አፍሪቃና ዴሞክራሲን የመትከል ጥረቷ በ2015ዓም
2015 ዓም ተጨማሪ ዴሞክራሲ ለማስገኘት ትግሉ ተጠናክሮ የተካሄደበት እና ትግሉን ለማክሸፍ ከባድ ርምጃ የተወሰደበት ዓመት ነበር።
« ሶስተኛ የስልጣን ዘመንን አንቀበልም!»
በቡሩንዲ ፕሬዚደንቱ በስልጣን ለመቆየት ማቀዳቸውን ባለፉት የፀደይ ወራት ባስታወቁበት ጊዜ በሺዎች የሚቆጠሩ የሃገሪቱ ዜጎች እቅዱን በመቃወም አደባባይ ወጡ። የሃገሪቱ ሕገ መንግሥት የፕሬዚደንቱን ስልጣን በሁለት የስልጣን ዘመን ቢገድብም፣ ፕሬዚደንት ፒየር ንኩሩንዚዛ ይህንኑ የሕገ መንግሥቱን አንቀጽ በማስቀየር ባለፍው ሐምሌ ራሳቸውን ለተጨማሪ የስልጣን ዘመን አስመርጠዋል። የፀጥታ ኃይላት በዚህ አንፃር የታየውን ተቃውሞ በኃይል ደምስሰዋል፣ ተቃዋሚዎች ታስረዋል፣ ተገድለዋል፣ ክትትልም አርፎባቸዋል። በሰበቡም ቡሩንዲ በወቅቱ በእርስ በርሱ ጦርነት አፋፍ ላይ ትገኛለች።
ከጎረቤት ርዋንዳ ጋር የተፈጠረው ጠብ
በቡሩንዲ የተፈጠረው ቀውስ ከጎረቤት ርዋንዳ ጋር ባለው ግንኙነትም ላይ አሉታዊ ተፅዕኖ ማሳረፉ አልቀረም። የርዋንዳ ፕሬዚደንት ፖል ካጋሜ«በስተ ግራ» የቡሩንዲ መንግሥት የገዛ ራሱን ሕዝብ ይጨፈጭፋል ሲሉ በቡሩንዲው አቻቸው ፒየር ንኩሩንዚዛ «መሀል» ላይ ወቀሳ ሰነዘሩ። ይሁን እንጂ፣ ካጋሜም ቢሆኑ ስልጣናቸውን የመልቀቅ ሀሳብ የላቸውም። በጎርጎሪዮሳዊው 2017 ዓም በርዋንዳ በሚደረገው ፕሬዚደንታዊ ምርጫ ላይ መወዳደር አይፈቀድላቸውም። በዚህ የተነሳም እጩነታቸውን የሚያግደውን የሕገ መንግሥቱን አንቀጽ አስቀየሩ። የርዋንዳ ሕዝብ ይህንኑ የሕገ መንግሥት ማሻሻያ መደገፍ አለመደገፉን በሬፈረንደም ማሳወቅ ይኖርበታል።
ኮንጎ ብራዛቪል፣ ከ30 ዓመት በኋላም በስልጣን የመቆየት ፍላጎት
ዴኒ ሳሱ ንጌሶም ለተጨማሪ የስልጣን ዘመን ሁኔታዎችን አመቻችተዋል። የ72 ዓመቱ ፕሬዚደንት እጎአ ከ1992 እስከ 1997 ዓ,ም በስተቀር ኮንጎ ብራዛቪልን ከ30 ዓመት በላይ በመምራት ላይ ናቸው። የሃገሪቱን መሪ የስልጣን ዘመን በሚመለከተው የሕገ መንግሥቱ አንቀጽ ላይ በተደረገው ማሻሻያ ላይ ባለፈው ጥቅምት ወር በተካሄደው ሕዝበ ውሳኔ ወቅት ደም አፋሳሽ ሁከት ቢፈጠርም፣ በይፋ የወጡ ውጤቶች እንዳሳዩት፣ ማሻሻያው የሰፊውን ሕዝብ ድጋፍ አግኝቶዋል። የተቃውሞ ቡድኖች ውጤቱን የተጭበረበረ ነው በሚል አልተቀበሉትም። የጎረቤት ዴሞክራቲክ ኮንጎ ሬፓብሊክ ሕዝብም ፕሬዚደንት ጆሴፍ ካቢላ በያዙት ተመሳሳይ እቅድ አንፃር ተቃውሞ ጀምሮዋል።
ታሪካዊ የስልጣን ለውጥ በናይጀሪያ
ሙሀማዱ ቡሀሪ በናይጀሪያ በተካሄደ ዴሞክራሲያዊ ምርጫ ለስልጣን የበቁ የመጀመሪያው ርዕሰ ብሔር ሆኑ። ከእርሳቸው በፊት ሃገሪቱን የመሩት ጉድላክ ጆናታን ስልጣናቸውን በቀላሉ ያስረክባሉ ብሎ የጠበቀ አልነበረም። ሙስናን ለማብቃት ቆርጠው የተነሱት ቡሀሪ አዳዲስ በለስልጣናትን ከመሾማቸው ጎን፣ ያላቸዉን የግል ንብረት ግልጽ አደርገዋል። ለቡሀሪ በውቅቱ ትልቁ ተግዳሮት ቦኮ ሀራምን መታገል ነው።
ከዚህ በላይ የለም፣ 100% ለኢትዮጵያ መንግሥት
ወደ 35 ሚልዮን የሚጠጉ ኢትዮጵያውያን ባለፈው ግንቦት ወር አዲስ ምክር ቤት መርጠዋል። በምርጫው ገዢው ኢሕአዴግ እና አገር ፓርቲዎቹ 547 የምክር ቤቱን መንበሮች አሸንፈዋል። ከምርጫው በፊት በምክር ቤቱ ውስጥ በአንድ እንደራሴ ተወክለው የነበሩት የተቃዋሚው ቡድኖች በዚሁ ምርጫ አንድም ውክልና ሳያገኝ ቀረ። የተቃዋሚ ቡድኖች እና ጋዜጠኞች ከምርጫው ቀደም ባሉ ጊዚያት በመንግሥት ግዙፍ ጭቆና ደርሶባቸዋል ሲሉ ታዛቢዎች ተችተዋል።
ታንዛንያ፣ ማጉፉሊ ምን ያደርጉ ይሆን?
ማጉፉሊ ምን ያደርጋሉ? በዚሁ በማህበራዊ መገናኛ ብዙኃን በቀረበው መፈክር ስር አፍሪቃውያን ተጠቃሚዎች ወጪን መቀነስ የሚያስችሉ የተለያዩ ሀሳቦችን በትዊተር አስፋፍተዋል። ምክንያቱም፣ አዲሱ የታንዛንያ ፕሬዚደንት ጆን ፖምቤ ማጉፉሊ የመንግሥቱን ገንዘብ ለውዱ ይፋ ግብዣ ከሚያወጡ ይልቅ የሀኪም ቤት አልጋዎችን ለመግዛቱ ቢጠቀሙበት እንደሚመርጡ አሳይተዋል። ይህ አሰራራቸው ግን ሁሉን አላስደሰተም። ፕሬዚደንታዊው ምርጫ ተጭበርብሮዋል በሚል የሚጠረጥሩት የተቃዋሚ ቡድኖች የማጉፉሊን ድል አልተቀበሉትም። ለነገሩ፣ ታዛቢዎች ተቃዋሚዎች በምርጫው ደህና ዕድል እንደነበራቸው ገምተው ነበር።
ኮት ዲ ቯር፣ የሴቶች ድጋፍ ያልተለያቸው ዋታራ
የኮት ዲ ቯር ዜጎች እጎአ ጥቅምት 25፣ 2015 ዓምን በትልቅ ስጋት ነበር የጠበቁት። እንደሚታወሰው፣ ከአምስት ዓመት በፊት የተካሄደው ፕሬዚደንታዊ ምርጫ በሃገሪቱ የእርስ በርሱን ጦርነት ቀስቅሶ ነበር። በዚያ አንፃር፣ የዘንድሮው ምርጫ በሰላማዊ ሁኔታ ነበር የተጠናቀቀው። «አ ዴ ኦ» በሚል ቅጽል ስም የሚጠሩት ፕሬዚደንት ዋታራ በምርጫው የርዕሰ ብሔርነቱን ስልጣን እንደያዙ መቆየት አስችሏቸዋል። ማሪያም ሱዋሬ «በስተ ግራ» በምርጫ ዘመቻ ወቅት ለዋታራ አድናቆታቸውን ገልጸዋል። ዋታራ ያካሄዱት የምርጫ ዘመቻ በተለይ ከሴቶች ብዙ ድጋፍ አግኝቶዋል።
አንጎላ፣ የተሟጋቾች ፍርድ ቤት መቅረብ
ወጣት አንጎላውያን ባለፈው ህዳር ወር በመዲናዋ ሉዋንዳ ክስ በተመሰረተባቸው የአንድ የወጣቶች ድርጅት 17 አባላት ላይ ችሎት ይካሄድበት በነበረው ፍርድ ቤት ደጃፍ ተቃውሞ አካሂደዋል። 17 ቱ በአንድ መጽሐፍ መሸጫ መደብር በመገናኘት ሰላማዊ ተቃውሞ ሰልፍ በማደራጀታቸው የመፈንቅለ መንግሥት ለማሴር ነው የተገናኛችሁት በሚል ነው የተከሰሱት። አንጎላን ካለፉት 36 ዓመታት የሚመሩት ኾዜ ኤድዋርዶ ዶሽ ሳንቶሽ በተቺዎቻቸው አንፃር ጠጣር ርምጃን ይወስዳሉ።
ማሊ ሰላም አላገኘችም
የማሊ መንግሥት እና በርካታ ታጣቂ ቡድኖች ባለፈው ግንቦት አጋማሽ አንድ የሰላም ስምምነት ተፈራረሙ። በቀጠለው ሰኔ ደግሞ የቱዋሬግ ዓማፅያን ቡድን ውሉን ፈረመ። በዚህም ከረጅም ድርድር በኋላ በሰሜናዊ ማሊ ሰላም የሚወርድ መስሎ ነበር። ይሁንና፣ ተቀናቃኞቹ የቱዋሬግ ቡድኖች ባለፈው ነሀሴ ወር እንደገና እርስ በርስ መዋጋት ጀመሩ፣ ሙስሊም ፅንፈኞችም ከአንድ ወር በፊት በመዲናይቱ ባማኮ አንድ ትልቅ ሆቴል በኃይል በመያዝ፣ 170 ሰዎችን ባገቱበት እና 20 ሰዎች በገደሉበት ጥቃት ይኸው ተስፋ እውን ሳይሆን ቀርቶዋል።
የብሩሕ ለውጥ ተስፋ በቡርኪና ፋሶ
በቡርኪና ፋሶ የመጀመሪያ ዙር ፕሬዚደንታዊ ምርጫ አስገራሚ ድል ተመዝግቦዋል። ቡርኪናቤዎቹ፣ 27 ዓመታት ሙሉ ሃገሪቱን የመሩትን ብሌዝ ካምፓዎሬን ከስልጣን ካስወገዱ ከአንድ ዓመት በኋላ፣ ባለፈው ህዳር ወር ሮኽ ማርክ ካቦሬን አዲሱ ርዕሰ ብሔር አድርገው መርጠዋል። ባለፈው ጥቅምት ወር እንዲካሄድ ታቅዶ የነበረው ፕሬዚደንታዊው ምርጫ ፕሬዚደንታዊው ክብር ዘብ የከሸፈ መፈንቅለ መንግሥት ሙከራ ካደረገ በኋላ ነበር ሕዝቡ ከረጅም ጊዜ ወዲህ በጉጉት ሲጠብቀው የነበረው ምርጫ ወደ ህዳር ወር የተላለፈው።
ቀውስ እና ሁከት በማዕከላይ አፍሪቃ ሬፓብሊክ
የማዕከላይ አፍሪቃ ሬፓብሊክ ሕዝብም ባለፈው ጥቅምት ወር ምርጫ እንዲያካሂድ ታቅዶ ነበር። ይሁን እንጂ፣ በሙስሊሞቹ የሴሌካ ዓማፅያን እና በክርስትያኖቹ የፀረ ባላካ ሚሊሺያ ደጋፊዎች መካከል በየጊዜው የቀጠለው የኃይል ተግባር ምርጫውን አከላክሎ ቆይቶዋል። አሁን ምርጫው እጎአ በታህሳስ፣ 2015 ዓም መጨረሻ እንዲደረግ ተወስኖዋል። ከዚያ በፊት መራጩ ሕዝብ ባለፈው እሁድ የፕሬዚደንቱን ስልጣን ቢበዛ ከሁለት የስልጣን ዘመን እንዳይበልጥ የሚል አንቀጽ ጭምር በሰፈረበት አዲሱ ሕገ መንግሥት ላይ ሬፈረንደም እንዲያካሂድ በታቀደው መሰረት፣ ምንም እንኳን ኃይል ቢታከልበትም ባለፈው እሁድ ሕዝቡ በብዙ የሃገሪቱ አካባቢ ድምፁን ሰጥቶዋል።