ሣምንታዊ የስፖርት ጥንቅር
ሰኞ፣ ታኅሣሥ 14 2006ይህ አማካይ ባየርን ተጫዋች 30 ዓመቱን ሊደፍን ጥቂት ነው የቀረው፤ ማነው?
አርሰናል ብቸኛ ግስጋሴው ለጊዜውም ቢሆን የተገታ ይመስላል፤ አሁን አንድ ተስተካካይ ጨዋታ እየቀረው መሪው ሊቨርፑል በአንድ ነጥብ በልጦታል። ዛሬ ምሽት አራት ሠዓት ላይ ከሌላኛው የእንግሊዝ ፕሬሚየር ሊግ ተቀናቃኝ ቸልሲ የሞት ሽረት፣ ኃያል ፍልሚያ ይጠብቀዋል። አርሰናል ምሽቱን በለስ ከቀናው በድጋሚ የደረጃ ሠጠረዡን በበላይነት ይቆጣጠራል ማለት ነው። 36 ነጥቦችን ይዞ የደረጃ ሠንጠረዡን የሚመራው ሊቨርፑል ደጋፊዎች ፀሎት ያ እንዳይከሰት ነው። ለነገሩ በ33 ነጥብ አምስተኛ ደረጃ ላይ የሚገኘው ቸልሲም ቢሆን ዛሬ ካሸነፈ ወደጫፍ መጠጋቱ አይቀርም። ቸልሲ 35 ነጥቦችን ሰብስቦ ሁለተኛ ደረጃ ላይ ከሚገኘው ማንቸስተር ሲቲ በሁለት ነጥብ ብቻ ነው የሚለየው።
ኤቨርተን ትናንት ስዋንሲን 2 ለ1 ሸኝቶ 34 ነጥቦችን ሲያስመዘግብ በደረጃ ሠንጠረዡ አራተኛነትን ተቆናጧል። እላይ ለሰፈሩት ለእነሊቨርፑልም ብዙም አልራቅኳችሁም እያለ ነው። ቶትንሐም ሳውዝሐምፕተንን 3 ለ2 አሸንፏል ከትናንት በስትያ ደግሞ ሁለቱ ማንቸስተሮች እና ሊቨርፑል ድል ቀንቷቸዋል። ማንቸስተር ዩናይትድ ዌስትሐምን እንዲሁም ሊቨርፑል ካርዲፍሲቲን እያንዳንዳቸው 3 ለ1 አንበርክከዋል። ማንቸስተርሲቲ በበኩሉ ፉልሀምን 4 ለ2 ረቷል። ኒውካስል ክሪስታል ፓላስን 3 ለባዶ አብረክርኮታል። ስቶክአስቶንቪላን 2 ለ1 ሲያሸንፍ፤ ሰንደርላንድ ከኖርዊች ባዶ ለባዶ፣ እንዲሁም ዌስትብሮም ከሁልሲቲ ጋር አንድ ለአንድ አቻ ወጥተዋል።
የማንቸስተር ሲቲ እና የሊቨርፑል ተጫዋቾች በርካታ ግቦችን ከመረብ በማሳረፍ ከአንደኛ እስከ አራተኛ ደረጃን ይዘዋል። እስካሁን ድረስ ግን የሊቨርፑሉ ግብ አዳኝ ሉዊስ ሱዋሬዝን ፕሬሚየር ሊጉ ውስጥ የሚስተካከለው አልተገኘም። የጎርጎሮሳዊው ዓዲስ ዓመት ሊብት ጥቂት ቀናት በቀሩበት በአሁኑ ወቅት ያስመዘገባቸው ግቦች 19 ደርሰዋል። የማንቸስተርሲቲው ሠርጂዮ አጉዌሮ በ6 ግቦች ተበልጦ ይከተለዋል። ሌላኛው የሊቨርፑል የቁርጥ ቀን ልጅ ዳንኤል ስቱሪጅ እና የማንቸስተርሲቲው ያያ ቱሬ እያንዳንዳቸው 9 ግቦችን ከመረብ በማሳረፍ ሶስተኛ ደረጃ ላይ ይገኛሉ።
ባየርን ሙንሽን ግስጋሴውን ቀጥሏል
ወደጀርመን ቡንደስ ሊጋ ስንሻገር ደግሞ በርካታ ግቦችን በማሳረፍ የመሪነቱን ስፍራ የያዙት ሶስት ተጨዋቾች ከባለፈው ሣምንት ምንም አይነት ለውጥ አላሳዩም። የቦሩሲያ ዶርትሙንዱ ሮበርት ሌቫንዶቭስኪ ልክ እንደባለፈው ሣምንት ሁሉ በ11 ግቦች እየመራ ይገኛል። የሔርታ ቤርሊኑ አድሪያን ራሞስ እና የባየርሙንሽኑ ማሪዮ ማንቹኪ እያንዳንዳቸው 10 ግቦችን በማስቆጠር ይከተሉታል። አንድ ተስተካካይ ጨዋታ የሚቀረው ባየርሙንሽን አሁንም የደረጃ ሠንጠረዡን በ44 ነጥብ እየመራ ይገኛል። ባየርሊቨርኩሰን በ7 ነጥብ ልዩነት ለመከተል ግድ ሆኖበታ። ቦሩሲያ ሞንሽንግላድባህ ቦሩስያ ዶርትሙንድን በአንድ ነጥብ በልጦ 33 ነጥቦችን በመያዝ ሶስተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል።
በጀርመንም ሆነ በዓለም ከሚገኙ ታላላቅ ቡድኖች መካከል ዘንድሮ እንደባየር ሙንሽን በድል የሰከረ የእግር ኳስ ቡድን የለም። ባየርን ከትናንት በስትያ የዓለም የእግር ኳስ ቡድኖች ዋንጫን ሞሮኮ ድረስ በመጓዝ ከራጃ ካዛብላንካ ቡድን ነጥቋል። የሞሮኮ ንጉሥ ሞሐመድ ስድስተኛን ጨምሮ 45 000 ተመልካቾች በተገኙበት ማራኬ ሽስታዲየም ባየርን ሙንሽን ካዛብላንካን 2 ለባዶ ኩም በማድረግ የዋንጫው ባለቤት ሆኗል። ሊጠናቀቅ በቀረው የጎርጎሮሳዊው ዓመት ባየር ሙንሽን የሻምፒዮንስ ሊግን ጨምሮ የተለያዩ ዋንጫዎችን በእጁ ሲያስገባ የትናንት ወዲያው አምስተኛው መሆኑነው። የጀርመን ብሔራዊ ቡድን እና የባየር ሙንሽን ተሰላፊው ፊሊፕ ላም ዋንጫውን ከሞሮኮው ንጉሥ እጅ ከተረከበ በኋላ ስሜቱን እንዲህ ነበር የገለፀው።
«ዛሬ በመጠኑም ቢሆን ራሳችንን ችግር ውስጥ ከተን ነበር። ጥሩው ነገር ግን ሜዳ ውስጥ ተረጋግተን ነው የገባነው። በፍጥነት ግብ ማስቆጠር ፈልገን ተሳክቶልናል። ከእዚያ በኋላ በጣም ቀለለን ማለት ይቻላል። ቆየት ብሎ ግን ትንሽም ቢሆን ተዳክመን ነበር። በስተመጨረሻ ይሄን ተጨማሪ ዋንጫ በአንድ ዓመት ውስጥ ጨብጠናል። የማይታመንነው።»
ለባየር ሙንሽን ሁለቱን ግቦች ያስቆጠሩት ዳንቴ እና ቲያጎና ቸው። ገና ሰባተኛው ደቂቃ ላይ ነበር ዳንቴ የመጀመሪያዋን ግብ ከሰባት ሜትር ርቀት ገደማ ላይ ከመረብ ሲያሳርፍ። ከእዚያም ሁለተኛዋን ግብ ቲያጎ ያስቆጠረው በ22ኛው ደቂቃ ገደማ ነበር። ካዛብላንካዎች ከእረፍት መልስ ሁለት የግብ ድሎችን አምክነዋል። በተለይ የባየርሙንሽኑ ግብ ጠባቂ ማኑኤል ኖየር የለጋት ኳስ ብዙም ሳትርቅ የካዛብላንካ ተጫዋች እግር ብትገባም ወደ ውጤት አልተቀየረችም። ሁኔታው ለባየርኑ ግብ ጠባቂ ማኑኤል ኖየር ከእፍይታም በላይነ በር።
«አሁን በቃ የእረፍት ጊዜያችን አስደሳች ነው የሚሆነው። ከእዚያ በፊት አሸንፈናል። ዋንጫው ለእኛ ከፍተኛ ትርጉም ነው ያለው። ከምንም በላይ ግን እዚህ ድረስ መጥተን አሸንፈናል። በጣም ነው ደስ የሚለው።»
ሞሮኮ ውስጥ በተካሄደው የዓለም የእግር ኳስ ቡድኖች ዋንጫ ውድድር የደቡብ አሜሪካው ሻምፒዮን የብራዚሉ አትሌቲኮ ሜኔሮ የቻይናውን ባለድል ጉዋንዡኤቨርግራንዴን በጭማሪ ሠዓት 3 ለ2 አሸንፏል። በእዚሁ ሞሮኮ ውስጥ በተካሄደው ፍልሚያ ባለድል የሆነው የባየርሙንሽኑ አማካይ ተጨዋች ባስቲያን ሽቫይንሽታይገር ዕድሜዬ 30 ቢጠጋም ገና የዛሬ 8 ዓመት የሚካሄደውን የዓለም ዋንጫ እሳተፋለሁ ሲል ተናግሯል። ለጀርመን ብሔራዊ ቡድን 100 ጊዜ የተሰለፈው ባስቲያን የማንቸስተር ዩናይትዱ ሪያንጊግስ በ40 ዓመቱ ምርጥ እንቅስቃሴ እያሳየ ነው።
ስለእዚህ አይደለም ከብራዚል ቀጥሎ በፈረንሳይ በሚካሄደው በሩስያው የዓለም ዋንጫም የመሳተፍ ብቃት አለኝ ሲል ተናግሯል። ባስቲያን ሽቫይንሽታይገር ጀርመን በተካሄደው እና በደቡብ አፍሪቃው የዓለም ዋንጫ ተሳታፊ ነበር። አሁን በጉዳት ላይ የሚገኘው ባስቲያን በእርግጥም እዚያ የመድረስ ብቃት ይኖረው እንደሆን በብራዚሉ የዓለም ዋንጫ ላይ የሚፈተን ይሆናል።
ላሊጋውን ባርሴሎና እየመራ ነው
በስፔን ላሊጋ ባርሴሎና በ46 ነጥብ አሁንም መሪነቱን እንዳስከበረ ነው። አትሌቲኮ ማድሪድ በግብ ልዩነት ብቻ ሁለተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ኃያሉ ሪያልማድሪድ ከባርሴሎና በ5 ነጥብ ዝቅ ብሎ ሶስተኛ ደረጃን ይዟል። ትናንት በላሊጋው ግጥሚያ ኤስፓኞላ ቫላዶይድን 4 ለባዶ ቀጥቷል። ባርሴሎናም ጌታፌን 5 ለ2 አርበድብዶ ጥንካሬውን አሳይቷል። ማድሪድ ቫሌንሺያን 3 ለ2፣ አትሌቲኮ ቢልባዎ ራዮቫሌቻኖን 2 ለ1 አሸንፈዋል። የሪያል ማድሪዱ ዲዬጎ ኮስታ በ19 ግቦች ኮከብ ግብ አግቢነቱን እንዳስጠበቀ ነው። የሪያል ማድሪዱ ክሪስቲያኖ ሮናልዶ በ18 ግቦች እንዲሁም ዣቪጉዌራእና አንቶኒዮ ግሪስማን በ11 ግቦች ሁለተኛ እና ሶስተኛ ደረጃ ላይ ይገኛሉ።
በጣሊያን ሴሪኣ የፊዮሬንቲናው ጁሴፔሮሲ በ14 ግቦች መሪነቱን ይዟል። የጁቬንቱሱ ካርሎስ ቴቬዝ በ11 ግቦች ይከተላል። የኢንተርሚላኑ ሮድሪጎ ፓላቺዮ 10 ግቦችን ከመረብ አሳርፏል። ጁቬንቱስ በ46 ነጥብ የደረጃ ሠንጠረዡን በመምራት ላይ ይገኛል ሮማ በ41 ነጥብ ሁለተኛ፣ ናፖሊ በ36 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዘዋል። ኢንተርሚላን በፊዮሬንቲና በ2 ነጥቦች ተበልጦ በ31 ነጥብ አራተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ትናንት በተደረገው የሴሪኣው 8 ግጥሚያዎች አራቱ አሸናፊ ቡድኖች ያሸነፉት እያንዳንዳቸው አራት አራት ግቦችን በማስቆጠር ነበር። ጁቬንቱስ አትላንታን 4 ለ1፣ ሮማ ካታንያን 4 ለባዶ፣ ቶሪኖ ቺዬቮን እንዲሁም ቬሮና ላትሲዮን 4 ለ1 አሸንፈዋል።
አጠር ያሉ ስፖርት ነክ ዘገባዎች
የቀድሞው የBBC የስፖርት ዘጋቢየ87 ዓመቱ ጋዜጠኛ ዴቪድኮሌማን አረፈ። ዴቪድ ለ50 ዓመታት ግድም ለBBC በስፖርት ዘጋቢነት ያገለገለ ሲሆን፤ 11 የኦሎምፒክ እና 6 የዓለም ዋንጫ እግር ኳስ ግጥሚያዎችን በመዘገብ ይታወቃል።
የባየር ሙንሽኑ ወሳኝ ሰው ፍራንክሪቤሪ በዓለም የእግር ኳስ ቡድኖች ፍልሚያ ምርጥ ተጨዋች ተብሎ ከመመረጡ 24 ሠዓታት ባልሞላ ጊዜ ውስጥ የጀርመን የዓመቱ ምርጥ ተጨዋች ተብሎ በድጋሚ መመረጡም ተገለፀ።
የጀርመን አዲሷ የትብብር ሚንስትር ጌርድሙለር እጎአ በ2022 ካታር የዓለም ዋንጫን እንድታዘጋጅ መታጨቷ አግባብ አይደለም አሉ። የ58 ዓመቷ ጀርመናዊት ፖለቲከኛ የትችታቸው መንስዔ የካታር ሠብዓዊ አያያዝ እንደሆነም ጠቅሰዋል። የስፖርት ዝግጅታችን በተመለከተ አስተያየታችሁን ላኩልን። ተሳትፎዋችሁ አይለየን።
ማንተጋፍቶት ስለሺ
ኂሩትመለሰ