1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

በውጥረት የተዋጠችው ሶሪያ

ረቡዕ፣ የካቲት 21 2004

የሶሪያው ዓመፅ አመት ሊሞላው እየተጠጋ ነው። የሐገሪቱ ፕሬዚዳንት ባሽር አል አሳድ የፀጥታ ሀይላት በዲሞክራሲ አቀንቃኝ ሰልፈኞች ላይ በከፈቱት ተኩስ እስካሁን የተገደሉት ሰዎች ቁጥር ቢያንስ 6 ሺህ እንደሚደርስ ተገልጿል።

https://p.dw.com/p/146GK
ምስል Reuters

የሶሪያው ዓመፅ አመት ሊሞላው እየተጠጋ ነው። የሐገሪቱ ፕሬዚዳንት ባሽር አል አሳድ የፀጥታ ሀይላት በዲሞክራሲ አቀንቃኝ ሰልፈኞች ላይ በከፈቱት ተኩስ እስካሁን የተገደሉት ሰዎች ቁጥር ቢያንስ 6 ሺህ እንደሚደርስ ተገልጿል። የሶሪያው ዓመፅ ከተቀጣጠለ 11ኛ ወሩን እያገባደደ ነው። ሕዝቡ ሠልፍ ለማከናወን በየጊዜው ከአደባባይ ይሰየማል፤ የሶሪያ መንግስት ታጣቂዎችም ሳይታክቱ በሰልፈኛው ላይ ይተኩሳሉ። የዕለት ተዕለት ተግባር የመሰለው ይህ ሂደት ቀጥሎ በሶሪያ የፀጥታ ሀይላት የተገደሉት ሰዎች ቁጥር ቢያንስ 6 ሺህ መጠጋቱ ተነግሯል። በተለይ ሆምስ በተባለችው ከተማ ነፍጥ ያነገቡ ተቃዋሚዎች ከመንግስት ታጣቂዎች ጋር መፋጠጥ ከጀመሩ ወዲህ ውጥረቱ እያየለ ሄዷል። የአረብ ሊጋው ምክትል ዋና ፀሀፊ ናቢል አል አራቢ ተወካይ አልጄሪያዊው አህመድ ቤንሄሊ፣

Syrien Protest
ምስል picture-alliance/dpa

«በመጀመሪያ ከመንግስትም ከተቃዋሚዎችም በኩል የሀይል ተግባሩ ማብቃት አለበት። ከዚያም ፕሬዚዳንቱ ስልጣናቸውን ለተወካዩ የሚያስረክቡበት የሽግግር መንግስት ያስፈልጋል። ምርጫ ይደረጋል፣ ከዚያም አዲስ ህገ-መንግስት ይረቀቅና ለውጥ ይከናወናል።»

በሶሪያ ላይ መስማማት የተሳነው የተባበሩት መንግስታትን ጨምሮ፤ የተለያዩ ዓለም አቀፍ ተቋማት ለሀገሪቱ ይበጃል ያሉትን የመፍትሄ ሀሳብ ይዘው ቀርበዋል። «ጥርስ አልባው ነብር» እየተባለ የሚተቸው የአረብ መንግስታቱ ድርጅት በበኩሉ በሶሪያ ለተከሰተው ቀውስ አፋጣኝ መፍትሄ ማግኘት የተሳነው ይመስላል። ለዚህ ደግሞ ይላሉ፤ አልጀሪያዊው አህመድ ቤንሄሊ፣

Syrien Panzer Patrouille
ምስል dapd

የሶሪያው ዓመፅ አመት ሊሞላው እየተጠጋ ነው። የሐገሪቱ ፕሬዚዳንት ባሽር አል አሳድ የፀጥታ ሀይላት በዲሞክራሲ አቀንቃኝ ሰልፈኞች ላይ በከፈቱት ተኩስ እስካሁን የተገደሉት ሰዎች ቁጥር ቢያንስ 6 ሺህ እንደሚደርስ ተገልጿል። «አየህ እያንዳንዱ የአረብ መንግስት የተለያየ ደረጃ ነው ያለው። እናም የአረብ ሊጋው የተዋቀረው ከነዚህ ደረጃዎች አንፃር ነው። ያም በመሆኑ ሁሌም በተለያየ መልኩ ነው አፀፌታው።»

በሶሪያ ጉዳይ የተለያየ አቋም የያዙት ሃያላኑ ሀገራት ጭምር ናቸው። የፀጥታው ምክር ቤት በሶሪያ መንግስት የሚፈፀመውን የሀይል ተግባር አውግዞ ያቀረበውን የመፍትሄ ሀሳብ ቻይና እና ሩሲያ በተደጋጋሚ ውድቅ ማድረጋቸው አይዘነጋም። ትናንት የሩሲያ የዓለም አቀፍ ጉዳዮች ባለስልጣን የሆኑት አሌክስ ፑሽኮቭ ዳማስቆስ ተገኝተው የሶሪያው ፕሬዚዳንት ባሽር አል አሳድን አነጋግረዋል። አሳድ የሩሲያውን ባለስልጣን አመስግነው፤ የውጭ ሀይላት «የታጠቁ አሸባሪ ቡድናትን» እያደራጁ ነው ሲሉ ኮንነዋል። የዩ ኤስ አሜሪካ ወታደራዊ ባለስልጣን በበኩላቸው በሶሪያ ጉዳይ ጣልቃ መግባት «በጣም አስቸጋሪ ይሆናል» ብለዋል።

Syrien Protest
ምስል picture-alliance/dpa

የቻይናው ሕዝባዊ ዕለታዊ ጋዜጣ የምዕራቡ ዓለም የሶሪያ ተቃዋሚዎችን መደገፉ ግጭት ባዳቀቃት ሶሪያ ውስጥ የርስ በርስ ጦርነትን ሊያጭር ይችላል ሲል ስጋቱን ገልጿል። ከትናንት በስተያ ሁለት የኢራን የጦር መርከቦች ለሶሪያ የባህር ሀይል ስልጠና ለመስጠት መልህቃቸውን ታርቶስ በተባለችው የሶሪያ ወደብ መጣላቸው ተዘግቧል። «የሶሪያ ወዳጆች ቡድን» የተሰኘ አካል ደግሞ የፊታችን አርብ ቱኒዚያ ዋና ከተማ ቱኒስ ውስጥ እንደሚሰበሰብ ተዘግቧል። በስብሰባው ዩ ኤስ አሜሪካ፣ የአረብ ሊጋው፣ የአውሮጳ ኅብረት ልኡካናት እና የሶሪያ ተቃዋሚዎች እንደሚገኙ ከወዲሁ ተገልጿል።

ማንተጋፍቶት ስለሺ

አርያም ተክሌ