በሽብር ጥቃቶች ላይ የወጣቶች አስተያየት
ዓርብ፣ ኅዳር 10 2008
የሽብር ጥቃት በተለያዩ የዓለም ሀገራት ከፍተኛ ተፅዕኖ እያሳደረ ይገኛል። በሊቢያ በናይጄሪያ ፣በሶማሊያ በተደጋጋሚ የሽብር ጥቃት ተጥሎ የብዙ ንፁሀን ሕይወት ጠፍቷል።ከሳምንት በፊት ፓርስ ውስጥ ጥቃት የጣለው እና ራሱን እስላማዊ መንግሥት ሲል የሚጠራው ቡድን ከዚህ ቀደም ሊቢያ ውስጥ ኢትዮጵያውያንንም ዘግናኝ በሆነ መንገድ መግደሉ ይታወሳል። በዓለም ላይ ስለሚታየው የሽብር ጥቃት ለመሆኑ ወጣቶች ምን ይላሉ?
በቅድሚያ አስተያየቱን ሊያካፍለን ፍቃደኛ የሆነው፤ የ20 ዓመቱ ወጣት ዮናታን ሲሆን ስለ ፓሪሱ ጥቃት የሰማውም ባህር ዳር ከተማ በፌስ ቡክ ማህበራዊ የመገናኛ ብዙኃን አማካይነት ነው።ሀሳባቸውን ያካፈሉን ሌሎቹ የ 28 ዓመቱ ኢብራሂም ከሶማሌ ክልል እና የአዲስ አበባ ነዋሪ የሆነው የ 25 ዓመቱ ወጣት ዳንኤል ናቸው።
አብዛኛውን ጊዜ በአጥፍቶ መጥፋቱ የሽብር ጥቃት ወጣቶች ሲሳተፉ ተስተውሏል። ለዚህ ደግሞ የተለያዩ ምክንያቶች አሉ ብለው ኢትዮጵያውያን ወጣቶቹ በምክንያትነት ይጠቅሳሉ። ከነዚህም መካከል ስራ አጥነት እና የሽብር ጥቃቶች ሁልጊዜ ከእስልምና ዕምነት ጋር አብረው መታየታቸውን ጠቅሰዋል።
የሽብር ጥቃቶች ላይ ጥቂት ወጣቶች ያካፈሉንን አስተያየት ነበር አድማጮች በዛሬው የወጣቶች ዓለም ያሰማናችሁ። ሳምንት በሌላ ርዕስ እንገናኛለን።
ልደት አበበ
አዜብ ታደሰ