ሰዉ ሰራሽ የአየር ንብረት ለዉጥ ተጽዕኖ
ማክሰኞ፣ ታኅሣሥ 11 2009የአሜሪካ የዉቅያኖስ እና ከባቢ አየር አስተዳደር ያወጣይ ይህ ጥናት እንደሚለዉ ግራ አጋቢ እና ያልተለመዱ ካላቸዉ 30 የአየር ጠባይ ክስተቶች በ24ቱ ላይ ሰዎች የፈጠሩት የአየር ንብረት ለዉጥ ጫና ታይቶባቸዋል።
ያለፈዉ ጎርጎሪዮሳዊ ዓመት 2015 በተለያዩ የዓለም ክፍሎች ብዙም ያልተገመቱ እና ያልተጠበቁ የአየር ጠባይ ክስተቶችን አስተናግዷል። ከፍተኛ ሙቀት፤ እንደ ብሪታንያ ባሉት አካባቢዎች ደግሞ በክረምት ያልተለመደ ፀሐይ፤ በዩንይትድ ስቴትስም በአንድ ወገን ከበድ ያለ ቅዝቃዜ፤ በሌላ በኩል ደግሞ የሰደድ እሳት፤ ወጀብ እና ማዕበልም በተለያዩ አካባቢዎች እያልን መዘርዘር ይቻላል። ባለፈዉ ሳምንት ሐሙስ ዕለት በዚህ ላይ አተኩሮ የአሜሪካ የዉቅያኖስ እና ከባቢ አየር አስተዳደር ያወጣዉ ጥናት ለማመልከት የሞከረዉ ከእነዚህ በጣም ፅንፍ የወጡ የአየር ጠባይ ክስሰቶች አብዛኞቹ የሰዎች እንቅስቃሴ ያመጣዉ የአየር ንብረት ለዉጥ ጫና አድርጎባቸዋል የሚለዉን ነዉ። ይህም ደግሞ በምሳሌነት በአላስካ፤ በዋሽንግተን እንዲሁም በደቡብ ዩናይትድ ስቴትስ፤ በካናዳ፤ አዉሮጳ፣ አዉስትራሊያ፣ ቻይና፣ ጃፓን፣ ኢንዶኔዢያ፣ ሲሪ ላንካ፣ ህንድ፣ ፓኪስታን፣ ግብፅ፣ ኢትዮጵያ እና ደቡብ አፍሪቃ የታየዉ የአየር ጠባይ ላይም የአየር ንብረት ለዉጡ የበኩሉን ተፅዕኖ ማሳረፉን ያመላክታል። ለመሆኑ ይህ ምን ማለት ነዉ? በካናዳዉ ካልጋሪ ዩኒቨርሲቲ የአካባቢ ተፈጥሮ ዘርፍ ተባባሪ ፕሮፌሰር እና ተመራማሪ ዶክተር ጌታቸዉ አሰፋ።
ይህን መሰሉ ጥናት ሲደረግ ይህ የመጀመሪያ አይደለም አምሰተኛ ጊዜ መሆኑ ነዉ የአሁኑ። በጎርጎሪዮሳዊዉ 2013ዓ,ም የወጣዉ አንዱ ጥናት በየዓለመቱ በተወሰነ ወቅት የሚጠበቁ የአየር ጠባይ ክስተቶች ምን ያህል ከአየር ንብረት ለዉጥ ጋር ግንኙነት አላቸዉ የሚል ጥያቄ አንስቷል።
በዚህ ምርምር 116 የሚሆኑ የዘርፉ ተመራማሪዎች መሳተፋቸዉን እና ዉጤቱም የእነሱን ይሁንታ አግኝቶ ለአደባባይ እንደበቃ ነዉ የተገለፀዉ። በጥናቱ ካልተሳተፉ መካከል አንዳንዶች ግኝቱ አንድ ነገር መሆኑን አፅንኦት ሰጥተዉ እንዲያም ሆኖ ሁሉንም ክስተቶች አላጠቃለለም ይላሉ። ለምሳሌ ከተነሱት መካከልም ባለፈዉ የካቲት ወር በዩናይትድ ስቴትስ ሰሜን ምሥራቅ አካባቢ የታየዉ ከባድ ቅዝቃዜ ወይም ደግሞ በናይጀሪያ እና ህንድ የታየዉ ከባድ ሙቀት ተጠቃሽ ናቸዉ። እነሱ እንደሚሉት የእነዚህ ክስተቶች መንስኤ ከዚህ ይለያል ነዉ።
ይህ ጥናት የወጣዉ የአየር ንብረት ለዉጥ የሚባል ነገር የለም የሚል ፅኑ አቋማቸዉን በአደባባይ የሚያስተጋቡት ቱጃሩ ዶናልድ ትራምፕ በዩናይትድ ስቴትስ የፕሬዝደንትነቱን በትረ ስልጣን ሊጨብጡ ከአንድ ወር ያነሰ ጊዜ ሲቀራቸዉ ነዉ። ቢሊየነሩ ለሀገሪቱ የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣንነት ያጩዋቸዉ ብጤያቸዉን ማይሮን ኢቤልን መሆኑ ደግሞ ከሀገሬዉ ብቻ ሳይሆን በተለያዩ ሃገራትም ስጋትና መደናገር አስከትሏል። ምናልባት ከአንድ መቶ የሚበልጡ ሳይንቲስቶች ያመኑበት እና በሀገሪቱ የዉቅያኖስ እና ከባቢ አየር አስተዳደር የቀረበ ይህ ጥናት ለአዎንታዊ አመለካከት መንገድ ይከፍት ይሆን? ዶክተር ጌታቸዉ የንግድ ጉዳይ ሚናዉ ስለሚያይል ለዉጥ አያመጣም ባይ ናቸዉ። ሙሉ ቅንብሩን ከድምጽ ዘገባዉ ያድምጡ!
ሸዋዬ ለገሠ
ነጋሽ መሐመድ