1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ምሥራቅ አፍሪቃ እና የሽብርተኝነት መዘዝ

ቅዳሜ፣ ነሐሴ 28 2003

አሸባሪዎች በኒው ዮርክ እና በዋሽንግተን ወደ ሶስት ሺህ የሚጠጋ ሰው የገደሉበት ጥቃት ከጥቂት ቀናት በኋላ አስር ዓመት ይሆነዋል።

https://p.dw.com/p/Rjkr
እ.ጎ.አ 1998 በኬንያ ናዮቢ ዩኤስ አሜሪካ ኤንባሲ ላይ የደረሰው ጥቃትምስል AP

ይሁንና፡ አሸባሪዎች በሁለት አይሮፕላኖች በኒው ዮርክ በነበሩት ሁለት ሰማይ ጠቀስ የዎርልድ ትሬድ ሴንተር ህንጻዎች ላይ ገና ጥቃት ሳይሰነዝሩ ነበር ሽብርተኝነት በምሥራቅ አፍሪቃ ስር መስደድ የጀመረው። ከአስራ ሶስት ዓመታት በፊት እአአ በ 1998 ዓም ኬንያ እና ዩጋንዳ መዲኖች፡ ናይሮቢ እና ዳሬ ሰላም ባሉት የዩኤስ አሜሪካ ኤምባሲዎች ላይ አጥፍቶ ጠፊ ጥቃት መጣላቸው ይታወሳል። እንደፖለቲካ ተንታኖች አስተያየት፡ ይኸው ጥቃት በምስራቅ አፍሪቃ በህዝቡ ኑሮ ላይ አሉታዊ ተጽዕኖ አሳርፎዋል።

እአአ ነሀሴ ሰባት 1998 ዓም ትዋት ነበር ኬንያ እና ታንዛንያ በሚገኙት የዩኤስ አሜሪካ ኤምባሲዎች ላይ አጥፍቶ ጠፊዎች ጥቃት ጣሉ። በዚሁ አካባቢ በሚንቀሳቀሱት የአሸባሪው የአል ቓይዳ አባላት ባዘዙዋቸው ሁለት የአጥፍቶ ጠፊዎች ጥቃት ሁለት መቶ ሀያ አራት ሰዎች ተገድለዋል። ከነዚህም ሁለት መቶ አስራ ሶስቱ ኬንያ ውስጥ ነው። ኬንያዊቱ ዋሂሩ ካኒሁ ፍሮም ኧ ዊስፐር ስለ ሁለት የተለያዩ ሰዎች ትተርካለች፤ የመጀመሪያው ታሪክ በቦምቡ ጥቃት እናትዋ ስለተገደሉባት ታማኒ ሲያወሳ፡ ሁለተኛው ደግሞ የቅርብ ጓደኛው አሸባሪ ሆኖ ስለተገኘው አቡ ነው።
-በነዚህ ሁለት ምሳሌዎች አማካኝነት የአጥፍቶ ጠፊዎቹ ጥቃት በኬንያ ማህበረሰብ ላይ ያስከተለውን መዘዝ ለማሳየት ሞክራለች። ካሂው
« ብሄራዊ ሀዘን ሰዎችን በተለያዩ፡ ማለትም፡ በማህበራዊው፡ ኤኮኖሚያዊው እና ፖለቲካዊ ዘርፎች፡ የሚነካ ይመስለኛል። ከናይሮቢው ጥቃት በኋላ በማህበራዊው እና ባህላዊው ዘርፍ ላይ ትልቅ ለውጥ ታይቶበታል። ጥቃቱ ከመጣሉ በፊት በሀገሪቱ ያሉት የተለያየ እምነት ተከታዮች ጎን ለጎን ተስማምተው በሰላም ይኖሩ ነበር፤ ከጥቃቱ በኋላ ግን ድንገት ማህበረሰቡ ተከፋፈለ። ሙስሊሞች እንደ አሸባሪ ይታዩ ጀመር። እና ሀገሪቱ በአሁኑ ጊዜ ከዚህ አመለካከት ለመላቀቅ እየሞከረች ያለ ይመስለኛል። » በስዊድን የገተቦርግ ዩኒቨርሲቲ የምስራቅ አፍሪቃ አካባቢ የሽብርተኝነት ጉዳዮች ተመራማሪ ያን ባኽማን እንዳስረዱት፡ ሙስሊሞች የመገናኛ ብዙኃን፡ የህዝቡ፡ እንዲሁም ጸረ ሽብርተኝነት ህግ ለማውጣት የሞከሩት ፖለቲከኞች ጭምር ዒላማ ሆነዋል። ኬንያ ውስጥ በፕሬዚደንት ምዋይ ኪባኪ የተመራው ዴሞክራሲያዊ መንግስት እአአ በ 2005 ዓም መጨረሻ ስልጣን ከያዘ ከስድስት ወራት በኋላ፡ በምክር ቤት ክርክር ሳይካሄድበት እና ሲቭሉ ማህበረሰብ ሳይስማማበት ድንገት አንድ ጸረ ሽብርተኝነት ህግ ወጣ። ጠበቆች እና የመብት ተሟጋቾች ይህንኑ የህግ ረቂቅ ጨቋኝ ሲሉ ማውገዛቸው ይታወሳል። ህጉ ወደ ቀድሞው የሀገሪቱ ፕሬዚደንት ዳንየል አራፕ ሞይ አገዛዝ ዘመን ይመልሳል በሚል መከራከሪያ ሀሳብ ውድቅ ሆኖዋል። ህጉ ተቀባይነትን ቢያገኝ ኖር ለመንግስቱ የጸጥታ አውታር እና ለሀገር አስተዳደር ብዙ ስልጣን ይሰጥ ነበር። እንዲያውም አንዱ የህጉ አንቀጽ አንድ የልብስ ዓይነት የሚለብሱ ሰዎች እንዲታሰሩ ያዝ ነበር። ይህ በርግጥ በአናሳኑ የሀገሪቱ ሙስሊሞች አንጻር የተዘጋጀ ሆኖ ነበር የታየው»
ሲቭሉ ማህበረሰብ እና አንዳንድ የመብት ተሟጋቾች ተቃውሞ ካሰሙ በኋላ ህጉ ተሽሮዋል። በዚህም የተነሳ በታንዛንያ እና በዩጋንዳ አንጻር፡ ኬንያ እስከ ዛሬ ድረስ ጸረ ሽብር ህግ የላትም። ዓለም አቀፉ ማህበረሰብም በበኩሉ ስልቱን መቀየር ግድ ነበር የሆነበት፤ ያን ባኽማን
«የጦር ኃይሉን በገንዘብ መርዳቱ፡ የፖሊስ ኃይሎችን ማቋቋሙ እና ድንበሩን ጥበቃ አስተማማኝ ማድረጉ አዳጋች እየሆነ ተገኘ። ውሁዳኑን ሙስሊሞች እንደ ወንጀለኛ መመልከት ከተጀመረ በኋላ ዓለም አቀፍ ቡድኖች አሰራራቸውን መቀየር ግድ ነበር የሆነባቸው። የልማቱ ፖለቲካ ሙስሊሞችን እንደ አሸባሪ በመመልከቱ አንጻር ጣልቃ መግባት፡ የመብት ተሟጋቾች ወደብ ከተማ ሞምባሳ እና በባህሩ ጠረፍ አካባቢ ከሚኖሩት ሙስሊሞች ጋ ሆን ብለው የቅርብ ግንኙነት መፍጠር ጀመሩ። ድህነትን ለመታገል እና ሰዎችን በስራው ዓለም ውስጥ ለማዋኃድ የሚያመቻቹ ሴሚናሮች ተዘጋጁ»
በመሰረቱ የሽብርትነትን መንስዔ በተለይ ድህነትን የመታገል ዓላማ ነበር የተቀመጠው። ይሁንና፡ አሁኑ ጊዜ ዩኤስ አሜሪካ ሽብርተኝነትን ለመታገል በጦር ኃይሉ እና በስለላ ድርጅቱ ላይ አትኩራለች። ኬንያውያን እስረኞች አሜሪካውያን የጦር መኮንኖች በዩጋንዳ እና በሶማልያ በተዘጋጁ በርካታ ድብቅ እስር ቤቶች እንደመረመሩዋቸው ተናግረዋል። የዩኤስ አሜሪካ ፕሬዚደንት ባራክ ኦባማ እነዚህን በህቡዕ የተቋቋሙትን እስር ቤቶች የመዝጋት ፍላጎት ነበራቸው፤ ስልጣን ከያዙ ከሁለት ቀናት በኋላ ወህኒ ቤቶቹን እንደሚዘጉ ቃል መግባታቸው አይዘነጋም።

Bombenanschlag auf das Paradise Hotel in Mombasa
በኬንያ- ሞባሳ ሆቴል የደረሰ ጥቃትምስል AP
Anschlag auf Botschaft der USA in Dar es Salaam Tansania 1998
እ.ጎ.አ 1998 በታንዛንያ ዳሪሰላም ዩኤስ አሜሪካ ኤንባሲ ላይ የደረሰው ጥቃትምስል AP

ኦድሪ ፓርሞንትየ
አርያም ተክሌ
መስፍን መኮንን

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ