1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

አፍሪቃዉያን ተገን ጠያቂዎች

ዓርብ፣ መስከረም 20 2009

የስደተኞች ቀዉስን በተመለከተ የጀርመን ፖለቲካ አትኩሮቱ በአብዛኛዉ በሶርያ፤ በኢራቅና በአፍጋኒስታን ላይ ነዉ። ባለፈዉ ዓመት ጀርመን የገቡት አብዛኞቹ ስደተኞች ከነዚህ ሦስት ሃገራት ቢሆንም የሜዲተራንያ ባሕርን አቋርጠዉ ወደ አዉሮጳ የገቡ አፍሪቃዉያን ስደተኞች ጥቂት አይደሉም።

https://p.dw.com/p/2Qmdi
Niger Konvoi in Agadez
ምስል DW/A. Kriesch

Warum afrikanische Migranten ihre Heimat verlassen - MP3-Stereo

 

አፍሪቃዉያኑ ስደተኞች ሜዲተራንያንን አቋርጠዉ በተለይ ወደ ኢጣልያ በመግባት ወደ ሌሎች የአዉሮጳ ሃገራት ለመሻገር ይሞክራሉ። የአዉሮጳዉ ኅብረትና የጀርመን መንግሥት ስደተኞች ወደ ሃገራቱ እንዳይገቡ ርምጃዎችን እንደሚያካሂዱ ይገልፃሉ። ሕይወታቸዉን በከፍተኛ አደጋ ላይ ጥለዉና እጅግ ከፍተኛ ገንዘብ ከፍለዉ ከአፍሪቃ ሃገራት ወደ አዉሮጳ የሚያቀኑ ስደተኞች ለመሰደድ የሚያነሳሳቸዉ ዋና ምክንያት ምን ይሆን? ዝርዝር      

በማዕከላዊ ኒጀር የምትገኘዋ አቧራሟዋና በቆሻሻ የተሞላችዉ አጋዴዝ ከተማ ከፍተኛ የሥራ አጥነትና ድኅነት ይታያል። በዓለም ደኃ ከሚባሉት ሃገሮች ተርታ መጨረሻ ላይ የምትገኘዉ ምዕራብ አፍሪቃዊትዋ ኒጀር ፤ አፍሪቃዉያን ስደተኞች አዲስ እድልን የማግኘት ሙሉ ተስፋን ሰንቀዉ ኒጀር አጋዴዝ የሚገኘዉን በረኃ አቋርጠዉ ወደ ሊቢያና አልጀርያን ተሻግረዉ ወደ አዉሮጳ የሚያቀኑባት ከተማም ናት። በዚች ከተማ በኩል በዓመት ወደ 120 ሺህ አፍሪቃዉያን ስደተኞች ወደ አዉሮጳ ለመሻገር ይነሳሉ ሲል የዓለም አቀፉ የስደተኞች ድርጅት «IOM» ግምቱን አስቀምጦአል።       

Niger Agadez Sahara Flüchtlinge Schuhe
ምስል Reuters/Akintunde Akinleye

በቅርቡ በኒጀርዋ አጋዴዝ ከተማ የገባዉና እጅግ ከስቶ ጠዉልጎ የሚታየዉ የ 24 ዓመቱ ማሃማዱ ኮንቴ ወደ አዉሮጳ ለማለፍ ወደ አጋዴዝ የመጣዉ ከማሊን ነዉ። አጋዴዝ ለሱና ለመሰሎቹ ወደ አዉሮጳ መሸጋገርያ ከተማ ነች። ማሃማዱ ታሪኩን እንዲህ ሲል ይጀምራል። በትዉልድ ሃገሪ በቡርኪናፋሶ ወላጆቼና ሁለት ታናናሽ እህቶቼ ይኖራሉ። ቤተሰቦቼን ለማስተዳደር ለትንንሽ እህቶቼ የትምህርት ቤት የወር ክፍያን፤ የሚመገቡትን ሁሉ ለመክፈል ስል ትምህርቴን አቋርጬ ስሰራ ነበር። ከዚህ ሌላ ይላል ማሃማዱ ወደ አዉሮጳ ለመሻገር እንድችል የሚያስፈልገኝን ገንዘብ ሁሉ ለማጠራቀም ሦስት ዓመታት ሌት ከቀን ሰርቼአለሁ። ይህን ገንዘብ ለማጠራቀም መሃማዱ በቡርኪናፋሶ አለ የተባለ ሥራን ሁሉ ሳያማርጥ ነበር የሰራዉ።  ማሃማዱ ገንዘቡ ሲሟሟላለት የጀመረዉን ሥራ ሁሉ አቋርጦ ከቡርኪናፋሶዋ ዋና ከተማ ዋጋዱጉ፤ አፍሪቃዉያኑ ወደ አዉሮጳ ለመጓዝ የበረሃ ጉዞን ከሚጀምሩባት ወደ ኒጀርዋ አጋዴዝ ከተማ አቀና። በቅድምያ ግን ስለጉዞዉ ከባድነትና ቀላልነት እናቃለን ከሚሉት ባልንጀሮቹ ሁሉ መረጃን ሰብስቦ ነበር።  

« በመንገድ ላይ ምንም ዓይነት ችግር እንደማያጋጥመኝ ነዉ የነገሩኝ። እዚህ ችግር ላይ የነበሩት ጉደኞቼ በቀጣይ ወደ ሊቢያ አቅንተዋል »

መሃማዱ ከዋጋዱጉ ተነስቶ አጋዴዝ እስኪደርስ ወደ አዉሮጳ ለመሻገር ያጠራቀመዉ ገንዘብ ሁሉ ተሟጦ አልቆአል። እሱና ሌሎች ስደተኞች ወደ አጋዴዝ የተጓዙበት አዉቶቡስ በየመንገዱ በተለያዩ ሰዎች ተገዶ ሲቆምና፤ ሰዎች ገንዘብ ሲቀበሉም ነበር።    

የዓለም አቀፉ የስደተኞች ድርጅት «IOM» ፖሊሶች ይህን ዓይነት ድርጊት ይፈጽማሉ  መባሉን በተለያዩ ዘገባች አረጋግጦአል። ማሃማዱ ኮንቴ በኒጀርዋ አጋዴዝ ከተማ ሲደርስ በኪሱ ስባሪ ሳንቲም አልነበረዉም። አሁን የስደተኛ እና ሰዎችን በሕገ-ወጥ የሚያዘዋዉሩ ሰዎች በሚገኙባት አጋዴዝ ከተማ ነዋሪ ሆንዋል፤ ከተማዋ ደግሞ ሥራ፤ ገንዘብ፤ እንዲሁም ተስፋ የማይታይባት ናት። በአጋዴዝ የሚኖሩ አፍሪቃዉያን ስደተኞች ሁሉ የመሃማዱን ዓይነት ተሞክሮን እንዳላቸዉ ነዉ የሚተርኩት።     

የጀርመኑ የልማት ትብብር ሚኒስትር ጌርድ ሙለር በነሐሴ ዋር ላይ አጋዴዝን እንደጎበኙ የሰሙት ይህንኑ ዓይነት መሰል ታሪክ ነዉ። የአዉሮጳ ኅብረት አንድ በአጋዴዝ ከተማ ለሚገኝ የስደተኞች መቀበያ ማዕከል ድጋፍ በመስጠት ወደ ሃገራቸዉ ለመመለስ የሚፈልጉ ስደተኞች ይረዳል። የጀርመኑ የልማት ትብብር ሚኒስትር ይህን ማዕከል ከጎበኙ በኋላ እንደተናገሩት፤

« በመዓከሉ የሚገኙትን ወጣቶች የፊት ገጽታና አቋም እንዲሁም ያላቸዉን ሃሳብ ለማወቅ እነሱን ሲያይና ከነሱ ጋር ሲነጋገር  ተስፋ የማጣት ትርጉሙ ምን እንደሆን በድንብ ይረዳል። እነዚህ ወጣቶች ከወደፊት ተስፋቸዉ ሌላ የሚፈልጉት ሌላ ጉዳይ የለም፤ ሥራና ፤ በሕይወት መኖርን ነዉ የሚሹት»  

የአዉሮጳዉ ኅብረት «ከሃገራት ጋር በአጋርነት መፍትሄን ማግኘት» በሚል ተገን ጠያቄዎች ያላቸዉን ልዩ የሆነ ሚና ከየሃገራቱ ጋር መነጋገር እንደሚሻ ተገልጾአል። ከነዚህ ሃገራት መካከል ኒጀር በተለይ ደግሞ የስደተኞች መሸጋገርያ የሆነችዉ የኒጀርዋ አጋዴዝ ከተማን ያካትታል። እንደ አዉሮጳዉ ኮሚሽን ግምት በአንድ ሳምንት ጊዜ ዉስጥ ብቻ በሽዎች የሚቆጠሩ ስደተኞች የኒጀርዋን አጋዴዝ ከተማን አቋርጠዉ ወደ ሰሜናዊ አፍሪቃ ይጓዛሉ። ስደተኞቹ በቀጣይ በሊቢያ የባህር ጠረፍ በኩል አድርገዉ ሜዲተራንያን አቋርጠዉ ወደ አዉሮጳ ለመግባት የሚሞክሩ ናቸዉ።  

Karte Niger Agadez Deutsch
ምስል DW

አዉሮጳ አፍሪቃዉያኑ ስደተኞች በአፍሪቃ እዳሉ እንዲቆዩና በዝያዉ ተስፋን የሚያገኙበትን መንገድ ለማበጀት እንደሚፈልግ ተገልጾአል።  የአዉሮጳ ኅብረት ኮሚሽን ምክትል ፕሬዚዳንት ፍራንስ ቲመርማንስ ኅብረቱ በተለይ ስደተኞችን በተመለከተ ሊሠራ ከሚፈልግባቸዉ ሃገሮች መካከል ማሊ፤ ናይጀርያ፤ ሴኔጋልና ኒጀር መሆናቸዉን ገልፀዋል። የአዉሮጳ ኅብረትም ሆነ የጀርመን መንግስት ከአፍሪቃ የሚሰዱ ወጣቶችን የስደት መንስዔ ለመቅረፍ የመጀመርያዉ ርምጃ አንድ መሆኑን ይስማማሉ። የጀርመኑ የልማት ትብብር ሚኒስትር ጌርድ ሙለር ይኸዉም ይላሉ፤

« እዚህ ላይ ወሳኙ ነጥብ በነዚህ ሃገራት ዉስጥ የሚገኘዉ ወጣት ትዉልድ በሃገሩ ብሩህ ተስፋ እንዲኖረዉ  አዉሮጳ መዋዕለ ንዋይ ማፍሰስ ይኖርበታል።»  

ይህ መዋዕለ ንዋይ ትምህርት ቤቶችን፤ የስልጠና ማዕከሎችን ለመዘርጋትና አስፈላጊ ለተባሉ መሰረተ ልማት ማሟያ የሚሚዉል ነዉ። በዚህም አዉሮጳ እስከ ጎርጎረሳዉያኑ 2020 ዓ,ም ድረስ እስከ 8 ቢሊዮን ይሮ ርዳታ እንደሚያደርግ ይጠበቃል። ለአፍሪቃ ሃገራት ከዓመታት ጀምሮ የልማት ርዳታን በመስጠት ያለዉን የአኗኗር ሁኔታ ለማማሻሻል ቢሞክርም ዉጤቱ ግን እንብዛም አመርቂ አለመሆኑ እዉን ነዉ የተመለከተዉ። እንድያም ሆኖ የጤና አጠባበቅ የትምህርት አሰጣጥ በመሳሰሉት መሻሻሎች መታየታቸዉ ተዘግቦአል።

የንስ ቦርሸር / አዜብ ታደሰ

ኂሩት መለሰ