1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

በውጭ የሚኖሩ ዜጎች የሚልኩት ገንዘብ መጨመሩ

ሐሙስ፣ ጥቅምት 25 2008

በውጭ ከሚኖሩ ዜጎች፣ ወደ ኢትዮጵያና ኬንያ የሚላከው ገንዘብ መጠን እያደገ በመሄድ ላይ መሆኑ ተገለፀ። በዚህ መንገድ ወደ ሁለቱ ሃገራት የሚገባው የውጭ ምንዛሬ ከሰሃራ በስተደቡብ ከሚገኙ የአፍሪቃ ሃገራት ጋር በንፅፅር ሲታይ ከፍተኛ መሆኑን የዓለም ባንክ አስታውቋል።

https://p.dw.com/p/1H0Ic
Kuba, Havanna Western Union Büro
ምስል picture-alliance/dpa

[No title]

በዓለም ባንክ መረጃ መሠረት፣ በውጭ ከሚኖሩ ዜጎች ወደ ኢትዮጵያና ኬንያ የሚገባው ገንዘብ ከሰሃራ በታች ከሚገኙ ሌሎች ሃገሮች ጋር ሲነፃፀር እየጨመረ ነው። በውጭ ከሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ወደ ሀገር ቤት የሚላከው ገንዘብ መጠን ባለፉት ዓመታት ማደጉን የዓለም ባንክ ያወጣው አንድ አዲስ መረጃ አስታውቋል። በዚሁ መረጃ እንደተጠቀሰው በሚቀጥሉት 3 ዓመታትም በዉጭ የሚኖረዉ ዜጋ ወደ ሀገር ቤት የሚልከው ገንዘብ በ50 በመቶ ያድጋል ተብሎ ይጠበቃል። ወደ ኢትዮጵያ የሚላከው የውጭ ምንዛሪ እያደገ መሄዱ ለሀገሪቱ ከፍተኛ ጠቀሜታ እንደሚያስገኝ የኤኮኖሚ ባለሞያዎች ያስረዳሉ። ብሩክ አብዱ በኤኮኖሚ እና ፋይናንስ ጉዳዮች ላይ በሚዘግበው ፎርቹን ጋዜጣ ሪፖርተር ነው። ብሩክ በዉጭ ሀገር ከሚኖረዉ ዜጋ የሚላከው ገንዘብ ኢትዮጵያ የሚያስፈልጋት አንዱ የውጭ ምንዛሪ ምንጭ ነው ይላል።

የኬንያ ማዕከላዊ ባንክ እንዳስታወቀው፣ እስካለፈው ነሐሴ ድረስ በዉጭ ሀገር ከሚኖሩ ኬንያዉያን የገባው ገንዘብ ከዓመት በፊት በዚሁ ጊዜ ውስጥ ከተላከው በ9 በመቶ አድጓል። ከአንድ ዓመት በፊት ማለትም በጎርጎሮሳዊው 2014 1 ሚሊዮን ዶላር ነበር በውጭ ከሚኖረው ኬንያዊ ወደሀገር ቤት የተላከው ገንዘብ። ዘንድሮ በተመሳሳይ ጊዜ ግን ከአምናው በ9 በመቶ ጨምሮ 1.5 ሚሊዮን ዶላር ደርሷል።

Symbolbild Geld Geldscheine Dollar Yen Euro und Britische Pfund
ምስል ullstein bild - Schöning

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ እንዳስታወቀው ደግሞ ዉጭ ከሚኖሩ ኢትዮጵያዉያን የተላከው ገንዘብ መጠን ዘንድሮ ከ1.5 ቢሊዮን ዶላር በልጧል። ይህ ማለት ከአምናው በ88 በመቶ እምርታ አሳይቷል። የዓለም ባንክም ሆነ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ የገለጹት ይህ ገንዘብ በባንኮችና በሌሎች የገንዘብ ማስተላለፊያ ተቋማት በኩል ወደ ኢትዮጵያ የሚገባ ነው። ይሁንና ጋዜጠኛ ብሩክ እንደሚለው በሌሎች መንገዶችም ወደ ሀገር ውስጥ የሚገባው የውጭ ምንዛሪ መጠን ከዚህ የሚተናነስ አይደለም። በብሩክ አስተያየት ከውጭ የሚላከው ገንዘብ ማደጉ የውጭ ምንዛሪ እጥረትን ለመቀነስ ጠቃሚ ነው። ሆኖም ይበልጥ አስተማማኙ የውጭ ምንዛሪ ምንጭ፣ የውጭ ንግድ ነው ።

ኂሩት መለሰ

ሸዋዬ ለገሠ