1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

አዲሱ የኢትጵያ ጠ/ሚ እና መርሐቸዉ

ሰኞ፣ መስከረም 14 2005

በጠቅላይ ሚንስትር መለስ ዜናዊ ዘመን ተመሳሳይ ጥሪ ተደርጎ ገቢራዊነቱ መና መቅረቱን ዋቢ የሚጠቅሱ ወገኖች የአዲሱ ጠቅላይ ሚንስትር ጥሪም ካንጀት መሆኑን ይጠራጠራሉ።ሌሎች ደግሞ ጥሪዉ ከልብ ቢሆን እንኳን የአዲሱ ጠቅላይ ሚንስትር ሥልጣን የይስሙላ በመሆኑ ገቢር ሊያደርጉት አይችሉም ባዮች ናቸዉ።

https://p.dw.com/p/16DTd
Ethiopian state television announced on August 21, 2012 that Hailemariam Desalegn will be acting prime minister, after the death of Ethiopian Prime Minister Meles Zenawi.
ምስል CC-BY-SA- World Economic Forum

የጠቅላይ ሚንስትር መለስ ዜናዊ ሞት ተከታይ፣ ደጋፊ፣ አድናቂዎቻቸዉን፣ ከቤተ-ሰብ፥ ከዘመድ አዝማዶቻቸዉ እኩል፣ ማቅ አስለብሶ፣ እንባ እንዳራጨ ሁሉ፣ አብዛኛ ተቃዋሚዎቻቸዉን አንድም ለባሕል ወግ አሳድሮ፣ ሁለትም ሰብአዊነታቸዉን አግዝፎ፣ ሰወስትም፣ለፖለቲካ ከሰብ አትብቶ የሐዘን፣ ማስተዛዘኛ መልዕክቶቻቸዉን አሰምቷል።የዉጪ ወዳጅ፣ አጋሮቻቸዉም እንዲሁ።ከሐዘኑ ጥልቀት፣ ምክንያት ልዩነት በስተቀር እኩል ያዙኑት ወገኖች የድሕረ-መለሷ ኢትዮጵያ ፖለቲካዊ ጉዞ በዘመነ-መለስ ጎደናዉ መቀጠል አለበት፣ የለበትም ልዩነት ላይደማመጡ እንደተወዛገቡ ኢትዮጵያ አዲስ መሪ ተሾሙላት።የአዲሱ መሪ ሹመት መነሻ፣ የዝግቡ ቅንጭብ ምክንያት ማጣቀሻ፥ የኢትዮጵያ ፖለቲካዊ ጉዞ እንዴትነት ማጠያየቂችን ነዉ ላፍታ አብራችሁኝ ቆዩ።

አንድ ወዳጄ ባለፈዉ ቅዳሜ የላከልኝን ኢሜይል ሥከፍተዉ አይኔ አጭር መልዕክቱ ላይ ነጥሮ ከመልዕክቱ ግርጌ ከተለጠፈችዉ ትንሽ ፎቶ ላይ አረፈ።ፎቶዉ የሥጋ ቤት ነዉ።የሉካንዳ።

«በጣም አስቂኝ፣ በእዉነቱ ሰዉዬዉ ብልሕ ነጋዴ መሆን አለበት።» ብዬ ተረጎምኳት ፎቶዉን ለወዳጄ የላከለት ወዳጁ በእንግሊዝኛ የፃፋትን መልዕክት።ብልሁን ነጋዴ ትኩር ብዬ ሳይ፣እስከወገቡ ከሸፈነዉ ባንኮኒ የዉጪ ግርግዳ ላይ የተፃፈዉን አነበብኩት።ፅሁፉ ወንከርከር ያለ ነዉ።የወንካራዉ ፅሁፍ መልዕክት ግን የኢትዮጵያን ሰሞናዊ እዉነት ባጭሩ አለዉ።«ጀግናዉ አይሞትም ሥጋ ቤት.....ጥሬና ጥብስ አለ።»ብሎ።የኢትዮጵያ መንግሥት ተቃዋሚዎች ከዉጪም ከዉስጥም የድሕረ-መለስዋ ኢትዮጵያ ከዘመነ-መልሷ የተሻለች እንድትሆን በተደጋጋሚ ጠይቀዋል።

ዓለም አቀፍ የመብት ተሟጋቾችና ገለልተኛ የፖለቲካ ተንታኞችም የወደፊቷ ኢትዮጵያ ገዢዉ ፓርቲና ተቃዋሚዎች ከስካሁኑ በተሻለ ሁኔታ ተግባብተዉ የሚሠሩባት፥ጋዜጠኞች በነፃነት የሚዘግቡባት፥ መቻቻል የሠፈነባት፥ ሰብአዊ መብት የሚከበርባት፥ ልማትዋ የሚጠናከርበት እድትሆን መክረዋል።ከኢትዮጵያዉያን የፖለቲካ ተንታኞች ዶክተር መሐሪ ታደለ ማሩ አንዱ ናቸዉ።

የኢትዮጵያ መንግሥቷ ኢትዮጵያ ዉሎ አዳር ግን ከወደፊቷ ኢትዮጵያ ይልቅ በቅርቡ ያረፉት የጠቅላይ ሚንስትር መለስ ዜናዊ ታላቅ ገድል፥ ግዙፍ ድል፥ እቅድ፥ ራዕይ፥ ምትክ የለሽ መሪነት ነዉ የደመቀባት።የመንግሥት መገናኛ ዘዴዎች የመዓልት-ወሌት ዘገባ ርዕስ፥ ምስልና ድምፅ እሳቸዉና የሳቸዉ ነዉ።


የኢትዮጵያ ገዢ ፓርቲ የኢሕአዴግ አምደ መረብ ወይም ልሳኖች የየዕለት ሐተታ ጭብጥና ፎቶ እሳቸዉና የሳቸዉ ነዉ።የመንግሥት ባለሥልጣናት ንግግር መግለጫ፥ የተራዉ ሰዉ አስተያየትም እሳቸዉ ሥለ እሳቸዉ ነዉ።«ጀግናዉ አይሞትም፥ ጥብስም-ጥሬም አለ» አለ-ብልሁ ባለልኳንዳ።ኢትዮጵያ ፖለቲካዋም እንደ ልኳንዳዋ ብስልና ጥሬ የመሆኑ ምልክት ይሆን?።ጥያቄዉ ሳያበቃ አቶ ሐይለማርያም ደሳለኝ እንደ መለስ ምክትል ብዙ ጊዜ ያሉትን በቀደም እንደ ምትካቸዉ ለሐገሪቱ ምክር ቤት አባላት ደገሙት።

የመማር፣ ተምሮ፣ በሐኪም ጥሩ ደሞዝ ጥሩ ኑሮ የመኖር ጅምር ተስፋቸዉን ሰዉተዉ ላመኑ፣ ለተቀበሉት አለማ ስኬት ምናልባትም ሕወታቸዉን ጭምር ለመሰዋት የመወሰናቸዉ ፅናት፣ ደፈጣ ተዋጊ ቡድናቸዉን ለሐገር መሪነት ድል የማብቃታቸዉ ብስለት፣ በችግር የተተበተበችዉን ትልቅ ሐገር ሃያ አንድ ዓመት የመምራታቸዉ ብልጠትን መዘከር በርግጥ ክፋት የለዉም።

መለስ ያለሙ፣ ያቀዱ የጀመሩትን ከግብ ለማድረስ ተከታይ ጓዶቻቸዉ ቃል መግባት፣ መማል፣ መገዘታቸዉ የቀሪ ደቀመዛሙርት ወግ፥ ተገቢም ነዉ።አለማ፣ እቅድ፣ ጅምሩ ለሐገርና ለሕዝብ እስከጠቀመ ድረስ ደግሞ ገቢር የማድረጉ ሐላፊነት የመለስ ደጋፊ ተከታዮች ብቻ ሳይሆን የመለስ፣ የድርጅታቸዉና የተከታዮቻቸዉ ተቃዋሚዎች፣ የገለልተኞች፥ የመላዉ ኢትዮጵያዊ ሁሉ ሐላፊነት መሆኑ ቸልመባሉ፥ የተቃዋሚዎች ጥያቄ፥ የመብት ተሟጋቾች ምክርና የፖለቲከ ተንታኞች ምክር የተዘንጋ መምሰሉ እንጂ ሥጋቱ።

የአዲሱ ጠቅላይ ሚንስትር የበቀደሙ መልዕክት ግን የገዢዉን ፓርቲ አቋምን ከመድገም እኩል መንግሥታቸዉ ጥያቄ፥ ምክር አስተያየቱን አይዘነጋዉም አይነት ይዘትም ተቀይጦበታል።

አቶ መለስ የሐገር መሪነቱን ሥልጣን በያዙ ሰሞን አንዱ ጋዜጠኛ «ደፈጣ ተዋጊ እያሉ የሐገር መሪ እሆናለዉ ብለዉ አስበዉ ያቁ ነበር» ብሎ ጠየቋቸዉ።«የለም አስቤ አላዉቅም። ምክንያቱም ትግሉ አንዱ ሲወድቅ ሌላዉ እየተካዉ የቀጠለ የቅብብሎሽ ሥለነበር።»አይነት ብለዉ መለሱ።

ገዢዉ ፓርቲ በቅርቡ «መተካካት» ባለዉ መርሑ መሠረት የምክትል ጠቅላይ ሚንስትርነቱንና የዉጪ ጉዳይ ሚንስትርነቱን ሥልጣን የዛሬ ሁለት አመት የያዙት አቶ ሐይለ ማይርያም ደሳለኝ በመለስ ሞት፥ የመሪነቱን ሥልጣን፥ በመለስ ቋንቋ ሲቀበሉ ያስተላለፉት ቅይጥ መልዕክት፥ የኢትዮጵያን የወደፊት ፖለቲካ በዘመነ-መለስ መርሕ ላይ መሥርተዉ ግን በአዲስ ጎደና ለማጓዝ የማቀዳቸዉ መንታ ሥልትን መጠቆሙ አልቀረም።

ግን አዲስ አይደለም።መለስ በሃያ-አንድ የመሪነት ዘመናቸዉ ብዙ ጊዜ ብለዉት ነበር።አቶ ሐይለ ማርያምም ከመለስ ሞት በሕዋላ ካንዴም ሁለቴ ብለዉታል።የሥልታዊ ጥናት ተቋም (ISS-በእንግሊዝኛ ምሕፃሩ) የፖለቲካ ተንታኝ ዶክተር ሠለሞን አየለ ደርሶ እንደሚሉት ቁም ነገሩ የመልዕክቱ አዲስ አሮጌነት አይደለም ቃል የተገባዉ መቼና እንዴት ነዉ-የሚለዉ እንጂ።

ቃሉ ከመደጋጋሙ፥ ከመቼነቱም በላይ ግን መሠረታዊዉ ጥያቄ፥የተገባዉ ቃል በርግጥ ገቢር ይሆናል ወይ-የሚለዉ መሆን አለበት።ጠቅላይ ሚንስትር መለስ ዜናዊ ከሞቱ በሕዋላ ወደ ሁለት ሺሕ የሚጠጉ እስረኞች በይቅርታ መለቀቃቸዉን ሰምተናል።የኢትዮጵያ መንግሥት በአሸባሪነት ፈርጆት ከነበረዉ ከኦጋዴን ብሔራዊ ነፃ አዉጪ ግንባር (ኦብነግ) ጋር ለመደራደር መስማማቱም ተዘግቧል።

እስረኞች በይቅርታም ይሁን በሌላ ምክንያት መለቃቀቸዉ በነፍጥ ከሚፋለመዉ ቡድን ጋር ለመደራደር የተደረገዉ ሥምምነትም የከረረዉ ፖለቲካዊ መርሕ የመለሳለሱ ምልክት መሆኑ አያጠያቅም።ሁሉም የተወሰነዉ ግን የመንግሥት ባለሥልጣናት እንዳስታወቁት የቀደሞዉ ጠቅላይ ሚንስትር በሕይወት በመበሩበት ጊዜ ነዉ።

ይሕ እዉነት የድሕረ-መለሷ ኢትዮጵያ የመለስን ዉሳኔዎች ገና አስፈፅማ አለማጠናቀቅዋን አመልካች ነዉ።በዚሕ መሐል የተሰማዉ የአዲሱ ጠቅላይ ሚንስትር አሮጌ ቃል ገቢራዊነቱን ብቻ ሳይሆን የመርሁን እንዴትነትም አጠያያቂ ያደርገዋል።

ዶክተር ሠለሞን እንዳሉት አዲሱ ጠቅላይ ሚንስትር ለገዢዉ ፓርቲም፥ ለጠቅላይ ሚንስትርነቱም በርግጥ አዲስ ናቸዉ።አዲስ ባይሆኑ እንኳን ሃያ-አንድ ዓመት አብዛኛዉን ጉዳይ ጠቅልለዉ የመሩ አንጋፋ ፖለቲከኛን መተካት ሲበዛ ከባድ ነዉ።መተካቱ ለዉጥ የሚጠይቅ ከሆነ ደግሞ ይበልጥ ከባድ ያደርገዋል።

አቶ ሐይለ ማርያም ከብዙ ተፅዕኖዎች ጋር ከተቃዋሚዎች፥ ከመብት ተሟጋቾችና ከነፃ ጋዜጠኞች ጋር ተባብሮ ለመስራት የገቡትን ቃል ገቢር ለማድረግ እንዲችሉ ዶክተር ሰለሞን እንደሚሉት የሁሉም ትብብር፥ ትዕግስትና ጊዜ ያስፈልጋቸዋል።


ተቃዋሚ ፖለቲከኞች በኢትዮጵያ ፖለቲካዊ ሒደት ሰፊ ተሳትፎ እንዲኖራቸዉ፥ ከገዢዉ ፓርቲ ጋር በጋራ ለመስራት ያልጠየቁበት ጊዜም የለም።በዚሕም ሰበብ የአዲሱ ጠቅላይ ሚንስትር የተባብረን እንሥራን ጥሪ አይቀበሉትም ማለት የራሳቸዉን ጥያቄ አፈረሱት ከማለት እኩል ነዉ።

ትብብሩ እንዴት ይጀመራል።የትብብሩ ደረጃስ እስከየት ነዉ የሚለዉ ጥያቄ በርግጥ ከሁለቱም ወገን ግልፅ መልስ የሚያሻዉ ጉዳይ ነዉ-የሚሆነዉ።በጠቅላይ ሚንስትር መለስ ዜናዊ ዘመን ተመሳሳይ ጥሪ ተደርጎ ገቢራዊነቱ መና መቅረቱን ዋቢ የሚጠቅሱ ወገኖች የአዲሱ ጠቅላይ ሚንስትር ጥሪም ካንጀት መሆኑን ይጠራጠራሉ።

ሌሎች ደግሞ ጥሪዉ ከልብ ቢሆን እንኳን የአዲሱ ጠቅላይ ሚንስትር ሥልጣን የይስሙላ በመሆኑ ገቢር ሊያደርጉት አይችሉም ባዮች ናቸዉ።ዶክተር ሰለሞን ግን፥ አስተያየት ጥርጣሬዉን የኢሕአዲግ ምክር ቤት አቶ ሐይለ ማርያምን የፓርቲዉ ሊቀመንበርና ጠቅላይ ሚንስትር፥ አቶ ደመቀ መኮንን ምክትል ሊቀመንበርና ምክትል ጠቅላይ ሚንስትር አድርጎ እስከመረጠበት ጊዜ ድረስ ይሰጥ ከበበረዉ አስተያየት ጋር ያመሳስሉታል።


የኢሕአዴግ ምክር ቤት ያሳየዉ አንድነት፥ ከሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ለሁለቱ ሹማምንት የተሰጠዉ ድጋፍ የፖለተካ ተንታኙ እንደሚሉት የአቶ ሐይለ ማርያም ሥልጣን የይስሙላ ነዉ የሚለዉን ጥርጣሬና አስተያየት ያከሽፈዋል።የዶክተር ሰለሞንን ሐሳብ ተቀብለን አዲሱ ጠቅላይ ሚንስትርና ምክትላቸዉ ከገዢዉ ፓርቲ ነባር ባለሥልጣናት ጠንካራ ድጋፍ አላቸዉ እንበል።አቅሙስ ነዉ ጥያቄዉ።

የገቡትን ቃል ገቢር ለማድረግም ሆነ የአቅም ሥልጣናቸዉን ደረጃ ለማረጋገጥ የሚመሠርቱት ካቢኔ ስብጥርና ጥንካሬ አሉታዊም ሆነ አወንታዊ ተፅዕኖ ማሳረፉ አይቀርም።የኢትዮጵያ የዉጪ መርሕ በኢትዮጵያ ረጂዎች፥ በወዳጆችዋና በአካባቢዉ ሐገራት ዘንድ ተቀባይነት እንዲኖረዉ ለማድረግ ደግሞ ከካቢኔዉም መሐል በዉጪ ጉዳይ ሚንስትርነት የሚሾሙት ሰዉ ችሎታ ወሳኝ ነዉ።

አቶ ሐይለ ማርያም ትናንትና ዛሬ የሁለቱን ሱዳኖች መሪዎች ለማስታረቅ አዲስ አበባ ላይ አስተናግደዋል።በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት አመታዊ ጠቅላላ ጉባኤ ላይ ለመካፈል ወደ ኒዮርክ ይሔዳሉ ተብሏል።ከዚያስ---ከዚያ የሚሆነዉን እስክናይ እስክንሰማ እንጠብቅ።ለዛሬዉ ነጋሽ መሐመድ ነኝ ቸር ያሰማን።

ነጋሽ መሐመድ
ሸዋዬ ለገሠ







epa03307749 (FILE) A file photo dated 17 September 2011 shows Ephiopian Prime Minister Meles Zeinawi speaking during a join press conference with his Egyptian counterpart Essam Sharaf (not pictured), in Cairo, Egypt. Reports on 16 July 2012 state that Meles Zenawi was unable to attend the opening on 15 July of the African Union Summit being held in Ethiopia because of rumoured health concerns. The Ethiopian government declined to make a statement on the issue. EPA/KHALED ELFIQI /POOL *** Local Caption *** 50045673
የቀድሞዉ ጠቅላይ ሚንስትርምስል picture-alliance/dpa
Ethiopian government spokesman Bereket Simon (R) makes the official announcement of the death of Prime Minister Meles Zenawi in Ethiopia's capital Addis Ababa August 21, 2012. Zenawi, regarded by the West as a bulwark against Islamic militancy, died while being treated abroad for an undisclosed illness, the government said on Tuesday. REUTERS/Tiksa Negeri (ETHIOPIA - Tags: POLITICS)
ነባሮቹ ባለስልጣናትምስል Reuters
***Für mögliche Ergänzungen der Karte, wie z.B. andere Sprachen, zusätzliche Orte oder Markierungskreuz, wenden Sie sich bitte an infografik@dw-world.de (-2566), Außerhalb der Bürozeiten an bilder@dw-world.de (-2555).*** DW-Grafik: Per Sander 2011_03_10_Laender_Prio_A_B
ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ