ምዕራባዊ ሰሀራ እና የ«ሚኑርዞ» ተልዕኮ 25ኛ ዓመት
ቅዳሜ፣ ሚያዝያ 22 2008በሰሜን ምዕራባዊ አፍሪቃ የሚገኘው ምዕራባዊ ሰሀራ እጎአ በ1975 ዓም ከስጳኝ ቅኝ አገዛዝ ከተላቀቀ በኋላ ግዛቱ ይገባናል ያሉት ሞሮኮ እና ሞሪታንያ ግዛቱን እጎአ እስከ 1979 ዓም ተከፋፍለውት ቆይተዋል። ከዚያ ሞሪታንያ ግዛቱን በለቀቀችበት ጊዜ እአአ ህዳር ስድስት ፣ 1975 ዓም ወደ ምዕራባዊ ሰሀራ «አረንጓዴ ጉዞ» ያካሄደችው ሞሮኮ ይህንኑ ደቡባዊ አካባቢ ከግዛቷ አጠቃልላ ዛሬም እንደተቆጣጠረችው ትገኛለች። በዚህም የተነሳ የምዕራባው ሰሀራ ሕዝብን የወከለው የሞሮኮን ርምጃ እንደ ወረራ የተመለከተው በአልጀርያ የተረዳው የፖሊሳርዮ ግንባር ለግዛቱ ነፃነት ለብዙ ዓመታት በሞሮኮ መንግሥት አንፃር ውጊያ አካሂዶዋል።
ይኸው 15 ዓመት ሙሉ የቀጠለው ውጊያ በተመድ ሸምጋይነት በተካሄደ ድርድር እጎአ ከመስከረም ስድስት ፣ 1991ዓም በፀና የተኩስ አቁም ደንብ አቁሞዋል፣ የተመድ ፀጥታ ጥበቃ ምክር ቤትእጎአ ሚያዝያ 29፣ 1991ዓም ባሳለፈው ውሳኔ አንቀጽ 690 ም በሞሮኮ እና በፖሊሳርዮ መካከል የተደረሰውን የተኩስ አቁም ደንብ የሚቆጣጠር እና የምዕራባዊ ሰሀራ ሕዝብም ስለግዛቱ የወደፊት እጣ በሬፈረንደም የሚወስንበትን ሂደት የሚከታተል በምህፃሩ «ሚኑርዞ» የተባለውን የተመድ ተልዕኮ አቋቁሞዋል። ተልዕኮው 245 ወታደሮች እና ሲቭል ሰራተኞች የያዘው ይኸው ተልዕኮ አሁን 25ኛ ዓመቱን ቢሞላም፣ ተልዕኮውን ሙሉ ለሙሉ አላስፈጸመም። ይሁን እንጂ፣ በሕዝበ ውሳኔው የሚሳተፈውን ሕዝብ ምዝገባ በተመለከተ በሞሮኮ እና በሳህራውያኑ መካከል በተፈጠረ ልዩነት ሬፈረንደሙ እስከዛሬ አልተደረገም።
ከ«አረንጓዴው ጉዞ» በኋላ ወደ አካባቢው የገቡት የሞሮኮ ዜጎች በሕዝበ ውሳኔው እንዲሳተፉ ሞሮኮ የያዘችውን እቅድ ሳህራውያኑ ዛሬም እንደተቃወሙት ሲሆን፣ የውዝግቡ መፍትሔ ዛሬም እንደራቀ ይገኛል፣ የተመድ ዋና ጸሐፊ ፓን ኪ ሙን በአልጀርያ 90,000 ተፈናቃይ ሳህራውያን የሚኖሩበትን እና ፖሊሳርዮ የሚያስተዳድረውን ጎስቋላውን የቲንዱፍ መጠለያ ጣቢያ ባለፈው ወር ከጎበኙበት ጊዜ አንስቶምውዝግቡ በተመድ እና በሞሮኮ መካከል ልዩነት ፈጥሮዋል። ፓን ኪ ሙን ያኔ ሁኔታውን እንዲህ ነበር የገለጹት፣
« የቲንዱፍ መጠለያ ጣቢያን ጎብኝቼ መመለሴ ነው። በዚያ ስደተኞቹ የሚኖሩበትን ከባድ ሁኔታ ተመልክቼአለሁ። ካለፉት 40 ዓመታት ወዲህ ከቤተሰቦቻቸው ተለያይተው ነው የሚኖሩት፣ ባየሁt በጣም በጣም አዝኛለሁ፣ በተለይ ደግሞ የሕፃናቱ እጣ ፈንታ አሳስቦኛል። »
እነዚህ ሕፃናት ከስደተኛው ጣቢያ አጥር ማዶ ሌላ ዓለም እንደማያውቁ የገለጹት የተመድ ዋና ጸሐፊ ስደተኞቹን ወደ ትውልድ ቦታቸው፣ ማለትም፣ ወደ ምዕራባዊ ሰሀራ መመለስ ይችሉ ዘንድ ሞሮኮ እና አልጀርያ በጀመሩት ውይይታቸው አንድ ሁነኛ ውጤት እንዲያስገኙ አሳስበዋል።
« በምዕራባዊ ሰሀራ ጥያቄ ላይ ድርድር የጀመሩት ቡድኖች እስካሁን ተቀናቃኞቹ ወገኖች የሚቀበሉት ትክክለኛ እና ዘላቂ ፖለቲካዊ መፍትሔ ማስገኘት የሚያስችል መሻሻል አላሳዩም። »
የተመድ ዋና ጸሐፊ ፓን ኪ ሙን በቲንዱፍ ባሰሙት ንግግራቸው ወቅት ሞሮኮ በምዕራብ ሰሀራ የምታደርገውን እንቅስቃሴ «ወረራ» ያሉበት አነጋገራቸው የሞሮኮን መንግሥት እና ሕዝብ እጅግ አስቆጥቶ፣ በመዲናይቱ ራባት ግዝፍ ተቃውሞ ሰልፍ አስነስቶ ነበር።
ሞሮኮ እንዲህ ዓይነት ተቃውሞ አይታ እንደማታውቅ ነው ታዛቢዎች የገለጹት። በተቃውሞ ሰልፉ ላይ የተሳተፈው የሞሮኮ ሕዝብ፣ በይፋ ዘገባዎች መሰረት፣ ሶስት ሚልዮን ነበር። ያኔ ከተቃዋሚዎቹ መካከል አንዷ የዓለሙ መንግሥታት ድርጅት ዋና ጸሐፊ ፓን ኪ ሙን ገለልተኛ መሆን ሲገባቸው በዚሁ አነጋገራቸው ወገን ለይተዋል ስትል በአስተያየታቸው ብርቱ ቁጣ እንደተሰማት እና ምዕራባዊ ሰሀራ የሞሮኮ ግዛት መሆንዋን ለመጉላት መውጣቷን ገልጻለች። እንደ «ሞሮኮ ዎርልድ ኒውስ» የተባለው በእንግሊዝኛ ቋንቋ የሚዘጋጀው ኦንላይን ገጽ ዋና አዘጋጅ ሳሚር ቤኒስ አስተያየት፣ የዋና ጸሐፊው አስተያየት ተገቢ አልነበረም።
« „ወረራ“የሚለው ቃል ዓለም አቀፍ ሕግን፣ የተመድ አሰራርን እና የፀጥታ ጥበቃ ምክር ቤቱ ለዋና ጸሐፊ የሰጠውን ኃላፊነት ይጥሳል። »
የፓን ኪ ሙን አስተያየት ባስከተለው ቁጣ ሰበብ፣ ሞሮኮ በዚያ ከተሰማሩት 500 የ«ሚኑርዞ » አባላት መካከል ከ80 የሚበልጡትን አሁንም ማወዛገብ ከቀጠለው ምዕራባዊ ሰሀራ ግዛት አስወጥታለች፣ ለጓዱ የምትሰጠውን ድጋፍም እንደምታቋርጥ እና ከምትሳተፍባቸው ሌሎች የተመድ ተልዕኮዎችም ተሳትፎዋን ለማቋረጥ ዝታለች። ይህ የ«ሚኑርዞን» ስራ ማስተጓጎሉን የተልዕኮው በተመድ ጓድ ውስጥ በጦር ታዛቢነት የሚሰሩት ክሪስቶስ ጻጹሊስ አመልክተዋል።
« የሞሮኮ መንግሥት ለ «ሚኑርዞ» የሚያደርገው ድጋፍ ለተመድ ጓድ በጣማ ወሳኝ ነው። እና የሞሮኮ መንግሥት እንደዛተው ለ«ሚኑርዞ» የሚሰጠውን ድጋፍ ካቋረጠ የጓዱ የወደፊት ኅልውና ሊረጋገጥ ይችላል ብየ አላምንም። »
ፓን ኪ ሙን ሞሮኮ በትክክል እንዳልተረዳችላቸው በማስታወቅ ያቀረቡትን የይቅርታ ጥያቄ የሞሮኮ ንጉሥ መሀመድ ሳድሳይ አልተቀበሉትም። ይህ ዲፕሎማሲያዊ ውዝግብ ለምዕራባዊ ሰሀራ ውዝግብ ዘላቂ መፍትሔ ለማስገኘት ጥረት የጀመረውን እና የ«ሚኑርዞ»ን ተልዕኮ መቀጠል የሚፈልገውን የተመድን አዳጋች ሁኔታ ውስጥ ከመጣሉም ጎን፣ ከብዙ ዓመታት ወዲህ በአልጀርያ እና በሞሮኮ መካከል በምዕራባዊ ሰሀራ ጉዳይ የተነሳ ውስጥ ለውስጥ መብላላት የያዘውን ውዝግብ እንዳያባብስ እና ሌላ መዘዝ እንዳያስከትል ጀርመናዊው የኮንራድ አድናወር የፖለቲካ ጥናት ተቋም ተወካይ ሄልሙት ራይፌልት አሳስበዋል።
« ውዝግቡ ሽብርተኝነትን መታገሉ ላይ ትልቅ ችግር ሊደቅን ይችላል። ይህ እንዲፈጠር ሁለቱ መንግሥታት ባንድነት እንዲሰሩ ግፊት ማሳረፉ ሊታሰብበት ይገባል። »
ይሁንና፣ በወቅቱ ይህ የሚሆን አይመስልም። የኮንራድ አድናወር የፖለቲካ ጥናት ተቋም ተወካይ ሄልሙት ራይፌልት እንደሚሉት፣ በአሁኑ ጊዜ በአውሮጳ ከሞሮኮ ጋር በምዕራባዊ ሰሀራ የተነሳ መነጋገር የሚፈልግ ሀገር የለም፣
« በተለይ በወቅቱ ወደ አውሮጳ በብዛት የሚታየውን ፍልሰት ለመቆጣጠር አውሮPA በሞሮኮ ላይ ጥገኛ ናት፣ ይህንን በሚገባ የምታውቀው ሞሮኮ በአውሮጳውያኑ ላይ ግፊት ለማሳረፊያ ልትጠቀምበት ትችላለች። »
በዚህ ሁሉ መሀል ተጎጂው የምዕራብ ሰሀራ ሕዝብ ነው የሚሆነው። ዓለም አቀፉ የመብት ተሟጋች ድርጅት፣ አምነስቲ ኢንተርናሽናል ባለፈው ዓመት ብቻ በሞሮኮ እስር ቤቶች 175 የቁም ስቅል ተግባር መዝጎቦዋል። ሳህራውያን የመብት ተሟጋቾች በተል,ይ ትልቅ የመታሰር ስጋት ተደቅኖባቸዋል። እና ጀርመን ሞሮኮን አስተማማኝ ሀገር ከብላ ከመደበች መፍትሔ ያጣው የምዕራብ ሰሀራ ተወላጅ የሆኑት ሳህራውያኑ ልክ እንደሞሮኮ ተወላጆች ተገን ማግኘት አይችሉም።
አርያም ተክሌ
ማንተጋፍቶት ስለሺ