በናይጄሪያ የተጣሉ የቦምብ ጥቃቶች
ሰኞ፣ ሚያዝያ 22 2004ትናንት በናይጄሪያ በሰሜናዊቱ ከተማ በካኖ ዩኒቨርሲቲ ግቢ ውስጥ በአንድ የክርስቲያን ተማሪዎች የቅዳሴ ስነ-ስርዓት ላይ በደረሰው ፍንዳታ 15 ሰዎች ሲሞቱ ዛሬ ደግሞ በፋይናንስ ሚኒስቴር ህንፃ ላይ ቦምብ ፈንድቷል ።
ኬንያ ርዕሰ-ከተማ ናይሮቢ ውስጥም ትናንት በአንድ ቤተ-ክርስቲያን ላይ በደረሰ የቦምብ ጥቃት ቢያንስ 15 የሚሆኑ መቁሰላቸው ተገልጿል። ናይጄሪያ ውስጥ ባለፉት ጊዜያት በክርስቲያኖች ላይ በተደጋጋሚ ጥቃት ሲደርስ መቆየቱ ይታወሳል። የአገሪቷ ፖሊስ እንደገለፀው ዛሬ ጠዋት በአገሪቱ የሰዓት አቆጣጠር ከጥዋቱ ሁለት ሰዕት በፋይናንስ ሚኒስቴር ህንፃ ላይ ቦምብ ፈንድቷል ። በሰዓቱ ሰራተኞች ወደ መስራቤታቸው እየገቡ ነበር። የህንፃው ትልቅ አካል መፍረሱንም የፖሊስ ኋላፊው ኢባንግ ባሲከ ለጀርመን የዜና አገልግሎት DPA ገልፀዋል።
በብዛት ክርስትያኖች የሚኖሩበት ሰሜን ምስራቃቂ የአገሪቷ ክፍል ከሌላ የአገሪቷ ክፍሎች ጋ ሲነፃፀር ክርስትያን እና ሙስሊሞች በሰላም ተቻችለው የሚኖሩበት ክፍለ ግዛት በመሆን ይታወቃል። ይሁን እና እንዲሁ ትናንት በሰሜናዊቱ ከተማ በካኖ ዩኒቨርሲቲ ግቢ ውስጥ በደረሰ ፍንዳታ የ15 ሰዎች ህይወት ማለፉ ተነግሯል። ለሁለቱም ጥቃት ሃላፊነቱን የወሰደ አካል የለም። ይሁንና «ቦኮ-ሃራም» የተሰኘ አክራሪ ቡድን ዋና ተጠርጣሪ ነው።
« በዚህ አካባቢ እና ይች ሀገር በእንደዚህ አስገራሚ ሁኔታ ላይ መገኘቷ። በጣም የሚያሳዝን ነው።»
ይላሉ ራቢው ሙሳ የከተዋው ነዋሪ። የቦኮ-ሃራምን ጥቃት አስመልክተው የናይጄሪያ የኢንፎርሜሽን ሚኒስትር ላባራን ማኩ፤ ትልቅ እውቅና በመስጠት ነፍሰ ገዳዮች ጀግንነት እንዲሰማቸው እያደረገን ነው፤ ስለሆነም የመገናኛ ብዙኃን ሽብር ለመቀነስ ስለ ቡድኑ ተግባር መዘገብ መቀነስ አለበት ብለው ነበር። ይህንንም በተመለከተ የናይጄሪያ የጋዜጠኞች ማህበር ኃላፊ ማህመድ ጋርባን የሚኒስትሩን ሀሳብ እንዴት እንደሚመለከቱት ተጠይቀው ሲመልሱ « ከመንግስት ወገን ሆነው ነው የተናገሩት። በእርግጥ በናይጄሪያ በከፊል የሚካሄደው የአገሪቷ ደህንነት ተግዳሮት መሆኑን አውቃለሁ። ጉዳዩን ከደህንነት ጉዳይ ተለይቶ የማይታይበት መንገድ የለም። ስለሆነም እንደ ናይጄሪያውያን ማድረግ የሚገባን ነገር ቢኖር ፤እንደዚህ አይነት ጉዳዮች በትክክል መፍትሄ እንዲያገኙ አስፈላጊ የሆነውን ድጋፍ ለደህንነት መ/ቤቶች መስጠት ነው።»
ቦኮ-ሃራም ለናይጄሪያ ህዝብ ብቻ ሳይሆን ለአገሪቷ የመገናኛ ብዙኃን ፈተና ሆኗል። ቡድኑ ትክክለኛ ያልሆነ መረጃ በመገናኛ ብዙኃን ቀርቧል ሲል ወቅሶ ነበር። ስለሆነም ጋዜጠኞች በማህበረሰቡ ዘንድ ያለባቸውን ኃላፊነት እንዲወጡ የጋዜጠኝነት ስነ ምግባር በትኩረት መመርመር ይኖርበታል ይላሉ ጋምባ ። ይሁንና እነዚህ ጥቃቶች በክርስትያን እና ሙስሊሙ ማህበረሰብ ዘንድ የጎላ ችግር ይፈጥራል ብለው ጋርባ አያምኑም።
« አይ እንደሚመስለኝ ያለው ግንኙነት እጅግ ጤናማ ነው ፤ምክንያቱም ቁጥራቸው ከፍ ያለ በደቡቡ ክፍል የሚኖሩ ሙስሊሞች ይገኛሉ የዛኑ ያህል ቁጥራቸው ከፍ ያለ ክርስትያኖች በሰሜኑ ክፍል ይኖራሉ። እና ያለው ግንኙነት ጤናማ ነው ብዬ አምናለሁ። የናይጄሪያን ታሪክ ብትመለከቱ በተለይ ፖለቲከኞች ይህቺን ሀገር በዘር እና በሀይማኖት ለያይተው ለመከፋፈል እንደሚሞክሩ መገንዘብ ይቻላል። ነገር ግን ናይጄሪያውያን አሁን የበለጠ ንቁ ሆነዋል ብዬ አምናለሁ። የተለያዩ እምነቶች መቻቻል እንዳለባቸው ጎልቶ ይታያል።»
ህዝቡ ተቻችሎ እንደሚኖር ጋርባ ቢገልፁም ለቦኮ ሀራም ቡድን ክርስትያኖች በተለይም ካቶሊኮች የምዕራቡን አለም የሚያንፀባርቁ ስለሆኑ የጥቃታቸው ኢላማ ናቸው።
ልደት አበበ
ሂሩት መለሰ