ሞኖሮቪያ፤ በላይቤሪያ የኤቦላ ወረርሽኝ ስጋት አከተመ
ሐሙስ፣ ጥር 5 2008በወቅቱ የወረርሽኙ መስፋፋት ከመድኃኒት አለመገኘት ጋር ተደራርቦ ያሰጋዉ የዓለም የጤና ድርጅት በመላዉ ዓለም የጤና ስጋት መከሰቱን አዉጆ ነበር። በበሽታዉ ከተጠቁት ሃገራት ቀደም ሲል ጊኒ እና ሴራሊዮን ከኤቦላ ተሐዋሲ ስጋት ነፃ መሆናቸዉን ድርጅቱ ባለፈዉ ወር አመልክቷል። ከኤቦላ ነፃ የመሆኛዋን ቀን ስትጠብቅ የቆየችዉ ላይቤሪያ ዛሬ የጠበቀችዉን ይህን የምስራች በዋና ከተማዋ ተቀብላለች። በዓለም የጤና ድርጅት የአስቸኳይና አደጋ ሰብዓዊ አስተዳደር ዳይሬክተር ዶክተር ሪክ ብረኒን የወረርሽኙ ስርጭት በላይቤሪያ ብቻ ሳይሆን በመላዉ ምዕራብ አፍሪቃ ማክተሙን እንዲህ አብስረዋል።
«ክቡራት እና ክቡራን ዛሬ ጥሩና ወሳኝ ቀን ነዉ። የዓለም የጤና ድርጅት በቅርቡ ላይቤሪያ ዉስጥ የተቀሰቀሰዉ ገዳይ የኤቦላ ተሐዋሲ ወረርሽኝ ማክተሙን ይፋ ያደርጋል። ወረርሽኙ ካለፈዉ ኅዳር አጋማሽ ጀምሮ የመቆሙ ክትትል ሲደረግ ቆይቷል። በዚህም ላይ ሶስቱም የምዕራብ አፍሪቃ ሃገራት ጊኒ፤ ሴራሊዮን እና ላይቤሪያ ይህን ፈታኝ ወረርሽኝ ከተቀሰቀሰበት ጊዜ አንስቶ ለመጀመሪያ ጊዜ በጋራ ስርጭቱ እንዲቆም ማድረግ ችለዋል።»
አያይዘዉም ምንም እንኳን ወረርሽኙ አብቅቷል ቢባልም በበሽታዉ ተይዘዉ ከሞት የተረፉትን የመከታተል የማማከርና ተገቢዉን የህክምና ርዳታ የመስጠቱ እንቅስቃሴ ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም አመልክተዋል። ላይቤሪያ ከኦቦላ ነፃ የመሆኗ ማረጋገጫ የተሰማዉ የመጨረሻዉ የኤቦላ ታማሚ ተሐዋሲዉ በዉስጡ እንደሌላ ከተረጋገጠ ከ42ቀናት በኋላ መሆኑ ነዉ። ላይቤሪያ ቀደም ሲል ባለፈዉ ግንቦት ወር ከኤቦላ ነፃ መሆኗን ይፋ አድርጋ ነበር። ሆኖም በተሐዋሲዉ የተያዙ አዳዲስ በሽተኞች ሲገኙ ዳግም ከኤቦላ ለመላቀቅ ያለፉትን ወራት ስትታገል ሰንብታለች። በኤቦላ የሞቱትን ጨምሮ ባጠቃላይ በተሐዋሲዉ 28,600 ሰዎች መያዛቸዉን የዓለም የጤና ድርጅት መዝግቧል።