በለንደን የሶማሊያን ፀጥታ የተመለከተዉ ጉባኤ
ሐሙስ፣ የካቲት 15 2004ዴቪድ ካምሩን ፣ እንደ ሃገር መንቀሳቀስ ያቃታት ሶማሊያ በሁለት እግሮቿ እንድትቆም ዓለም ሊረዳት ይገባል ሲሉ ተማፅነዋል። የሶማሊያ ችግሮች ቁልፍም ሶማሊያውያን ብቻ መሆናቸውን በንግግራቸው አስገንዝበዋል።
«የሶማሊያ ችግር ሊፈታ የሚችለው በሶማሊያ ህዝብ በቻ ነው። እዚህ የተሰበሰብነው በርቀት ለሚገኝ ሃገር መፍትሄዎቸን በግዳጅ ልንጭን አይደለም ፤ ምን ማድረግ እንዳለባችሁ ልንነግራችሁም አይደለም። ይልቁንም እዚህ የተገኘነው ሁኔታዎችን ለመለወጥ ልንረዳችሁ እና የምታደርጉትን ጥረት ለመደገፍ ነው። ሶማሌዎች ችግራቸውን መፍታት እንደሚችሉና በአፍሪቃ እና በዓለም ውስጥ ሊኖራት የሚገባውን ቁልፍ ሚና መጫወት እንደምትችል ሙሉ በሙሉ እተማመናለሁ።»
ካሜሩን የአሁኑ ስብሰባ ዓላማ የሶማሊያን ፀጥታ ማጠናከር፤ ለሶማሊያ ሰብዓዊ የልማት እርዳታ ማሰባሰብ፣ ሶማሊያውያን የውልክና መንግሥት እንዲያቋቁሙ ዋስትና መስጠት እንደሆነም አስታውቀዋል። በዚሁ ጉባኤ ላይ የተገኙት የዩናይትድስቴትስ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሂለሪ ክሊንተን በበኩላቸው ዓለም ዓቀፉ ማህበረሰብ የሶማሊያን የሰላም ጥረት በሚያደናቅፉ ወገኖች ላይ ማዕቀብ እንዲጥል የመንግሥታቸው ፍላጎት መሆኑን አስታውቀዋል። ከዚሁ ጋርም የሶማሊያን መንግሥት የሚወጋው አሸባብ እየተዳከመ መሄዱን ያሳወቁት ክሊንተን በቡድኑ ላይ የሚደረገው ጫና ግን መቀጠል አለበት ብለዋል። አሸባብ ና አልቃይዳ ዘመን ያለፈባቸውን ቡድኖች ናቸው ሲሉም ተናግረዋል።
« አልሸባብ ና አልቄይዳ በመገፋታቸውና በመገለላቸው አንድ ላይ ሆነዋል ። በተለይ በብዙ አገሮች ዲሞክራሲያዊ አብዮቶች በሚካሄዱበት በአሁኑ ወቅት ከዚህ ቀደም በአክራሪ ኃይላት ተስበው የነበሩ ወጣቶች ይበልጡን ገንቢ የሆነ አቅጣጫ ተከፍቶላቸዋል ። መፃኤው እድል ይሄ ነው ። አሸባብና አልቃይዳ ጊዜ አልፎባቸዋል ። »
በለንደኑ ጉባኤ ላይ የተገኙት የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ዋና ፀሀፊ ባን ኪሙን ደግሞ ሶማሊያ ከግጭትና ከድህነት አዙሪት የመውጣት እድሉ አላት ብለዋል። ከሃምሳ የሚበልጡ ርዕሳነ ብሄርና መራህያነ መንግስት እንዲሁም የልዩ ልዩ ዓለም ዓቀፍ ድርጅቶች ተወካዮች የተገኙበት የለንደኑ የሶማሊያ ጉዳይ ጉባኤ በሶማሊያ የባህር ዳርቻ በሚንቀሳቀሱት የባህር ላይ ወንበዴዎች ላይ በሚወሰደው የተቀናጀ እርምጃ ላይም ተነጋግሯል።
ሂሩት መለሰ
አርያም ተክሌ
ሎንዶን ላይ በሱማሊያ ጉዳይ ላይ የሚመክረዉ ዓለም ዓቀፉ ጉባኤ ከመጀመሩ አንድ ቀን አስቀድሞ የተመድ የፀጥታዉ ምክር ቤት ሶማሊያ ዉስጥ የሚገኘዉን የአፍሪቃ ኅብረት የሠላም አስከባሪ ኃይል ቁጥርና አቅም ለማሳደግ ወሰነ። ምክር ቤቱ ለሠላም አስከባሪዉ ኃይል ስኬት የአፍሪቃ ኅብረት ሐገራት ሠራዊት በማዋጣት የተቀናጀ ድጋፍ እንዲያደርጉም ጠይቋል።
ሶማሊያ የሚገኘዉ የኢትዮጵያ ሠራዊት ከሶማሊያ የሽግግር መንግስት ወታደሮች ጋ በመሆን ከአምስት በላይ ከተሞችን ከአሸባብ ማስለቀቅ መቻሉን የኢትዮጵያ መንግስት አስታወቀ። ከሁለት አስርት ዓመታት በላይ ለዘለቀዉ የሶማሊያ ጦርነትና ግጭት መፍትሄ ለመፈለግ ዓለም አቀፍ ጉባኤ ዛሬ ሎንዶን ላይ እየተካሄደ ነዉ። በዚህ ላይ የኢትዮጵያን አመለካከትና በቀጣይ ሊኖር የሚችለዉን ሁኔታ አስመልክቶ ወኪላችን ጌታቸዉ ተድላ ኃይለጊዮርጊስ የዉጭ ጉዳይ ሚኒስቴርን ቃል አቀባይ አምባሳደር ዲና ሙፍቲን አነጋግሮ ቀጣዩን ዘገባ አድርሶናል።
አበበ ፈለቀ/ ጌታቸዉ ተድላ ኃይለጊዮርጊስ
ሸዋዬ ለገሠ
አርያም ተክሌ