ባግዳድ፤በአይሲስ የቦምብ ጥቃት 120 ሰዎች ተገደሉ
ቅዳሜ፣ ሐምሌ 11 2007ማስታወቂያ
ከኢራቅ ዋና ከተማ 35 ኪ.ሜትር ርቀት ላይ በምትገኘውና የሺዓ እስልምና ተከታዮች በሚኖሩባት የካን ባኒ ሳድ ከተማ በመኪና ላይ የተጫነው ቦምብ የረመዳን ቅዱስ ወርን መጠናቀቅ በማስመልከት የተሰበሰቡ ሰዎችን ዒላማ ማድረጉን የአገሪቱ ፖሊስ አስታውቋል። ከሟቾች መካከል ሴት እና ህጻናት ይገኙበታል።
ራሱን እስላማዊ መንግስት በማለት የሚጠራው አክራሪ ቡድን ለጥቃቱ ሃላፊነቱን ወስዷል። የዒድ በዓልን ለማክበር ወደ ገበያ የወጡ ሰዎች በዘንቢሎቻቸው በፍንዳታው የተበታተኑ የህጻናት አካላትን ሲለቃቅሙ መታየታቸውን ሮይተርስ ዘግቧል። አደጋው ታጣቂ ቡድኑ በኢራቅ ከፈጸማቸው ሁሉ የከፋ ነው ተብሎለታል።ከጥቃቱ በኋላ የአገሪቱ ፖሊስ የጸጥታ ቁጥጥሩን አጥብቋል።
በተያያዘ ዜና አይሲስ የአካባቢውን ባለስልጣናትና የስራ ባልደረቦቹን ይሰልላል ያለውን አንድ ጋዜጠኛ በሞስል ከተማ መግደሉን አዣንስ ፍራንስ ፕሬስ ዘግቧል። ጃላል አል አባዲ የተባለው ጋዜጠኛ ከቤቱ ተወስዶ በአክራሪ ቡድኑ ችሎት ሞት ከተበየነበት በኋላ ባለፈው ረቡዕ በጥይት ተደብድቦ ተገድሏል። በኢራቅና ሶርያ በእስልምና ህግጋት የሚተዳደር ግዛት መስርቻለሁ የሚለው አክራሪ ቡድን የሁለት ልጆች አባት የሆነውን ጃላል አል አባዲን ጨምሮ በርካታ ጋዜጠኞች መግደሉ ይነገራል።
እሸቴ በቀለ
ልደት አበበ