አጭር የስልክ የፁሁፍ መልዕክት (SMS)20ኛ አመት
ዓርብ፣ ኅዳር 28 2005አጭር የፁሁፍ መልዕክት ማለትም SMS በእጅ ተንቀሳቃሽ ስልክ መላክ ከተጀመረ እነሆ 20 አመት ተቆጠረ። እኢአ በ1980ቹ የዚህን አገልግሎት ፅንሠ ሀሳብ ያቀረቡት ጀርመናዊው ፍሪድሄልም ሔለብራንድ የፖስት ካርድ እና ቴሌክስ መልዕክቶችን እንደ መነሻ አድርገዉ ነበር የተነሱት፤ ያኔም የደረሱበት ድምዳሜ አብዛኞቹ መልዕክቶች ከ 160 ፊደል ያልበለጡ መሆናቸውን ነው። በዚህም የተነሳ የመልዕክቱ ርዝመት ከ160 ፊደል እንዳያልፍ ተወሰነ። ሀሳብን ለመግለፅ 160 ፊደላት በጣም ትንሽ ናቸዉ እያሉ ብዙ ተጠቃሚዎች ይወቅሳሉ። በተለይም ለእያንዳንዱ የስልክ መልዕክት ገንዘብ መክፈል ያለባቸው።
ባለፈው አመት ብቻ ጀርመን ውስጥ 46 ቢሊዮን ጊዜ የስልክ መልዕክቶች ተልከዋል። ቴክኖሎጂው ከዕለት ተዕለት ኑሮ ጋ ተዋህዷል ማለት ይቻላል። በአማካይ በቀን አንድ ሰው ጀርመን ውስጥ ሁለት አጭር የፁሁፍ መልዕክት ይልካል ተብሎ ይታሰባል።
ከ 20 ዓመታት በፊት SMS ይህን ያህል ስኬታማ ይሆናል ብሎ ያሰበ ሰው አልነበረም። የመጀመሪያው መልዕክት እኢአ ታህሳስ 3 1992 ዓም ተላከ። በወቅቱ አንድ ተንቀሳቃሽ ስልክ 1,500 €ያወጣ ስለነበር እና በየቤቱ የተስፋፋ ስላልነበር፤ የመጀመሪያውም መልዕክት ከኮምፒውተር ወደ ስልክ ነበር የተላከው። መልዕክቱም «መልካም የልደት በዓል!» የሚል ነበር። ላኪዎቹ የብሪታንያ የቴሌኮሚኒኬሽን ሰራተኞች ናቸው። ኋላም የቴሌኮሚኒኬሽን መስሪያ ቤቶች ለደንበኞቻቸው ይህንን ቴክኖሎጂ ያቀርቡ ጀመር።
በኢትዮጵያም በስልክ መልዕክት መላላክ ከተጀመረ አመታት ተቆጥረዋል።
ነጃት ዳውድ ከኢትዮጵያ በጣም የሚጠቅም አገልግሎት ነው ትላለች።
ነጃት በቀን ከ 3- 4 የግል እና የስራ መልዕክቶች ትልካለች። ሰላምታ፣ ቀጠሮ፣ እንዲሁም ሌሎች አስፈላጊ መልዕክቶች በፁሁፍ መልክ ይላካሉ። ከፁሁፍ መልዕክቱ ጋ ተያይዞ አዳዲስ የአገላለፅ ምህፃረ ቃላትም ተፈጥረዋል። ይህስ በአማርኛ ቋንቋ ይቻላል? ነጃትን እና ሌሎች ኢትዮጵያንን ጠይቀናል።
ዳዊት ወርቁ በዶቼ ቬለ ፌስቡክ ገጽ ላይ ፤ኢትዮጵያ ውስጥ ከተጀመረ ጊዜ አንስቶ የዚህ አገልግሎት ተጠቃሚ መሆናቸውን ፅፈዉልናል።« ጥሩ የመገናኛ ዘዴ ቢሆንም ውድ ነው፡፡ ቢሆንም ከድምጽ ጥሪ ይሻላል (ዋጋው)፡፡እኔ በደንብ ተረት ተረት ማውራት እስኪቀረኝ እየተጠቀምኩበት ነው፡፡ በርግጥ ቴሌ ከሚሰጣቸው ግልጋሎቶች ሁሉ ይኼኛው ማለትም አጭር የጽሑፍ መልዕክት የሚያረካኝ ነው፡፡ »ብለዋል።
የፌስ ቡክ ተከታታያችን ኢትዮጵያ ውስጥ ያልተስፋፉ በርካታ ቴክኖሎጂዎች እንዳሉም ሳይጠቁሙ አላለፉም። ልክ ነው። የድምፅ መልዕክት መተው ፣ ቪዲዮ እና ፎቶዎች መላክ የተለመዱ ሆነዋል። ኡርስ ማንስማን c´t የተሰኘ የኮምፒውተር መጽሔት ጋዜጠኛ ናቸዉ። አዲስ በመጡ ዘመናዊ ስልኮች አማካኝነት የቴሌኮሚኒኬሽን አገልግሎቶች አቅራቢች ኪሳራ ላይ እየወደቁ ነው ይላሉ።
« SMS ስኬታማ የሆነበትን ጊዜ አልፎ፤ አሁን የኢንተርኔት አገልግሎቶች ቀድመዉታል። ኢንተርኔት የመረቡ አገልግሎት አቅራቢዎች በዉስን ዋጋ ነፃ በሚባል ደረጃ ተጠቃሚዎች ያለ ገደብ መልዕክት የሚልኩበትን መንገድ ፈጥረዋል። ይህም የሚላከው ን የSMS መልዕክት ቁጥር ከፍ እንዲል ቢያደርገዉም ገቢው ግን እየቀነሰ ነው።»
ማንስማን ከሚሏቸው የኢንተርኔት አገልግሎቶች አንዱ «ዋትስአፕ» ነው። ይህ ፕሮግራም የጹሁፍ መልዕክቶች፣ ፎቶዎች ብሎም ቪዲዮችን ያለ ትርፍ ክፍያ በአለም ዙሪያ መላክ እንዲቻል ይረዳል። «ዋትስአፕ» ን ለመጠቀም ወሳኙ ነገር ፤ዘመናዊዎቹ ማለትም « ስማርት ፎን» በመባል የሚታወቁ ስልኮች ላይ ፕሮግራሙ መጀመሪያ መጫን ይኖርበታል፤ በተጨማሪም የኢንተርኔት አገልግሎት ያስፈልጋል።
ከጊዜ ወደ ጊዜ እንደ «አይፎን» እና ሌሎች ዘመናዊ ስልክ ተጠቃሚዎች ቁጥር በማደጉ፤ በቀን ከ10 ቢሊዮን በላይ መልዕክቶች በ «ዋትስአፕ» አገልግሎት አማካኝነት ይላካሉ። ይህ በተለይ የቴሌኮሚኒኬሽን አገልግሎት አቅራቢዎችን እያሳሰበ ይገኛል። ስለሆነም አቅራቢዎቹ አዲስ አገልግሎት ይዘው ለመውጣት አስበዋል። ይህም አገልግሎት«ጆይን» ይባላል። ራፋኤላ ሞህል «ቴልታሪፍ» ለሚባለው የቴሌኮሚኒኬሽን አገልግሎት ሰጪ ድርጅት ይሠራሉ። የ«ጆይን»ን ስኬታማ የመሆን ጉዳይ ጥያቄ ውስጥ ይከቱታል።
« በአሁኑ ሰዓት ይህን ለማድረግ ከባድ ነው ባይነኝ፤ ምክንያቱም «ዋትስአፕ» በቀላሉ ግንባር ቀደም ስፍራዉን ይዟል። «ጆይን» የግድ ሌላ የበለጠ ነገር ይዞ መምጣት ይኖርበታል። በአሁኑ ሰዓትእንደሚመስለኝ ይህ የሚቻል አይደለም።»
ተክኖሎጂው እየተሰፋፋ በሄደ ቁጥር ተጠቃሚዎች አትራፊ እየሆኑ መጥተዋል። ለምሳሌ ኦስማን ጋሹ የተባሉ አድማጫችን «በፌስ ቡክ የማደርጋቸው ግማሽ ንግግሮች የሚያልቁት በፁሁፍ ነው፤ ስለዚህ አጭር የፁሁፍ መልዕክት ለኔ ወሳኝ ነው» ይላሉ። ክንፌ ተፈራ ደግሞ «አሳብንይገልፃልአንደሌሎችማአበራዊድረገፅችዋጋሁቢቀንስጥሩነበር» ብለዋል።
አጭር የፁሁፍ መልዕክት አገልግሎትን ማለትም የ(SMS)ን 20ኛ አመት አስመልክቶ የተጠናከረውን የድምፅ ዘገባ ማድመጥ ይችላሉ።
ልደት አበበ
ሸዋዬ ለገሰ