በሱዳን የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ስሞታ
ማክሰኞ፣ ጥር 5 2007አቶ አስቻለው አስታጥቄ ከ30 በላይ አመታትን በስደተኝነት በሱዳን ኖረዋል። ለ30 አመታት በኖሩባት ሃገር መንግስትም ሆነ ህዝብ ችግር ገጥሞኝ አያውቅም የሚሉት አቶ አስቻለው ባለፉት ሁለት አመታት ግን ሁኔታዎች መቀየራቸውን ያስረዳሉ።
«በተባበሩት መንግስታት ድርጅት የስደተኞች ከፍተኛ ኮሚሽን እና የሱዳን መንግስት አውቆን ቋሚ የስደተኛ መታወቂያ ተሰጥቶን እያለ ከሁለት አመት በፊት ሁሉንም በጅምላ ጥገኝነት ጠያቂዎች የሚል መታወቂያ አወጡ። ያንን አሜን ብለን በየሶስት ወሩ እየታደሰ እያለ አሁን ደግ ሞ አናድስም አሉ። ምንድነው ምክንያታችሁ ብለን ብንጠይቅም ምክንያት የለም።»
ቄስ ማሩ ሃጎስ በሱዳን የሚኖሩ ኢትዮጵያዊ ስደተኛ ናቸው። በሱዳን ረጅም አመታትን የኖሩት ቄስ ማሩ ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ በኑሯቸው ፈተና እንደገጠማቸው ይናገራሉ። በስደተኝነት ለመኖር የተሰጣቸው ፈቃድ መታደስ አልቻለም። በዚህ ምክንያት ልጃቸው ለእስር ተዳርጎ እንደነበር ይናገራሉ። እንደ ቄስ ማሩ ከሆነ በሱዳን ለአጭር ጊዜ እና ለረጅም ጊዜ የኖሩ የኢትዮጵያ ስደተኞች የመኖሪያ ፈቃድ በሙሉ ጊዜያዊ እንዲሆን ተወስኗል።ጊዜያዊውን የመኖሪያ ፈቃድም ቢሆን ማሳደስ አለመቻላቸው ቄስ ማሩ ሃጎስ ይናገራሉ።
በሱዳን የሚኖሩት ኢትዮጵያውያን በስደተኝነት የሚኖሩበት የመኖሪያ ፈቃድ ሊታደስ ባለመቻሉ እስር እና እንግልት ገጥሞናል ይላሉ። እንደ ቄስ ማሩ ከሆነ ከመታሰር በሊቢያ ወደ አውሮጳ ለመሻገር የሚክሩም አሉ።
«ተሰደው የመጡ እና በሱዳን የተወለዱ ኢትዮጵያውያን እና ኤርትራውያን ልጆች የምንታሰር እና የምንገላታ ከሆነ ብለው ወደ ሊቢያ እየተነሱ ሄደው ብዙዎች በባህር በሰሃራ በርሃ ቀርተዋል።እኔም አሁን የ20 አመት ልጄ የት እንዳለች አላውቅም።»
በሱዳን የተባበሩት መንግስታትድርጅት የስደተኞች ኮሚሽንን ለማነጋገር የሞከርን ሲሆን በጉዳዩ ላይ አስተያየት ለመስጠት ፈቃደኛ አለመሆናቸው ገልጸውልናል። በድርጅቱ ድረ-ገጽ መረጃ መሰረት 7,790 ኢትዮጵያውያን ጥገኝነት ጠያቂዎች በሱዳን ይኖራሉ። አቶ አስቻለው አስታጥቄ የኢትዮጵያ መንግስት አስገድዶ የሚወስዳቸው ስደተኞች መኖራቸውንም ይናገራሉ።
እሸቴ በቀለ
ተክሌ የኋላ