1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

አሜሪካና የማጣሪያው የምርጫ ዘመቻ፧

ሰኞ፣ ታኅሣሥ 28 2000

አዪዋ በተባለችው ፌደራል ክፍለ-ሀገር የተጀመረው የማጣሪያ ምርጫ፧ አሜሪካውያንን፧ ዴሞክራቶችንም ሆነ ሪፓብሊካውያኑን አስደምሟል። እርግጥ ነው፧ አዪዋ ያን ያህል የመለኪያውን ውጤት አንጸባራቂ እንዳልሆነች ነው የሚነገርላት፧

https://p.dw.com/p/E87G
«ሴናተር« ባራክ ኦባማ፧
«ሴናተር« ባራክ ኦባማ፧ምስል AP Photo
ነገ፧ በ New Hampshireየሚካሄደው ተመሳሳይ የማጣሪያ የምርጫ ዘመቻ፧ የትኞቹ ተወዳዳሪዎች በህዝብ ዘንድ የላቀ ተፈላጊነት እንዳላቸው ይበልጥ ያመላክታል ተብሎ ይታሰባል። ካርስተን ሽሚስተር የላከውን ዘገባ፧ ተክሌ የኋላ እንደሚከተለው አጠናቅሮታል።
(ድምፅ) I believe in the young people of America...
«ምንም እንኳ ሁሉም አይሳተፉም እያለ ይናገር እንደነበረ ቢታወቅም፧ በወጣት አሜሪካውያን እተማመናለሁ።«
ይህን ያሉት ለዴሞክራቱ ፓርቲ እጩ ተወዳዳሪ ፕሬዚዳንት ሆኖ ለመቅረብ የዘመቻው ተከፋይ ከሆኑት አንዱ ሴናተር ባራክ ኦባማ ናቸው። አዪዋ ፌደራል ክፍለ-ሀገር ውስጥ፧ የማንኛውም ፓርቲ ደጋፊዎች ያልነበሩትን በሺ የሚቆጠሩ አሜሪካውያን ዜጎች በዲስኩራቸው አግባብተው የእርሳቸው ደጋፊዎች እንዲሆኑ ማብቃታቸውና በራሳቸው ፓርቲ ውስጥ የቅርብ ተፎካካሪያቸው የሆኑትን ሂለሪ ክሊንተንን ለማሸነፍ መብቃታቸው አስደማሚ ውጤት ተብሏል። ኦባማ፧ ነገም በንው ሃምፕሸር በተመሳሳይ ሁኔታ እንደሚቀናቸው ነው ተስፋ ያደረጉት። የ 46 ዓመቱ የ Illinois ፌደራል ክፍለ-ሀገር ተወካይ ሴናተር ኦባማ፧ የንግግር ተሰጥዖ ያላቸው የፖለቲካ ሰው ሲሆኑ፧ ለወጣቶች፧ ጎልማሶችና አዛውንት፧ ለሁሉም የዲስኩርቸው ዐቢይ ርእስ የለውጥን አስፈላጊነት የሚያስገነዝብ ነው። የእርሳቸው ፓርቲ አባል ሆኖም ለእጩነት የሚፎካከሩአቸው የቀድሞው የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ቢል ክሊንተን ባልተቤት ሴናተር ሮድሃም ሂለሪ ክሊንተን በነገው የንው ሃምፕሸር የህዝብ ዝብባሌ መለኪያ ምርጫ አሸንፋለሁ ብለው ቢነሱም፧ የአዪዋው ውጤት መጥፎ ገድ እንዳይሆን ሥጋት ሳያድርባቸው አልቀረም። ስለ አዪዋው ምርጫ እንዲህ ነበረ ያሉት፧
«ዕድሜአቸው ከ 45 ዓመት በላይ የሆኑትን ለማግባባት በጣሙን ተሳክቶልኛል። ከ 30 ዓመት በታች ዕድሜ ያላቸውን ግን፧ ደጋፊዎቼ ለማድረግ፧ አልሆነልኝም። ለዚህም ኀላፊነቱን ራሴ እቀበላለሁ።«
በሴናተርነት ካላቸው የሥራ ልምድ፧ ቀድሞም የኋይት ቤተመንግሥት ተቀዳሚ እመቤት በመሆን ካካበቱት የፖለቲካ ልምድ በመነሣት፧ ወጣቱን ትውልድ ለማማለል እንደሚባለው፧ በአዲስ ሥልት መጣራቸው አይቀሬ ነው። ስለዚህም ሲናገሩ፧
«ለፕሬዚዳንትነት በመወዳደር፧ የወደፊቱን መጻዔ ዕድል የፖለቲካ እርፍ ለመጨበጥ እሻለሁ። መጪው ዘመንም በተለያየ የዕድሜ እርከን ለምንገኝ አሜሪካውያን ሁሉ፧ በተለይ ለወጣት አሜሪካውያን እንዲሠምር ነው የምጥረው«
በንው ሃምፕሸር የሁለቱ ዴሞክራት ፖለቲከኞች ዕድል እስከምን ድረስ እንደሆነ ከ NBC የቴሌቭዥን ድርጅት የዜና ክፍል የተሰነዘረው ግምገማ፧ 45% መራጮች፧ ነጻ መሆናቸውን፧ ይህም ለኦባማ ማለፊያ አጋጣሚ መሆኑን በሌላ በኩል፧ የተጠቀሰው ፌደራል ክፍለ-ሀገር፧ ከዚህ ቀደም ሴት አስተዳዳሪ እንደነበረችው ብዙዎች ሴቶች በመንግሥት መሥሪያ ቤቶች እንደሚገኙ፧ ይህ ደግሞ ለሂለሪ ክሊንተን አመቺ ሁኔታን እንደሚፈጥር ነው የተነበየው!። ከአዪዋ ይልቅ ጥቂት ወግ አጥባቂ ክርስቲያኖች የሚገኙበት ክፍለ-ሀገር፧ ከሪፓብሊካውያን ያልተጠበቀ ውጤት ላስመዘገቡት ለቀድሞው ሰባኪ ቄስ Mike Huckabee መጥፎ ነው። ስለዚህ የንው ሃምፕሸር ውድድር፧ የቀድሞውን የማሳቹሰትስ አስተዳዳሪ Mitt Romney ንና ሴናተር John McCain ን ይሆናል የሚያሳትፈው።
ከ “Wall Street Journal” John Harwood ......ተወዳዳሪዎቹንና ሂደቱን አስመልክተው ሲያጠቃላሉ እንዲህ ብለዋል።
«ዋናዋዎቹ እጩ ተወዳዳሪዎች ለእጩነት ለመሰየም በሚያበቃ ጎዳና ላይ ናቸው። ፈተናዎቹ በአንዱም ሆነ በሌላው ተወዳዳሪዎቹን አተናክረዋቸዋል። ሆኖም በአሁኑ ወቅት፧ በሁሉም ግዛቶች አብዝሃ ድምፅ ለማግኘት ተስፋ ሊያደርግ የሚችል የለም።