ብሪታንያዊ ከያኒ ዴቪድ ቦዊ ከዚህ ዓለም በሞት ተለየ
ሰኞ፣ ጥር 2 2008ማስታወቂያ
ዲቪድ ለወራቶች በጉበት ካንሰር እደተሰቃየም ተመልክቶአል። ዴቪድ ቦዊ በተወለደበት ስፍራ በብሪታንያ ብሪክስቶን ዛሬ ከፍተኛ የመታሰቢያ ሥርዓት ተካሂዶአል። በሥርዓቱ ላይም አድናቂዎቹ የሮክ አቀንቃኙ አብዛኞቹን የዘርፉን ባለሙያዎች ከአማተርነት ወደአርቲስትነት የለወጠ እንደሆነ ተናግረዉለታል። በጎርጎሪዮሳዊዉ 1947ዓ,ም ጥር ወር በለንደን ብሪክስቶን የተወለደዉ ዴቪድ ቦዊ ጆንስ፤ የሙዚቃ ባለሙያ፤ ዘፋኝ፤ አዘጋጅ፤ የፊልም ተዋናይ እና ሰዓሊ ነበር።
ዴቪድ ቦዊ 140 ሚሊየን የሚሆኑ የሙዚቃ ቅጂዎቹን በመላዉ ዓለም የሸጠ ሲሆን በተለይ እጅግ ተወዳጅ የሆነበት «ሌትስ ዳንስ» የተሰኘዉ የሙዚቃ አልበሙ ሰባት ሚሊየን ቅጂ መሸጡ ተመዝግቦአል። በጀርመናዉያን ዘንድ ተወዳጅ የሆነዉ ከያኒ ዴቪድ ቦዊ ፤ ለሁለት ዓመታት በጀርመን እንደኖረም ተነግሮአል።
ዴቪድ ቦዊ በሙዚቃ ሥራዎቹ ለበርካታ ወጣት የሙዚቃ ባለሙያዎች በአርአያ የሚጠቀስ ሲሆን ላለፉት 18 ወራት ለአድናቂዎቹ ይፋ ሳያደርግ በጉበት ካንሰር ሲሰቃይ ቆይቶአል። እንግሊዛዊዉ ታዋቂና ተወዳጅ ዴቪድ ቦዊ በሕይወት ቢቆይ ኖሮ የፊታችን ዓርብ የ69ኛ የትዉልድ ቀኑን ያስብ ነበር። ዴቪድ የአንድ ሴትና የአንድ ወንድ ልጅ አባትም ነበር።
አዜብ ታደሰ
ሂሩት መለሰ