1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

አዲሱ የኢትዮጵያ ሕግና መያዶች

ረቡዕ፣ ሰኔ 30 2002

ሕጉ ከመዉጣቱ በፊት ተመዝግበዉ የነበሩት ድርጅቶች 3 522 ነበሩ።ሕጉ ከፀደቀ በሕዋላ የተመዘገቡት ግን አንድ ሺሕ ስድስት መቶ ሐምሳ አምስት ናቸዉ።ከነዚሕ መሐል 218ቱ ስማቸዉን፥ አስራ-ሰባቱ አላማቸዉን ቀይረዋል።

https://p.dw.com/p/ODAw
ርዳታ ያስፈልገዋልምስል AP

07 07 10

የኢትዮጵያ መንግሥት መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶችን (መያድ) ለመቆጣጠር አዲስ ሕግ ካወጣ ወዲሕ የመያዶች ቁጥር በግማሽ መቀነሱን የሐገሪቱ የፍትሕ ሚንስቴር አስታወቀ።ሚንስቴሩ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ባቀረበዉ ዘገባዉ እንዳስታወቀዉ ሕጉ ከመዉጣቱ በፊት ከ3 ሺሕ 5 መቶ በላይ መያዶች ተመዝግበዉ ነበር።ሕጉ ከፀደቀ በሕዋላ የተመዘገቡት ግን ከ1 ሺሕ 6 ብዙም አይበልጡም። አዲሱ ሕግ ከግብረሰናይ ድርጅቶችና ከመብት ተሟጋቾች የገጠመዉ ተቃዉሞ እንደቀጠለ ነዉ።ነጋሽ መሐመድ ዝር ዝር ዘገባ አለዉ

መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶችን-መያድ ባጭሩ ሥራና አሠራር ለመቆጣጠር የኢትዮጵያ መንግሥት ያረቀቀዉን ሕግ የሐገሪቱ ምክር ቤት ካፀደቀዉ አመት ከመንፈቅ አለፈ።በጣሙን የመብት ተሟጋች ድርጅቶችን፥ የሲቢል ማሕበራትንና የብጤዎቻቸዉን ሥራ-ና አሠራር ጫን-የሚለዉን ሕግ ብዙ አለም አቀፍ የመብት እና የፍትሕ ተቆርቋሪ ተቋማት ተቃዉመዉታል።

የኢትዮጵያ መንግሥት ግን ሕጉ በርዳታ ሥም ፍቃድ አዉጥተዉ፥ ገንዘብ እየሰበሰቡ ለግል ወይም ለቡድናት አለማ የሚንቀሳቀሱ ወገኖችን ለመቆጣጠር ያለመ ነዉ-ባይ ነዉ።ሕጉ ከፀደቀ ከአመት ከመንፈቅ በሕላ-የመያዶች ቁጥር በግማሽ ያሕል መቀነሱ ይላል-የፍትሕ ሚንስቴር ዘገባ -ወትሮም ቢሆን መያዶቹ ተመዘገቡ እንጂ በገቢር እንዳልነበሩ መስካሪ ነዉ።የሕጉ አወንታዊ ዉጤት ነዉ።

በደቡብ ኢትዮጵያ CRDA በሚል የእንግሊዝኛ ምሕፃረ ቃል የሚጠራዉ የክርስቲያናዊ የልማት በጎ አድርጎት ድርጅት ተጠሪ አቶ ብርሐኑ ገዙ እንደሚገምቱት ግን አዲሱ ሕግ አብዛኞቹን ድርጅቶች ካጣብቂኝ ነዉ-የዶለዉ።
የፍትሕ ሚኒስቴር ባለሥልጣናት ለምክር ቤት ሥላቀረቡት ዘገባ ማብራሪያ እንዲሰጡን በስልክ ጠይቀን ነበር።ቀጥሩን።በቀጠሩን ጊዜ ስንደዉል ግን የሉም ተባልን።ለምክር ቤት የቀረበዉ የፍትሕ ሚንስቴር ዘገባ እንደሚለዉ ግን በመያድ ሥም ሌላ ምግባርና አለማ የሚከዉኑ ወገኖችን በቅጡ ለመቆጣጠር ሕጉ በእጅጉ ጠቅሟል።አቶ ብርሐኑ ግን መንግሥት በድሮዉም ሕግ መቆጣጠር ጥፋተኞችን መቅጣትም ይችል ነበር።
ሕጉ ከወጣ በሕዋላ የተመዘገቡት መያዶች ቁጥር መቀነሱን ከተቋቋሙበት አለማ ዉጪ የሚንቀሳቀሱ ድርጅቶች እንደነበሩ የፍትሕ ሚንስቴር ዘገባ ዋቢ ያደርገዋል።የክርስቲያናዊ የልማት በጎ አድራጎት ድርጅት ተጠሪም ችግሩ እንደነበረ አይክዱም።ግን አንደኛ ጎልቶ የወጣ አልነበረም።ይላሉ።ሁለተኛ እነዚያን ወገኖች ለመቆጣጠር ወትሮም ይቻል ነበር።ሰወስት፣- አቶ ብርሐኑ በዙ ይቀጥላሉ።

ሕጉ ከመዉጣቱ በፊት ተመዝግበዉ የነበሩት ድርጅቶች 3 522 ነበሩ።ሕጉ ከፀደቀ በሕዋላ የተመዘገቡት ግን አንድ ሺሕ ስድስት መቶ ሐምሳ አምስት ናቸዉ።ከነዚሕ መሐል 218ቱ ስማቸዉን፥ አስራ-ሰባቱ አላማቸዉን ቀይረዋል።

ነጋሽ መሐመድ

ሒሩት መለሰ