ምስራቅ ኢትዮጵያና የሂውመን ራይትስ ዎች ዘገባ
ሐሙስ፣ ግንቦት 23 2004ባለፈዉ መጋቢት ወር በተለያዩ መንደሮች የሚገኙ ኗሪዎች በተጠቀሰዉ የፖሊስ ኃይል ታፍነዉ የተወሰዱ፤ ስቃይ የተፈፀመባቸዉ እንዲሁም ንብረት የተዘረፉ መኖራቸዉን ጠቅሰዉ አቤቱታ ማሰማታቸዉን ዘርዝሯል።
«ክስተቱን መርምረናል፤ ጋሻሞ ከሚባለዉ አካባቢ የሸሹ ሰዎችንም ጠይቀናል፤ ስለሁኔታዉ አንዳንድ የአካባቢዉን አዛዉንትም ጠይቀን አጣርተናል፤ ይህ ጉዳይ በማኅበረሰቡ ዘንድ የታወቀ ጉዳይ ነዉ፤ በዩቲውብም ምስሉን የሚያሳዩ መረጃዎች አሉ የሚል እምነት አለኝ።»
ቤን ሮዉለንስ በሎንዶን የሂዉማን ራይትስ ዎች የፍቃ ዘርፍ ከፍተኛ ተመራማሪ በምስራቅ ኢትዮጵያ ሶማሌ ክልል ዉስጥ ልዩ ፖሊስ ፈፀመ ሲል ድርጅታቸዉ ስላቸወጣዉ መግለጫ ምንጭ የገለፁት ነዉ። ሮዉለንስ ቀጠሉ፤
«በአካባቢዉ አለመግባባት ተፈጥሮ ነበር፤ ልዩ ፖሊስ አንድን ግለሰብ ያዋክብ ነበር፤ የአካባቢዉ ኗሪዎች ድርጊቱን እንዲያቆሙ ለማድረግ ሲሞክሩ ሰዉየዉን ገደሉት፤ ከዚያም ራግዳ አካባቢን ለቀዉ ሄዱ፤ ከዚያም ኗሪዎቹ መሣሪያ ይዘዉ ተከታተሏቸዉና ከመካከላቸዉ ጥቂቱን ገደሉ። በሚቀጥለዉ ቀን ፖሊስ አዳዳ እና ራግዳ ከተሞች ላይ ጥቃት ሰነዘረ። በየቤቱ እየተገቡ ተጠያቂዎችን በመፈለግ የተሰኑ ሰዎች ወሰዱ። ቢያንስ 25 አስረዋል፤ አስር ያልታጠቁ ሰዎች በእስር ላይ ሳሉ ገደሉ።»
እሳቸዉ እንደሚሉት በልዩ ፖሊስ እና በአካባቢዉ ኗሪዎች መካከል በተካሄደዉ ግጭት ሌሎች ከአስር በላይ የሚሆኑ ሰዎችም ህይወት ጠፍቷል። ሂውመን ራይትስ ዎች ይህን ጉዳይ በመከታተል የመዘገበ መሆኑን በመግለፅም የጉዳዩ አሳሳቢነት ከዚህ ይነሳል ይላሉ፤
«ይህ አሳሳቢ የሚሆነትበት ምክንያት፤ ልዩ ፖሊስ ከ1999ዓ,ም ጀምሮ በአካባቢዉ ይገኛል። ነገር ግን የሚፈፅሙትን ጥቃት ለማረጋገጥ እጅግ አስቸጋሪ ሆኖ ቆይቷል። ምክንያቱም ወደኦጋዴን ለመግባት አይፈቀድም። እናም ይህ ልዩ ፖሊስ የሚፈፅመዉን የሚያሳይ አንድ መረጃ በተቀረዉ የአካባቢዉ ግዛቶች ሊኖራቸዉ የሚችለዉን ባህሪ በመጠቆሙ ስጋቱን ከፍ ያደርገዋል። ይህ ማለት ወደዚያ መግባት ሊፈቀድ ይገባል፤ የኢትዮጵያ መንግስትም ልዩ ፖሊስ የሚፈፅመዉን ማዋከብ ተመልክቶ ተጠያቂ ሊያደርገዉ ይገባል።»
ቤን ሮዉለንስ እንደሚሉት ሂዉማን ራይትስ ዎች ባደረገዉ ጥናት በተጠቀሰዉ አካባቢ የኦጋዴን ብሄራዊ ነፃነት ግንባር እንቅስቃሴ በመንግስት ተገትቷል። ወትሮ የዚህ ግንባር አባል የነበሩ ወጣቶችም በልዩ ፖሊስነት ሳይካተቱ አልቀሩም።
«ኗሪዎች እንደሚሉት ኦብነግ በአካባቢዉ የለም። ኦብነግን በመበታተን ስኬት ሳይኖር የቀረ አይመስለኝም፤ አንዳንድ ወጣቶች በልዩ ፖሊስነት ሲመለመሉ አንዳንድ የቀድሞ የኦብነግ አባላትም ወደዚያዉ ሳይካተቱ አልቀሩም።»
እሳቸዉ አሁን በዚህ አካባቢ ሳይኖር አይቀርም ያሉት የጎሳዎች ቁርቁስ ቢሆንም የተጠቀሰዉ ልዩ ፖሊስ እዚያ መገኘቱ ኗሪዎችን ከማዋከብ የዘለለ ሚና የለዉም ባይናቸዉ። ሂዉማን ራይትስ ዎች ይህን ስጋቱን ያካተተዉን ዘገባ ለኢትዮጵያ መንግስም ሆነ ለሚመለከታቸዉ አካላት አቅርቦ ይሆን? ያገኘዉስ ምላሽ፤ ቤን ሮዉለንስ፤
«አዎ አቅርበናል፤ ከሶማሌ ክልላዊ መንግስት ባለስጣናት ጋ ለመነጋገር ሞክረናል፤ የፌደራል መንግስቱን ባለስልጣናትም ለማግኘት ሞክረናል ያገኘነዉ ምላሽ ግን የለም።»
ሸዋዬ ለገሠ
ሂሩት መለሰ