የኢትዮጵያውያን ስደተኞች ምሬት
ዓርብ፣ ሰኔ 2 2009ሱዳን የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ስደተኞች ለመኖሪያ ፈቃድ እድሳት የሚጠየቀው ክፍያ ከአቅማችን በላይ ሆኗል ሲሉ ማማረራቸውን ቀጥለዋል። የታደሰ የመኖሪያ ፈቃድ የሌላቸው ኢትዮጵያውያን ለእስር እና እንግልት እየተዳረጉ መሆኑንም ስደተኞቹ ለዶቼቬለ ተናግረዋል። ኢትዮጵያውያኑ እንደሚሉት በካርቱም የኢትዮጵያ ኤምባሲ ጉዳዩን ይዘነዋል ቢላቸውም ችግራቸው እስካሁን መፍትሄ አልተገኘለትም ። ኂሩት መለሰ
ሱዳን የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ስደተኞች በዚህ ዓመት ተግባራዊ በሆነው በአዲሱ የመኖሪያ ፈቃድ እድሳት ክፍያ መማረራቸውን ለዶቼቬለ ሲገልጹ የመጀመሪያቸው አይደለም። በየካቲት ወር ውስጥ ተመሳሳይ ምሬታቸውን ነግረውን ነበር። ያኔም ሆነ አሁን እንደሚሉት ከቀድሞው ከአምስት እጥፍ በላይ የጨመረው አዲሱ ክፍያ ከአቅማቸው በላይ ነው። ያልታደሰ መታወቂያ ይዘው የሚገኙ ስደተኞችም እየታሰሩ ለእድሳቱ ከሚጠየቀው በላይ የገንዘብ ቅጣት እየተጣለባቸው መሆኑን ካርቱም የሚገኙት እኚህ ስማቸው እንዲገለጽ ያልፈለጉ ተሰዳጅ ለዶቼቬለ ተናግረዋል።
ይህን መሰሉ ችግር የሚገጥማቸው ደግሞ እንደ ኢትዮጵያዊው ስደተኛ የመኖሪያ ፈቃዳቸው ያልታደሰው ዜጎች ብቻ አይደሉም ።
ለኢትዮጵያውያኑ ስደተኞች ችግር እና ጥያቄዎች መፍትሄ ለመሻት በካርቱም የኢትዮጵያ ኤምባሲ ከሚመለከታቸው መሥሪያ ቤቶች ጋር በንግግር እና በቀጠሮ ላይ መሆኑን ባለፈው የካቲት የኢትዮጵያ ኤምባሲ የዲያስፖራ ክፍል ዲፕሎማት አቶ ሙክታር መሐመድ ለዶቼቬለ ተናግረው ነበር። ሆኖም ኢትዮጵያውያኑ እንደሚሉት እስካሁን መፍትሄ አላገኙም።
ስለ ኢትዮጵያውያኑ ችግር እና ኤምባሲው ለመፍትሄው እያደረግኩ ነው ያለው ጥረት ምን ላይ እንደደረሰ በሱዳን የኢትዮጵያ ኤምባሲ ኃላፊዎችን ለማነገጋር ሞክረን ልናገኛቸው አልቻልንም። ሆኖም በስልክ ያገኘናቸው የኤምባሲው ጥበቃ ባልደረባ ነኝ ያሉን ሰው ኤምባሲው የኢትዮጵያውያኑን ጥያቄ ለሚመለከታቸው መሥሪያ ቤቶች በደብዳቤ አቅርቦ መልሱን በመጠባበቅ ላይ መሆኑን ነግረውናል።
ኂሩት መለሰ
ሸዋዬ ለገሠ