ሣን-ሱ-ቺ በምርጫዉ ታሪካዊ ድል ሳይጎናጸፉ አይቀርም
እሑድ፣ መጋቢት 23 2004ማስታወቂያ
በርማ ውስጥ በዛሬው ዕለት የሰላም ኖቤል ተሸላሚዋ አውንግ-ሣን-ሱ-ቺ ለመጀመሪያ ጊዜ የተሳተፉበት ማሟያ የም/ቤት ምርጫ ተካሄደ። ተቃዋሚው ብሄራዊ የዴሞክራሲ ሊጋ ከወዲሁ እንዳስታወቀው ድርጅቱና መሪው ሣን-ሱ-ቺ በምርጫው ታሪካዊ ድል ሳይጎናጸፉ አልቀሩም። ተቃዋሚው ድርጅት ሱ-ቺ ከራንጉን በስተደቡብ በተወዳደሩበት አካባቢ በብዙሃን ድምጽ ማሸፋቸውንና ውድድር ከተደረገባቸው 45 የም/ቤት መቀመጫዎች አንዱን እንደሚይዙም አስታውቋል። የምርጫው ይፋ ውጤት በይፋ ይቀርባል ተብሎ የሚጠበቀው ገና ከጥቂት ቀናት በኋላ ነው። ተቃዋሚዎች በምርጫው አካሄድ ላይ ጉድለት ማየታቸውን ሲናገሩ ዓለምአቀፍ ታዛቢዎች በአንጻሩ ድምጽ-አሰጣጡ በአብዛኛው ችግር-አልባ እንደነበር አመልክተዋል። የበርማ መፍቀረ-ዴሞክራሲው እንቅስቃሴ መሪ ሱ-ቺ የአገሪቱን ወታደራዊ አገዛዝ ከሃያ ዓመታት በላይ ሲታገሉ አብዛኛውን ጊዜ በቁም-እሥር ማሳለፋቸውም የሚታወቅ ነው። ምርጫው የደቡብ-ምሥራቅ እሢያይቱ አገር መንግሥት የለውጥ ቁርጠኝነት መለኪያ ሆኖ ሲታይ የአውሮፓ ሕብረትና አሜሪካ አሁን በበርማ ላይ የጣሉትን ማዕቀብ ቢቀር በከፊል እንደሚያነሱ ይጠበቃል።
አዜብ ታደሰ
መስፍን መኮንን