በታላቁ ሩጫ ለመጀመሪያ ጊዜ 2 ተሳታፊዎች ሞቱ
እሑድ፣ ኅዳር 17 2010ማስታወቂያ
በ17ኛው ታላቁ ሩጫ ዛሬ አዲስ አበባ ውስጥ እድሜያቸው 61 ዓመት እና በ40ዎቹ መካከል የሚገኙ ሁለት ሯጮች ሕይወት ማለፉን የታላቁ ሩጫ ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ ኤርሚያስ አየለ ለዶይቸ ቬለ ገለጡ። የሞቱበትም ምክንያት ግን አልታወቀም። አንደኛው ተሳታፊ ውድድሩን ካጠናቀቁ በኋላ ጊዮን ፋርማሲ አካባቢ በመውደቃቸው ወደ ሆስፒታል ቢወሰዱም ሕይወታቸው ማለፉን ሁለተኛው ተሳታፊ ደግሞ በውድድር ወቅት ሰባተኛው ኪ.ሜትር አካባቢ ወድቀው መሞታቸውን ጨምረው ተናግረዋል። ሁለቱን ተሳታፊው ለሞት ያበቃቸውን ምክንያት ለማወቅ የአስክሬን ምርመራ እየተደረገ መሆኑን አቶ ኤርሚያስ አክለው ተናግረዋል።
በዘንድሮው የታላቁ ሩጫ የጎዳና ውድድር 44 ሺ ተሳታፊዎች ተካፍለዋል። በወንዶች የ10 ኪ.ሜ. ውድድር ሰለሞን ባረጋ፣ ሞገስ ጥዑማይ እና ዳዊት ፍቃዱ ከአንደኛ እስከ ሦስተኛ በመውጣት አሸንፈዋል። ዘይነባ ይመር፣ ግርማዊት ገብረእግዚሃብሄር እና ፎተን ተስፋዬ ደግሞ በሴቶች ምድብ አሸናፊ ሆነዋል።
ማንተጋፍቶት ስለሺ
እሸቴ በቀለ