በማህበራዊ መገናኛዎች የሚፈፀሙ ወንጀሎች
ዓርብ፣ መጋቢት 29 2009በዓለም ላይ የፌስቡክ ተጠቃሚዎች ቁጥር ብቻ 1,8 ቢሊዮን ደርሷል። በአጠቃላይ የማህበራዊ የመገናኛ ዘዴዎች ተጠቃሚዎች ቁጥር ባለፉት ዓመታት እጅጉን ጨምሯል። ነገር ግን የተጠቃሚው ቁጥር ብቻ ሳይሆን የሚፈፀሙ ወንጀሎች ቁጥርም ከፍ ብለዋል። ቁጥሩ ከዓመት ዓመት እየጨመረ እንጂ እየቀነሰ አልሄደም። የወንጀል አይነቶቹም የዛኑ ያህል ጨምረዋል። የግለሰብን ፎቶ እና መረጃ ሰርቆ በሰው ስም መነገድ፣ የሀሰት ወሬዎችን ማዛባት እና ስም ማጥፋት፣ ያልሞቱ ታዋቂ ሰዎችንም ይሁን ተራውን ሰው ሞተዋል እያሉ ቀልብ ለመሳብ መሞከር፣ የሽብር ጥቃቶችን ማስተዋወቂያ መድረክ መክፈት፣ ከወሲብ ጋር የተገናኙ ጥቃቶች መፈፀም ከወንጀሎቹ ጥቂቶቹ ናቸው። ለዛሬ የማህበራዊ የመገናኛ ዘዴዎች ተጠቃሚ የሆኑ ሦስት ኢትዮጵያውያን የገጠማቸውን በቅድሚያ በአጭሩ እንቃኛለን።
ሳውዲ አረቢያ የምትኖር እና የምትሰራው አለምፀሀይ ፍቅረኛ ለመተዋወቅ አማራጭ ሆኖ ያገኘችው ፌስቡክ ነበር። እዛም ላይ አንድ ኢትዮጵያዊን ተዋወቀች አቀረበችው። ወጣቷም ፍቅረኛዋን ጨርሶ በአካል ሳታገኘው ግንኙነታቸው በስልክ ብቻ ይቀጥላል። የሆነ ጊዜም ቤት እንስራ ትባልና አለምፀሀይ ገንዘብ ትጠየቃለች። ትልካለችም። ይሁንና በመጨረሻ ግለሰቡ በተለያየ ስም ሌሎች የፌስቡክ ገፆች እንዳሉት እና ፍቅረኛ ያደረጋቸውም ሌሎች 5 ሴቶች እንዳሉ ትደርስበታለች።
ኢትዮጵያ የሚኖረው እና የፌስቡክ ተጠቃሚ የሆነው በላይነህ ደግሞ የገጠመው ከአለምፀሀይ ትንሽ ለየት ይላል። የፌስቡክ ገፁ በፖሊስ ተጠያቂ አድርጎታል። ለምን? ለዶይቸ ቬለ ገልጿል።
ሌላው EA ብላችሁ ጥሩኝ ያለን መምህር ደግሞ በማህበራዊ የመገናኛ ዘዴዎች ትዳሬ ተናግቷል። እኔም በሽታ ላይ ወድቄያለሁ ይላል። በመገናኛ ብዙኃን አማካኝነት ስሙ እንደጠፋ የነገረን EA ከዚያን ጊዜ አንስቶ የቴክኖሎጂው አድናቂ መሆኑ ቀንሷል።
ረዳት ኮሚሽነር የማነ ገሠሠው አዲስ አበባ በሚገኘው የፌደራል ፖሊስ ኮሚሽን፤ የኮሚሽነር ጀነራል ጽህፈት ቤት ኃላፊ ናቸው። ከላይ የጠቀስናቸው አይነት ገጠመኞች ለፌደራል ፖሊስ አዲስ አይደሉም። እነዚህ አይነት ጥቃቶችም በኢትዮጵያ ህግ ያስቀጣሉ። ተጠቂዎች መቼ እና የት ነው ለፖሊስ ማሳወቅ የሚኖርባቸው? ረዳት ኮሚሽነር የማነ ምላሽ ሰጥተውናል።
ሙሉውን ዘገባ በድምፅ ያገኙታል።
ልደት አበበ
አዜብ ታደሰ