1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ኑክሌር፣ኢራንና የአሜሪካ የስለላ ውጤት

ረቡዕ፣ ኅዳር 25 2000

ከአሜሪካ የስለላ ቢሮ የተሰራጨው አዲስ መረጃ መላውን ዓለም ያስደምም ይዟል።የዩናይትድ ስቴትስ መንግስት ኢራን ተያይዛ ለነበረው አደገኛ መንገድ መፍትሄ ይሆን ዘንድ የጦርነት ንድፍ ሁሉ አሰናድቶ ነበር።

https://p.dw.com/p/E87R
የኑክሌር መርሀ-ግብር በኢራን
የኑክሌር መርሀ-ግብር በኢራንምስል AP

አሁን እውነታው ሌላ ሆኖ ተገኝቷል።አስራሰባቱም የአሜሪካ የስለላ አባላት በአንድ ድምፅ ኢራን እ.ኤ.አ. ከሁለት ሺህ ሶስት ዓ.ም አንስቶ የአቶሚክ ቦንብ ባለቤት የሚያደርጋትን መርሀ ግብር ዘግታለች ሲሉ መስክረዋል።በሌላ አቅጣጫ ግን የአሜሪካን መንግስት ነገሩን በጎሪጥ ነው የተመለከተው።የኃይት ሀውስ ብሔራዊ የደህንነት አማካሪ የሆኑት ስቴፈን ሐድሌይ፤የጉዳዩ አሳሳቢነት አሁንም ድረስ እንዳለ ጠቁመዋል።

በእርግጥ ኢራን ዩራኒየም የማብላላት መርሀ-ግብሯ ለሠላማዊ መንገድ ከሆነ ልትቀጥልበት ትችላለች።እንደስለላ ውጤቱ መረጃ ከሆነ፤ኢራን ከአሁን በኃላ እ.ኤ.አ. እስከ ሁለት ሺህ ዘጠኝ ዓ.ም ድረስ የአቶሚክ ቦንብ ባለቤት ልትሆን የሚያስችል ስጋት የለም። ምናልባት እንኳን የአቶሚክ ቦንብ ባለቤት ልትሆን የምትችል ቢሆን እ.ኤ.አ. ከ ሁለት ሺህ አስራአምስት ዓ.ም በኃላ ቢሆን ነው ሲል አትቷል።የስለላ ውጤት መረጃውም አሁን ኢራን የኑክሊየር ባለቤት ሊያደርጋት የሚያስችል አቅም እንደሌላት ያለውን ተስፋ ገልጿል።

ያም ሆነ ይህ፤ላለፉት ሁለት ዓመታት የስለላ ድርጅቱ ኢራን ለዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ግፊት እጇን የምትሰጥ አይነት አይደለችም ሲል ቆይቶ፤አሁን ፍፁም የተለየ መረጃ ይዞ ብቅ ብሏል።ኢራን የአቶሚክ ቦንብ ባለቤት ሊያደርጋት ወደሚያስችል ደረጃ እየተሸጋገረች ነው የሚለውን የቀቀድሞ መረጃ ውድቅ አድርጎታል።ሆኖም በእርግጥ ኢራን የኑክሊየር ቦንብ ባለቤት ሊያደርጋት የሚያስችላትን መርሀ ግብር በድጋሚ ልትጀምር ትችል እንደሆነም ማንም አያውቅም።ስጋቱ በሌላ ጎኑ አሁንም ድረስ አለ ማለት ነው።የስለላ ውጤቱ መረጃ ይህ ስጋት ከሀይል ይልቅ በዲፕሎማሲያዊ ውይይት ሊፈታ እንደሚችል ያለውን ተስፋ ነው ያስቀመጠው።

በዚህም አለ በዚያ ግን አዲሱን መረጃ በተመለከተ የአሜሪካን መንግስት ሊጠየቅ የሚገባው ነገር አለ።ይህን የሚያህል ወሳኝ ጥያቄ ላይ ስለምን የአሜሪካን የስለላ ድርጅት ሊሳሳት ቻለ? በተመሳሳይም ጅምላ ጨራሽ መሳሪያ ይዛለች ሲል ኢራቅ ላይ ጣቱን ቀስሮ የነበረው ይህ የስለላ ድርጅት መሳሳቱ የሚታወቅ ነው።ሆኖም የአሜሪካ ብሔራዊ የደህንነት ሠራተኛ የሆኑት ስቴፈን ሐድሌይ ኢራን ዕቅዳቸውን በከፍተኛ ምስጢር ከሚያራምዱ አገራት አንዷ ናት ሲሉ ስጋታቸው አሁንም ድረስ እንዳለ ገልፀዋል።