1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

አፍሪቃና «ትራንስፓረንሲ ኢንተርናሽናል»

ማክሰኞ፣ ግንቦት 14 2004

የአፍሪቃው ክፍለ ዓለም በኤኮኖሚ ዕድገት እያሳየ መሆኑ ቢነገርም፤ ዕድገቱ ፤ ኑዋሪዎቹን ፤ እኩል የዕድገቱ ተጠቃሚ ባለማድረጉ አወንታዊ መልክ አይታይበትም ተብሏል። ይህ የተነገረው በቅርቡ፤ የአፍሪቃ የዕድገት መድረክ (አፍሪቃ ፕሮግረስ ፓነል )የተሰኘው መድረክ በኮፊ አናን ሊቀመንበርነት፤ ባካሄደው ጉባዔ ላይ ነው። ---

https://p.dw.com/p/150Fo

መድረኩ እስኮትላንድ ውስጥ የተቋቋመው፤ እ ጎ አ በ 2005 ዓ ም፤ በሰሜኑ ንፍቀ ክበብ ሞቃት ወራት እ ጎ አ ከሐምሌ 6 እስከ 8 ግሌን ኢግልስ ላይ የ 8 ቱ ታላላቅ ባለኢንዱስትሪ አገሮች መሪዎች ጉባዔ (G8)በተካሄደበት ወቅት ነው። ዋና ተግባሩም፤ በአፍሪቃ ዕድገት ይመዘገብ ዘንድ ሁኔታዎችን እየተከታተለ ማነቃቃት ነው። በአፍሪቃ ዕድገት እንዲመዘገብ ፤ ከዐበይት አንቅፋቶቹ መካከል አንዱ ፤ ለምሳሌ ያህል ሙስና መወገድ ይኖርበታል።ታዲያ ፣ ይህን ለማሣካት ምን ያህል ጥረት ተደርጓል? ከአፍሪቃ የዕደገት መድረክ አባላት መካከል ፤ ጀርመናዊው የፀረ ሙስና ድርጅት (ትራንስፓረንሲ ኢንተርናሽናል)መሥራች ፒተር አይገን ለዶ ቨለ የእንግሊዝኛው ክፍል በዘጡት ቃለ ምልልስ ላይ እንደገለጹት ፣ የአውሮፓ ዐበይት ኢንዱስትሪ ኩባንያዎች ለአፍሪቃ ፈላጭ ቆራጭ ባለሥልጣናት ጎቦ በመስጠት ያደረሱት ጉዳት በቀላል የሚገመት አይደለም።

Korruptionsindex 2010 Transparency International Deutsch Ausgewählte Länder

« በሙስና ለመግዛት ተሞክሯል። በተለይ ለአፍሪቃ የሚጠቅመው ጉዳይ ሌላ ሆኖ ሳለ፣ ብዙዎቹ የአፍሪቃ ተባባሪዎች፤ እዚህም ላይ ፣b ትልልቅ ኩባንያዎች ያሏቸው ጀርመንና ፣ ሌሎቹም ሃገራት፣ በአፍሪቃ አገሮች ዕጣ ፈንታ መወሰን ለሚችሉ ባለሥልጣናት፤ በትጋት ጉቦ ሲሰጡ ነው የኖሩት። እንዚህ ተባባሪዎች፤ እዚህ ጀርመን ውስጥም ሙስና አላካሄዱም አይባልም። እንዲያውም 100 የሚሆኑ ከሙስና ጋር ግንኙነት ያላቸው የታላላቅ ኩባንያዎች ጉዳዮች በህግ መዝገብ ተይዘዋል። እነዚህ የውጭ ሰዎችን ፤ ውሳኔ የመወሰን ሥልጣን ያላቸውን፤ በአፍሪቃ ጭምር ጉቦ ሲሰጡ የነበሩ ናቸው።»

እ ጎ አ፤ ሰኔ 11 ቀን 1938 ዓ ም በአውጉስቡርግ (ጀርመን)የተወለዱት፤ ፒትር አይገን የህግ ባለሙያ ሲሆኑ፣ በኤኮኖሚ ልማት 25 ዓመታት ሠርተዋል። በተለይ በዓለም ባንክ የአፍሪቃና ላቲን አሜሪካ መርኀ-ግብሮች ኃላፊ በመሆን ማገልገላቸው የሚታውስ ነው። የመንግሥት ያልሆነውን በዓለም ዙሪያ ሙስናን የሚታገለውን በአሁኑ ጊዜ ከ 90 በላይ በሚሆኑ አገሮች የሚንቀሳቀሰውን ትራንስፓረንሲ ኢንተርናሽናል የተሰኘውን ድርጅት የመሠረቱት እ ጎ አ በ 1993 ዓ ም ነው። ለእኒህ የፀረ ሙስናው ድርጅት መሥራች፤ ከቀረቡላቸው ጥያቄዎች ጥያቄዎች መካከል፤ በእርግጥ በአፍሪቃ ዕድገት ይታያልን ? የሚለው ነው።

«እርግጥ ዕድገት አለ። በሀገራት ውስጥ በተለይ በአህጉራዊ ሥራ አንቀሳቃሽ ድርጅቶች፤ ኔፓድን ወይም ኢፕራም በመሳሰሉ ወይም በከፍተኛ ደረጃ፤ ህገ-ወጥ በሆነ መንገድ፣ የገንዘብ ወደ ውጭ መውጣትን የሚቆጣጠርና የሚቀጣ የአፍሪቃን ኅብረት የመሳሰሉም ለአህጉሩ፣ ጠቀሜታ፤ ትርፍም ሆነ የመሳሰለ ዕድል እንደሚቀርባቸው ሲደርሱበት የነበረና ያለ ጉዳይ ነው። ይኸም ሁሉ ሆኖ፣ አዳዲስ የአፍሪቃ ተባባሪዎች፣ ወደ ክፍለ ዓለሙ በመግባት ላይ ሲሆኑ፤ እነርሱም ፤ ባለፉት ጊዜያት የተፈጸሙትን አንዳንዶቹን ስህተቶች፣ እንደገና ሲደግሟቸው ያታይል። »

Karte Afrika
ምስል DW

አፍሪቃ፤ የተፈጥሮ ሀብት የታደለ ክፍለ ዓለም ቢሆንም ፣ በተለያዩ ምክንያቶች ገሚሱ ህዝብ ፤ ከድህነት ጠርዝ በታች ባለ ደረጃ ላይ እንደሚገኝ ነው የሚነገርው። አፍሪቃ በራሱ ገዥዎች ፈላጭ ቆራጭነት፤ የፍትኅ እጦት፤ ስግብግብነት፤ የተዛባ የሀገር ሀብት አያያዝና አከፋፈል ፤ እነዚህና አያሌ ሰው ሰራሽ እንቅፋቶች ዕድገቱን በመግታት፣ ህዝቡን ለረሃብ ፤ ለበሽታና ለመሳሰሉ አስከፊ ሁኔታዎች ዳርገውታል። ክፍለ ዓለሙ፤ በውጭው ዓለም እኩል ዕድል አለማግኘቱም ተጨማሪ ሳንክ እንደፈጠረበት ይገኛል።

«በዘገባችን ላይ ምናልባት ጠንከር ብለው ከቀረቡት መልእክቶች አንዱ በእኩልነት አለመኖር ላይ ያተኮረው ነው! ይህ የአኩልነት አለመኖር፤ ሞራልና ፍትኀዊነት የጎደለው መሆኑ ብቻ ሳይሆን፤ በተጨማሪ ለኤኮኖሚ ልማት እጅግ ብርቱ ደንቃራ ነው። ሥራ አጥ ወጣቶች አሉ ። ቁጥራቸው እጅግ እየጨመረም ነው የሚሄደው። ሥራ ፈላጊ ሰዎች፤ ወጣቶች ፤ በሚመጡት ጥቂት ዓመታት ቁጥራቸው ወደ 150 ሚሊዮን ከፍ ማለቱ አይቀሬ ነው። ይህ ደግሞ ብስጭትን ፤ ቁጣን ይሆናል የሚያስከትለው። በዓረቡ ዓለም ገንፍሎ እንደታየው የወጣቶች መነሣሳት ማለት ነው።»

ተክሌ የኋላ

አርያም ተክሌ