ትኩረት የሚሻዉ የሴቶች መብት
ማክሰኞ፣ ኅዳር 18 2005የተመ የልማት መርሃግብር UNDP አፍጋኒስታን ዉስጥ ሴቶች በዝምታና በጽናት የተሸከሙት ስቃይ እስካሁን ምንም እንዳልተባለለት ነዉ የሚገልፀዉ። የድርጅቱ ባልደረባ ሻርሚስታ ዳስባርዋ ሴቶች ላይ የሚፈፀም ጥቃት እልባት እንዲያገኝ ባለፈዉ እሁድ የታሰበዉን ዓለም ዓቀፍ ቀን አስታከዉ በሰጡት መግለጫ ጦርነትና ግጭት ባልተለያት ምድር የሚኖሩት ሴቶች አካላዊና ስነልቦናዊ ጥቃቱ እየደረሰባቸዉም አንድቀን ከዚህ እንገላገላለን በሚል ተስፋ በፅናት ህይወታቸዉን እንደሚገፉ አመልክተዋል። እሳቸዉ እንደሚሉት የአፍጋኒስታን ሴቶች ዝምታ ላለፉት ዓመታት ከሲኦል የሚነፃፀር ስቃይ ዉስጥ አቆይቷቸዋል።
እንደእሳቸዉ አገላለፅም በሌሎች ሀገሮችም ሴቶች ላይ ጥቃት መፈፀማቸዉ እሙን ቢሆንም የአፍጋኒስታን ሴቶች የሚፈፀሙባቸዉ ጥቃቶች ግን ቀጣይነት ያላቸዉ በመሆናቸዉ ሴቶቹ የድረሱልኝ ርዳታ እንኳ እንዳይማፀኑ አሸማቆ አንገት የሚያስደፋ ነዉ። እንዲህም ሆኖ ይላሉ በተለያዩ ሀገሮች በተመሳሳይ ተግባር ተሰማርተዉ ያስተዋሉት ህንዳዊቱ የUNDP ባልደረባ የአፍጋኒስታን ሴቶች በዓላማቸዉ ፅኑና ያመኑበትን ከግብ ለማድረስ የማይታክቱ ናቸዉ። በዚህ ምክንያትም ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ ለዉጦች መታየት ጀምረዋል፤ ምክር ቤት ዉስጥ 27 በመቶዎቹ ሴቶች ናቸዉ፤ በሰላም ማስፈኑን በሽግግሩ ሂደትም ሴቶች መሳተፋቸዉ ለኅብረተሰቡ ህልዉና ወሳኝ መሆኑን የሚያምኑ አሉ። ችግሩ ግን ፅንፈኛ አመለካከትን የያዙት ኃይሎች አድብተዉ ከጀመሩት ጉዞ እንዳይገቷቸዉ ነዉ።
ሸዋዬ ለገሠ
ተክሌ የኋላ