለስልጣን ናቸዉ። ከገጠር ቢመጣም ባጭር ጊዜ ዉስጥ ነዉ ባለጸጋ የሆነዉ።» ይላል ሳንጃር። «እንደ አንድ የመንግስት ተቀጣሪ ይሄን ሁሉ ገንዘብ ከየት አመጣዉ የሚል ጥያቄ ይመጣብሃል።»

ከነዳሽ ዘይት፤ ወይ ከአደንዛዥ እፅ፤ ወይም ከሌላ ንግድ ገንዘብ ይሠራል። ስለዚህ ጉዳይ ህዝቡ ብቻ ሳይሆን በካቡል የተስፋፋዉ ግንባታ በራሱ ብዙ ይናገራል። ይህ ሁሉ ታዲያ የሳንካርን አመለካከት ቀይሮታል። «በጣም አዝናለሁ፤ በፊት መምረጥ የዜግነት ግዴታ ይመስለኝ ነበር፤ መምረጥ አለብኝ ብዬም አምን ነበር። አሁን ግን ይኸዉ ከአንድ ማፊያ የመጋፈጥ እንጂ ከመንግስት የምሟገት አይመስለኝም።» ምክር ቤትና 90ዎቹ የነበረዉ የእርስ በርስ ጦርነት የአንድ ሳንቲም ሁለት ገፅ መስለዉ ነዉ ለሳንጃር የሚታዩት። «የምክር ቤት ተወካዮች በሙሉ ገዳዮች ናቸዉ። እነዚህ ናቸዉ በወቅቱ የበርካታ ሰዎችን ህይወት የቀጠፉት። 60 ሟቾች ደም ተጠያቂ ናቸዉ። ያኔ አዉቶማቲክ መሳሪያ እኛ ላይ ተኩሰዋል። ዛሬ ደግሞ ምክር ቤት ተቀምጠዋል።» ሳንጃር ምዕራባዉያን እነዚህን የምክር ቤት አባላት እንደዴሞክራሲ ተምሳሌት መዉሰዳቸዉ ሊገባቸዉ አልቻለም። ለእሱ እነሱ ፍርድ ቤት መቅረብ ይገባቸዋል።

ማርቲን ጌርነር

ሸዋዬ ለገሠ