ኃላፊነት ገና በልጅነት
ዓርብ፣ ጥር 20 2008
ልጃቸውን ተንከባክበው ፣ ፍቅር በተሞላው አያያዝ እና የራስ መተማመን እንዲኖረው አድርገው የሚያሳድጉ ወላጆች ልጃቸው ገና በሕፃንነት እድሜው ኃላፊነት ሲወስድ መታዘብ ይችላሉ።
ወጣት ሳለን መቼ አድጌ፣ ራሴ ለራሴ መወሰን ችዬ እንላለን። ትልቅ ሰው መባል/መሆን ግን ራሱን የቻለ ከባድ ኃላፊነት አለው። ምክንያቱም ማንም ሰው ለሚወስደው ርምጃው በሙሉ ተጠያቂ ነውና። ይህን ደግሞ ትልቅ ችግር አድርገው እንደሚመለከቱት አንዳንድ ሰዎች ይናገራሉ። እነዚህ ሰዎች እንደሚሉት፣ ኃላፊነት መውሰድን ከጥሩ ጎኑ ሳይሆን ፣ አደገኛ ሊሆን ከሚችልበት ጎኑ ነው የሚመለከቱት።
ለራሱ እና ለሌሎች ኃላፊነት የሚወስድ ትውልድ ማፍራት፤ የሁሉም ሀገር ምኞት ነው። ለረዥም ጊዜ የተደረጉ ስነ ልቦናዊ ጥናቶች እንደሚያመላክቱት፣ የሰው ልጅ ገና በዘጠኝ ወሩ በአዎቂዎች ዘንድ ተደማጭነት የሚያገኝበትን ፀባይ ማዳበር ይጀምራል። የአንድ ሰው ኃላፊነት የመውሰድ ችሎታ የሚዳብረው ደግሞ በአካባቢው እንደሚያደርገው ተሞክሮ ይለያያል።
ከዚህም በተጨማሪ አንድ ሰው የሚወስደው ኃላፊነት ከእድሜው ጋር የተመጣጠነ መሆን እንዳለበት ባለሙያዎች ይገልፃሉ። አንድ ሕ ፃን ያለበትን ኃላፊነት ሳይከብደው እንዴት ሊወጣ ይችላል? ለዚህ ጥያቄ መልሱ በተናጥል የሚመለስ ነው። ምክንያቱም የአንድ ልጅ ኃላፊነት እድሜው እና ለሚሰጠው ኃላፊነት የሚኖረው ፍላጎት ይወስነዋል። ለምሳሌ አንድ ከልጅነቱ ጀምሮ በግ የሚወድ ልጅ ፤ እድሜ ው ከፍ ሲል በግ እንዲጠብቅ ቢታዘዝ ፤ ጨርሶ እንስሳ ከማይወደው ልጅ የበለጠ ኃላፊነቱን በአግባቡ ሊወጣ ይችላል። የዛሬው የወጣቶች ዓለም እንግዳ ኤልያስ አዳሙ ይባላል። የ15 ዓመት ወጣት ነው። ኃላፊነትን መውሰድ ገና በሕፃንነቱ ነው የጀመረው።የስራው አይነት እና ክብደት ይለያይ እንጂ ገና ከልጅነት አንስቶ ስራ ሰርቶ ማደግ፤ ለበርካታ ኢትዮጵያውያን ልጆች አዲስ ነገር ላይሆን ይችላል። ኤሊያስ ስለ ዕለት ከዕለት ህይወቱ ገልጾ በጻፈልን ደብዳቤ ላይ ለዶይቸ ቬለ ለመፃፍ ያነሳሳው ለኢትዮጵያውያን ወጣት ተማሪዎች መግለፅ የምፈልገው ቁም ነገር ስላለ ነው ብሎናል። ከወጣቱ ጋር የነበረንን ቆይታ በድምፅ ያገኙታል።
ልደት አበበ
አርያም ተክሌ