አዲሱ የግሪክ ጥምር መንግሥት
ሐሙስ፣ ሰኔ 14 2004
አዲሱ የግሪክ ካቢኔ ዛሪ ቃለ መሃላ ፈፅሟል ። የአዲሱ ጠቅላይ ሚኒስትር የአንቶንዮስ ሳማራስ ፓርቲ ኒያ ዲሞክራሲያ ወይም አዲስ ዲሞክራሲ በቀድሞው የገንዘብ ሚኒስትር ኢቫንጌሎስ ቬኒሴሎስ ከሚመራው የሶሻሊስቶቹ ፓርቲ ፓሶክና ከለዘብተኛው ግራ ፓርቲ የግራዎቹ ዲሞኮራሲያዊ ፓርቲ ጋር ነው የተጣመረው ። ሶስቱ ፓርቲዎች በጋራ ከ ግሪክ 300 የምክር ቤት መቀመጫዎች 179 ኙን ይዘዋል ። ሁለቱ ተጣማሪ ግራ ዘመም ፓርቲዎች በአዲሱ የሳማራስ ካቢኔ ውስጥ የራሳቸውን ሚኒስትሮች ግን ማስገባት አልፈለጉም ።
3 ቱ የግሪክ ፓርቲዎች ተጣምረው መንግሥት ለመመስረት የተስማሙት 3 ቀናት ከወሰደ ድርድር በኋላ ነበር ። ትንንት ማምሻውን የግሪክ ጠቅላይ ሚኒስትር ሆነው የተሰየሙት አንቶንዮስ ሳማራስ ቃለ መሃላ ከፈሙ በኋላ ባሰሙት ንግግር የግሪክ ህዝብ ድጋፉን እንዲሰጣቸው ጠይቀዋል ።
« ክእግዚአብሄር እርዳታ ጋር በተቻለ ፍጥነት ከገባንበት ቀወስ እንድንወጣ የግሪክ ህዝብ አገር ወዳደነቱን እንዲያሳይ እንዲተባበርና በኔም ላይ እምነት እንዲኖረው እጠይቃለሁ ። ለህዝባችን የሚጨበጥ ተስፋ መስጠት እንድንችል የሚመሰረተው መንግሥት ጠንክሮ እንዲሰራ እማፀናለሁ ። »የግሪክ ተጣማሪ ፓርቲዎችን የማያስማሟቸው የተለያዩ ጉዳዮች አሉ ። ከለጋሽ ሃገራት ጋር በተደረገ ውል የመንግሥት ይዞታዎች ወደ ግል እንዲዛወሩና ከሥራ ገበያ ጋር የተያያዙ የተሃድሶ እርምጃዎች ተግባራዊ እንዲሆኑ ወግ አጥባቂዎቹ የተስማሙ ሲሆን የግራ ፈለግ ተከታዮች ደግሞ ይቃወሙታል ። የፍልሰት መርህም ላይ እንዲሁ አወዛጋቢ ነው ።የግራ ዲሞክራሲያዊ ፓርቲ ፣ ሳማራስ አሁን የተዘጋጁበትን ሶሻሊስቶቹ ያጸደቁትን 2ተኛ ትውልድ የውጭ ዜጎች የግሪክ ዜግነት የሚያገኙበት ሁኔታ እንዲቃለል የሚለውን ደንብ ለመሻር ሳማራስ አሁን የተዘጋጁበትን ሃሳብ አጥበቀው በመቃወም ላይ ነው ።ከወግ አጥባቂዎቹ ጋር የተጣመሩት ሁለቱ ፕርቲዎች በአዲስ መንግሥት ውስጥ ብዙም ጠለቅ ብለው ላለመግባት እየተጠነቀቁ ነው ። ሃያሲያን እንደሚሉት በተለይ በእሁዱ ምርጫ በታሪኩ ዝቅተኛ ድምፅ ያገኘው ሶሻሊስቱ ፓሶክ በአዲሱ መንግሥት ብዙ ሃላፊነቶችን ከመውሰድ ወደ ኋላ እያለ ነወ ። ሶሻሊስቱ የህዝብ እንደራሴና የቀድሞው ሚኒስትር ኒኮስ ሲፉናኪስ ግን ይህን አይቀበሉም ።«ህገ መንግሥታችን በሚለው መሰረት በምርጫ አብላጫ ድምፅ ያገኘው ፓርቲ በመንግሥት ምስረታው ዋና ዋና ሃላፊነቶችን ይወስዳል ። እርግጥ የፓሶክ ፓርቲ አዲሱን መንግሥት ይደግፋል ፤ መንግሥቱ እዳይፈርስም ጠንካራ መሰረት ይሆናሉ ። ሶሻሊስቶቹ ሌላ አጣዳፊ ሥራም ማከናወን አለባቸው ። ይኽውም በተቻለ ፍጥነት ራሳቸውን ስርዓት ማስያዝና ወደ ግራው ፓርቲ የሄደውን መራጭ ህዝብ መመለስ ይኖርባቸዋል ።»
ፓሶክ ሶሻሊስታዊ ገፅታውን በማጠናከር ሲጠመድ ወግ አጥባቂዎቹ ደግሞ ፣ የፓርቲ አባላት ካልሆኑ ነፃ የምጣኔ ሃብት አዋቂዎች ጋር ሃገሪቱን ይመራሉ ። ለምሳሌ የምጣኔ ሃብት ፕሪፌሰር ና የግሪክ ብሔራዊ ባንክ ሃላፊ ቫሲላስ ራፓኖስ የገንዘብ ሚኒስትር ሲሆኑ ፣ ምክትላቸው ደግሞ የአሁኑ የጊዜያዊው መንግሥት የገንዘብ ሚኒስትር ያኒስ ዛንያስ ሳይሆኑ አይቀርም እየተባለ ነው ። ራፓኖስ ገና ቃለ መሃላ ስላለፈፀሙ ሃሙስ በሚካሄደው የአውሮፓ ህብረት የገንዘብ ሚኒስትሮች ጉባኤ ላይ የሚካፈሉት ዛንያስ ይሆናሉ ። በዚሁ ስብሰባ ላይ የሳማራስ መንግሥት የቁጠባ እርምጃዎች ተግባራዊ የሚሆንበት ጊዜ ቢያንስ በ 2 ዓመት እንዲራዘም ይጠይቃል ተብሎ ይታመናል ።አዲሱ ጠቅላይ ሚኒስትር በምርጫ
ዘመቻ ወቅት የአውሮፓ ህብረት ለግሪክ ባቀረበው የተሃድሶ መርሃ ግብሩ ላይም እንደሚደራደሩ ቃል ገብተዋል ሆኖም የምርጫው እለት ምሽት ላይ ይህንኑ ጉዳይ ላለማንሳት ተጠንቅቀው ከዚያ ይልቅ ለስምምነቱ ተገዥ እንደሚሆኑ ነው ያሳወቁት ።ይህን መግለጫቸውንም ግራ ፅንፈኛው የሲሪዛ ህብረት መሪ አሌክሲስ ትሲፕራስ ተቃውመዋል ። የሲሪዛ የምጣኔ ሃብት ጠቢብ ዩክላይዱስ ትሳካሎቶስ እንደሚሉት መንግሥት የገባውን ቃል ማክበረ አለማክበሩን ፓርቲው ይከታተላል ።
«ፖለቲከኞች ከምርጫ በፊት ያሉትን ከምርጫ በኋላም መናጋራቸው ጠቃሚ ነው ። በዚህ ምክንያትምም የግራዎቹ ፓርቲ ወግ አጥባቂዎቹም ሆኑ ሶሻሊስቶቹ በምርጫ ዘመቻ ወቅት የገቡትን ቃል እንዲጠብቁ አበክሮ ይጠይቃል በምርጫ ዘመቻ ወቅት ከግራ ፅንፈኞች ጋራ ሳይሆን በቁጠባ መርሃ ግብሩ ላይ መደራደር እንደሚፈልጉ ነው ያሳወቁት ። ይህን የሚያደርጉ ከሆነ የሚያስፈራቸው ነገር አይኖርም። አለበለዚያ ግን መላውን ህብረተሰብ በራሳቸው ላይ ማስነሳታቸው የማይቀር ነው ። »
ሂሩት መለሰ
አርያም ተክሌ