1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

በፍርሃት የታጠረ ነፃነት

ማክሰኞ፣ ነሐሴ 3 2003

የመስከረም 1 ,1994 ዓ.ምህረቱን የኒውዮርኩን የአሸባሪዎች አደጋ ዜና አኬል ኢብራሂም ላዚም የሰማው በሰርጉ ዝግጅት መካከል ነበር ።

https://p.dw.com/p/RcOs
ኢብራሂም ላዚምምስል DW

የያኔው የዩኒቨርስቲ ምሩቅ የዛሬው የጥርስ ሃኪም አኬል ከእጮኛው ጋር ስለ ሠርጉ ስነ ስርዓት በመመካር ላይ ባለበት ክፍል ውስጥ ነበር በእሳት የሚነዱትን የኒውዮርክ መንትያ ህንፃዎች በአደጋው የሞቱ ሰዎችን የሚያሳዩ አሰቃቂ ምስሎችን በቴሌቪዥን የተመለከተው ። እርሱ ካለበት በብዙ ርቀት ላይ የምትገኘው አደጋው የደረሰባት ዩናይትድ ስቴትስ በአገሩ በኢራቅ ይፋ ፕሮፖጋንዳ እንደ ጠላት ኃይል የምትፈረጅት ሀገር ናት ። ያኔ ነበር አኬል የሚያየው በሳዳም ሁሴን ቁጥጥር ስር ካለው የመንግሥት ቴሌቪዥን ጣቢያ የሚተለለፍ አሰቃቂ ፊልም ሳይሆን በውኑ ዓለም የደረሰ አደጋ መሆኑን የተገነዘበው ።

Irak 9/11 Flash-Galerie
ምስል DW

የዓለም መጨረሻ መስሎኝ ነበር

« በዚያ ቅፅበት የተሰማኝን ለመግለፅ በጣም ይከብደኛል » ይላል ላዚም ከ10 ዓመት በኃላ « ፍርሃት ሃዘንና ድንጋጤ የተቀላቀለበት ስሜት ነበር ፤ የዓለም መጨረሻ ነበር የመሰለኝ ፣ የሰው ልጅ ሥልጣኔ መሉ በሙሉ የወደምም ያህል ነበር የተሰማኝ ። » ሲል ነበር በወቅቱ የተሰማውን የገለፀው ።ለ 35 ዓመቱ ላዚም የአሜሪካኑ የሽብር ጥቃት በሰርጉ ላይ ጥላ ስለ ማጥላቱ ፣ በሀገሩ በኢራቅ ላይ ሌላ ጦርነት ስለ ማስከተሉና ብሎም ለሀገሪቱ ፕሬዝዳንት ሳዳም ሁሴን ከሥልጣን የመውረድ ምክንያት ስለ መሆኑ ያኔ የጠረጠረው ነገር አልነበረም ። በውስጡ ንዴትም የደህንነት ዋስትና ማጣትም ተሰምቶታል ። « ጥቃት የደረሰባቸው ሰላማዊ ሰዎች ናቸው ። ማንም ሃዘኔታ ያለው ሰው የጥቃቱ ሰለባዎች የየትኛው ሃገር ዜጋ ናቸው ብሎ አይጠይቅም እናም እንደ ሰብዓዊ ፍጡር በአደጋው ሰለባዎች ላይ በደረሰው በጣም አዝኛለሁ ። ሆኖም ጥቃቱን የፈፀሙት ሙስሊሞች መሆናቸው ደግሞ ከወትሮው በተለየ የሚያሳዝን ስሜት ነው ያሳደረብኝ ። »

Bildergalerie Irak 9/11
ምስል DW

እርግጥ ነው የዚያን ዕለቱ የአልቄይዳ የሽብር ጥቃት በሃገሩ በኢራቅ ላይ መዘዝ ማስከተል አለማስከተል ስለመቻሉ የሚያውቀው አልነበረም ። ቢያንስ በማግስቱ ግን በኢራቅ መሪዎች ትልቅ የመሸበር መንፈስ እንደነበረ ተገንዝቧል ። ኢራቅ ራሷ የዚህን መሰል ጥቃት ዒላማ ውስጥ የገባች እስኪመስል ድረስ የፀጥታ ኃይሎችና የታጠቁ የገዥው የባዝ ፓርቲ አባላት በድንገት በየመንገዱ መታየት እንደጀመሩ ያስታውሳል ።

ዛሬ በባስራ ዩኒቨርስቲ የሚያስተምረውና አነስተኛ የግል የጥርስ ህክምና ክሊኒክ ባለቤት የሆነው ላዚም ያኔ የገጠመው ከጠበቀው የተለየ ነበር «ስለ ሰርጉ መወራቱ ቀርቶ የመነጋገሪያው ርዕስ ሌላ ሆነ ። እንኳን ደስ ያለህ ከሚሉት የመልካም ምኞት መግለጫዎች ይልቅ ሌሎች ዜናዎችን ነበር የምሰማው ። » በወቅቱ የኢራቅ መንግሥት ሳዳም ሁሴንን የሚያወድስ ሰልፍ አደራጅቶ ነበር ። ያኔ ብዙ ህዝብ በግዳጅ እንዲወጣ መደረጉን ላዚም ያስታውሳል ። ላዚም እንደ አብዛኛዎቹ ሺአዎች የሱኒዎች ስብስብ የሆነው የሳዳም ሁሴን አገዛዝ ታቃዋሚ ነበር ።

Irak 9/11 Flash-Galerie
ምስል DW

ጦርነት የመቃረቡ ምልክቶች

የመስከረም አንዱ የሽብር ጥቃት ኢራቅን ወደ አዲስ ጦርነት ማስገባቱ እንደማይቀር ወዲያውኑ ግልፅ እየሆነ መጣ ። የዩናይትድ ስቴትስ መንግስት ሳዳም ሁሴንን በአውዳሚ የጦር መሣሪያዎች ባለቤትነት መወንጀል ጀመረ ። አገዛዙም ከአልቄይዳ ጋር ቀጥተኛ ግንኙነት እንዳለው ተነገረ ። ሁለቱም ውንጀላዎች ግን ኋላ ላይ ሀሰት መሆናቸው ተረጋግጧል ። ይሁንና ላዚም እንደሚያስታውሰው እነዚህ ውንጀላዎች ለኢራቃውያን ግጭት እየተቃረበ የመሆኑ ግልፅ ምልክቶች ነበሩ ። በወቅቱ የያኔው የአሜሪካን ፕሬዝዳንት የተናገሩትንም አይረሳም ።

« ቡሽ ለዓለም መሪዎች በሙሉ ወይ ከኛ ጋር ናችሁ አለያም ከኛ በተቃራኒው ቆማችኋል ። ሲሉ ተናግረው ነበር ። የኛን መንግሥት አሜሪካንን በጠላትነት ነው የሚፈርጃት ። ምክንያቱም ኢራቅ ኩዌትን ስትወር ጦርነት ከፍታባት ነበርና ። »

አዲሱ ጦርነት እ.ጎ.አ መጋቢት 19 ,2003 ዓም ከከአንድ ዓመት ተኩል በኋላ ተጀመረ ። « እኔ የማውቃቸው በርካታ ኢራቃውያን ሀገራቸው መወረሯን ተቃውመዋል ። የዚያኑ ያህል ደግሞ ሁላችንም ሳዳም ሁሴን ከሥልጣን እንዲወርዱ እንመኝ ነበር ።»

ይኽው ምኞታቸውም ከ 22 ቀናት በኋላ እውን ሆኖ በርካታ ዜጎችን አስፈነደቀ ። ደስታው ግን ሙሉ አልነበረም ።

« በመጨረሻ ከአገዛዙ ተላቀቅን ። ይሁንና በከተሞቻችን ወራሪ ወታደሮችን ማየታችን አሳዛኝ ስሜት አሳድሮብናል ። »

የሳዳም ሁሴን መውረድ ለላዚም እና ለሃገሩ ሰዎች ከዚህ ቀደም አይተዉት ያማያውቁትን ነፃነት አጎናፀፋቸው ። « የሚታመን አልነበረም ፤ በድንገት ሰዉ ሃሳቡን በነፃነት መግለፅ ቻለ ። » ለላዚም በሙያውም በኩል ቢሆን በግሉ ጥሩ ይዞታ ላይ ነበር ። የግል የጥርስ ህክምና ክሊኒክ ከፈተ ። በሳዳም ሁሴን አገዛዝ ዘመን ቢሆን ይህ የሚታሰብ አልነበረም ።

ቀውስ የገጠማት ሃገር ።

ይሁንና ለአዲሱ ነፃነት የተከፈለው ዋጋ ግን ከፍተኛ እና ደም ያፋሰሰም ነበር ። ሃገሪቱ ለዓመታት በቀውስ በግጭቶችና በሽብር ውስጥ ወደቀች ። ሲኒዎችና ሺአዎች ጎራ ለይተው እርስ በርስ ተጫራረሱ ። ማንም ከጥቃት እና ከመታገት የመዳን ዋስትና አልነበረውም ። « ይህ ግን ተስፋ ያደረግነው የነፃነት ዓይነት አልነበረም ። ፍፁም ህግ አልባነት የሰፈነበት ነፃነት ነበር ። » ይላል ላዚም ። በዚያን ወቅት በ 10 ሺህዎች የሚቆጠሩ ኢራቃውያን ተገድለዋል ። በመካከሉ ግን ሁኔታው ተሻሽሏል ። ያም ሆኖ የጥቃት ሰለባ ያልሆነ የቤተሰብ አባል የሌለው አንድም ኢራቃዊ የለም ።

Irak 9/11 Flash-Galerie
ምስል DW

ላዚም ራሱ በሽብሩ ወቅት በ 2006 ታፍኖ የተወሰደውን የአጎቱን ልጅ ሞሀመድን አጥቷል ። ያኔ ቤተሰቡ በሆስፒታሎች በፖሊስ ጣቢያ አስከሬን ተገኘ በተባለበት ስፍራ ሁሉ ሞሀመድን ፈልገውታል ። ላዚህም በነዚህ ስፍራዎች የተገኘበትን ወቅት በአስከፊነቱ ነው የሚያስታውሰው « ክፍሎቹ በአስከሬኖች ተሞልተዋል ። በድንጋጤ እነዚህ ሁሉ ሰዎች ለምን ተገደሉ ? ብዬ ራሴን ጠየቅኩ ። በየቦታው ያሉት አስከሬኖች ይሸታሉ ። ሃላፊዎቹ አዳዲስ ማቀዝቀዣዎችን መግዛት የሚችሉበት ሁኔታ ላይ አልነበሩም ። »የላዚም የአጎት ልጅ አስከሬን ባይገኝም ኋላ ላይ ግን መሞቱ ተነገረ ።

ላዚም እ.ጎ.አ መስከረም 11 ,2001 የደረሰውን የሽብር ጥቃት ምስል ዛሬ ሲያይ ሽብር ከጥቃት የተረፉትን ሰዎች ምን ያህል በሃዘን እንዲሚያቆራምድ ያስታውሳል ። ኢራቅ ውስጥ ምንም የማያውቁ ህፃናት በጦርነት በአመፅ እና በሽብር መካከል ተወልደዋል ። « ሁላችንም ችግሩን ቀምሰናል ። በልባችን ውስጥ ትልቅ ፍርሃት ሰፍኗል ። የመታፈን ፍርሃት ፤ የመገደል ፍርሃት ፤ ብዙ ሰው የሚፈጀው በመኪና ውስጥ የጠመደ ቦምብ ፍንዳታ ፍርሃት ።» ላዚም በዚህ ምክንያት ሁለቱን ልጆቹን ሳራንና ሞሀመድን ዛሬም ለደህንነታቸው ሲል በየቀኑ ጠዋት ትምሕርት ቤት ያደርሳቸዋል ።

ሙናፍ አል ሳይዲ

ሂሩት መለሰ