1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

በአፍጋኒስታን፣ የጀርመን ጦር ሠራዊት ተልእኮ መራዘም፣

ሐሙስ፣ ኅዳር 17 2002

የጀርመን የህዝብ እንደራሴዎች ም/ቤት(ቡንደስታግ) በዛሬው ዕለት ከተከራከረ በኋላ፣ አፍጋኒስታን ውስጥ ጸጥታ ለማስከበርና አገሪቱን መልሶ ግንባታ በዚያ እንደተሠማራ የሚገኘው የመከለካያ ሠራዊቱ(ቡንደስቬር) ተልእኮ፣ በአንድ ዓመት እንዲራዘም ወስኗል ።

https://p.dw.com/p/Kh60
ቮልፍጋንግ ሽናይደርሃንምስል AP

በሥልጣን ላይ ያለው ጥምር መንግሥትም ቀደም ሲል በሰጠው መግለጫ ላይ፣ የአፍጋኒስታን መንግሥት፣ እርምጃዎችን አሳይቷል ቢባልም እንኳ፣ ያገሩን ፀጥታ ለማስከበርና ህዝቡን ለማረጋጋት ገና አቅም አላገኘም የሚል ነው። በመሆኑም ዓለም አቀፍ የፀጥታ ረዳት ኃይል (ISAF) በመባል የታወቀው የምዕራባውያን መንግሥታት የተውጣጣ ጦር ኃይል ሥምሪት ፣ የጀርመን ጭምር፣ አሁንም አስፈላጊ ሆኖ ይገኛል።

አፍጋኒስታን ውስጥ፣ ታሊባኖች ከሥልጣን ከተባረሩ ከ 8 ዓመታት ወዲህም ቢሆን እስከዚህም ስኬታማ ተብሎ የሚነገርለት ተግባር እስካሁን አልተከናወነም። በደቡብም ሆነ፣ ጀርመናውያኑ በሚገኙበት በሰሜናዊው የአፍጋኒስታን ከፊል የመረጋጋት ምልክት አይታይም። ለአፍጋኒስታን በተመደበው፣ በዓለም አቀፉ የፀጥታ ረዳት ኃይል ውስጥ 4,500 ገደማ ጀርመናውያን ወታደሮች የተሠማሩ ሲሆን፣ አብዛኞቹ የሠፈሩት ፣ ማሳር ኢ-ሸሪፍ ላይ መሆኑ የታወቀ፣ ሲሆን ከአነዚህ መካካል ነው፣ አንድ ሺ ገደማ የሚሆኑት በቀጥታ በግዳጅ እንደተሠማሩ ናቸው። የኃይሉ እርምጃም በዚያ አካባቢ፣ ከጊዜ ወደ ጊዜ አስከፊ ገጽ ሆኗል የሚታይበት። በመሆኑም፣ ባለፈው የሰሜኑ ንፍቀ-ክበብ ሞቃት ወራት ኩንዱስ ላይ ስላጋጠመ ፣ በወታደራዊ አመለካከት፣ በቸልታ ሊታይ እንደማይገባ ስለሚነገርለት ተጻራሪ ኃይል አንድ የጦር አዛዥ የተናገሩትን እናስታውስ--

« ተጻራሪው ኃይል አሸምቆ የሚዋጋ ነው። ከበስተጀርባ ድንገት ከተፍ እያለ ነው የሚዋጋው። በማንኛውም ድክመታችን ሁሉ በመጠቀም ነው ለማጥቃት የሚጥረው። ድክመቶቹንም ጠንቅቆ ያውቃል። እንደ እርኩስ መንፈስ ነው፣ ፈጽሞ አይታይም።»

አማጽያኑ ኃይላት ለጥበቃ ከሚሠማሩት የቡንደስቬር ወታደሮች ጋር በየጊዜው ይዋጋሉ። የሚዋጉትም በጸረ-ታንክ መሣሪያና በአውቶማቲክ ጠብመንጃ ነው። በፈንጂ መሣሪያዎችም ያጠቃሉ። ካለፈው ዓመት ከጥር ወር አንስቶ አፍጋኒስታ ን ውስጥ በቡንደስቬር ላይ ከተሠነዘሩት ከ 70 በላይ ከሚሆኑት ጥቃቶች፣ ከ60 በላይ የሚሆኑት የተቃጡት በኩንዱስ አካባቢ ነው። በደቡቡ የአገሪቱ ክፍል ከሚሠነዘረው ጋር ሲነጻጻር፣ የሰሜኑ ያን ያክል አይደለም። ይሁንና አንድ ወቅት የተረጋጋ መስሎ በነበረው የአገሪቱ ከፊል ይበልጥ እያገረሸ ያለው ሁከት እጅግ ማሳሰቡ አልቀረም። ለኃይሉ እርምጃ መባባስ፣ ሰበቡ ፣ ኩንዱስ፣ የኔቶ ስንቅና ትጥቅ በሚተላለፍባት መሥመር ላይ የምትገኝ መሆኗ ነው። ለዓለም አቀፉ የፀጥታ ረዳት ኃይል (ISAF)ድጋፍ በመስጠት ረገድ ኀላፊነት ያለባቸውና በተጨማሪ የ(ISAF) ጦር ሹማማንት ኀላፊ ጀርመናዊው ጀኔራል Hans Erich Antoni—

«በሰሜናዊው አፍጋኒስታን፣ የመጓጓዣው መሥመር ይበልጥ ተግባራዊ መሆኑን፣ አማጽያን በቸልታ የሚያልፉት አልሆነም። ዒላማ ያደረጉበት አንዱ ምክንያት ይህ ሊሆን ይችላል። በሌላ በኩል፣ እኔም ይበልጥ ሊሆን ይችላል ብዬ የማምንበት፣ አማጽያኑ፣ በሌሎቹ አካባቢዎች ግፊት ስላየለባቸው ፣ የኔቶና የአፍጋኒስታን ጸጥታ አስከባሪ ኃይሎች፣

ተጠናክረው በማይገኙበት ክፍል ኀይላቸውን ይበልጥ አፈርጥመው መንቀሳቀሱን ሳይመርጡ አልቀሩም። ለዚህ ደግሞ፣ ኩንዱስ ተስማሚ ቦታ ናት።»

የአፍጋኒስታን ሰሜናዊ ጠ/ግዛት ፣ የጦር አውድማ የመምሰል ሁኔታ ያጋጠመው፣ ነሐሴ 29 ቀን 2002 ዓ ም፣ ታሊባኖች ሁለት ቦቴዎችን በቁጥጥር ሥር በማዋላቸውና ከባድ እርምጃ በመወሰዱ ነው። በኩንዱስ የጀርመናውያኑ ጦር ሠፈር አዛዥ፣ የአየር ኃይል ድብደባ እንዲካሄድ በመጠየቁ F-15 የአሜሪካ ተዋጊ ጀት አኤሮፕላን ድብደባ በማካሄድ ፣ የአፍጋኒስታን መንግሥት እንዳስታወቀው ፣ 69 ታሊባኖችና 30 ሲብሎች ነበሩ የተገደሉት። የጀርመን መንግሥት የመከላከያ ሚንስቴር ፣ በወቅቱ አንድም ሲቭል አልተ።ገደለም ሲል ቢያስታውቅም፣ በምሥጢር የቀረበ ዘገባ ፣ የሲቭሎችን መገደል አረጋግጧል። በመሆኑም ወቀሣው፤ በዚህ ረገድ በማየሉ፣ የጀርመን ጦር ኃይሎች ኤታ ማጆር ሹም፣ Wolfgang Schneiderhan በገዛ-ፈቃዳቸው መሆኑ ይጠቀስ እንጂ በዛሬው ዕለት ሥልጣን መልቀቃቸው ሊረጋገጥ ችሏል።

ተክሌ የኋላ/ነጋሽ መሐመድ