1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ማዕ/አፍሪቃ ሪፓብሊክና የአፍሪቃ ኅብረት

ሰኞ፣ መጋቢት 16 2005

ማዕከላዊት አፍሪቃ ሪፓብሊክ ውስጥ ፣ በሳምንቱ ማለቂያ ላይ የአማጽያኑ « ሴሌካ» ጥምረት፤ ከ 2 ወራት የሰላም ውል ወዲህ፤ 13 የደቡብ አፍሪቃ ወታደሮች ጭምር በተገደሉበት ቀልጣፋ የማጥቃት እርምጃ ፣ ሥልጣን ከፕሬዚዳንት ፍራንሷ ቦዚዜ መንጠቃቸው የሚታወስ ነው።

https://p.dw.com/p/18413
ሚሼል ኖንድሮኮ ጆቶጂያምስል Getty Images

የአማጽያኑ መሪ ሚሼል ጆቶዲያ ራሳቸውን ፕሬዚዳንት ብለው ለመሠየም በመዘጋጀት ላይ ሲሆኑ፤ ከአማጽያኑ እጅ ያመለጡት ፕሬዚዳንት ቮዚዜ ሸሽተው ያውንዴ ፤ ካሜሩን መግባታቸው ዛሬ ይፋ ሆኗል። የአማጽያኑን ድርጊት የተቃወመው የአፍሪቃ ኅብረት፤ በተለያ በ 7 የአማጽያኑ ጥምረት ከፍተኛ አመራር አባላት ላይ እገዳዎች ተግባራዊ እንዲሆኑ ወስኗል ።
« የአፍሪቃ ህብረት የሰላም እና ፀጥታ ምክር ቤት የሊብረቪል ውል እንዲከበር እና ሀገሪቱ የምትመራበትን የሽግግር ሁኔታ እንዲያመቻች፡ እንዲሁም፡ በሀገሪቱ ሕገ መንግሥታዊውን ሥርዓት መልሶ እንዲያረጋግጥ ያሳስባል። እንዲሁም፡ ውሳኔው በሴሌካ ስር በሚገኙ አካባቢዎች እና በሴሌካ መሪ ሚሼል ኖንድሮኮ ጆቶጂያ የጉዞ እና የንብረት ዝውውር ማዕቀብ ማሳረፍን ያጠቃልላል። »
የተመድ ዋና ፀሐፊ ፓን ኪ ሙን የዓማፅያኑን መፈንቅለ መንግሥት ርምጃ በማውገዝ፡ በከተማይቱ የቀጠለው ሁከት እና ዝርፊያ፡ እንዲሁም፡ አጠቃላዩ የሀገሪቱ የሰብዓዊ ሁኔታ እንዳሳሰባቸው ገልጸዋል።  የማዕከላይ አፍሪቃ ሬፓብሊክ መዲና ባንግዊን ትናንት የተቆጣጠረው ያማፅያኑ የሴሌካ ጥምረት መሪ ሚሼል ኖንድሮኮ ጆቶጂያ የሊብረቪሉ ውል ተግባራዊ እንደሚሆንና በሀገሪቱም በሚቀጥሉት ሦስት ዓመታት ውስጥ ምርጫ ሊደረግ እንደሚችል ለፈረንሣይ ዜና ማሠራጪያ ጣቢያ ኤር ኤፍ ኢ አስታውቀዋል። ትናንት መዲናይቱን ባንግዊን  ለመቆጣጠር ዓማፅያኑ ባካሄዱት ውጊያ በዚችው ሀገር የተሠማሩት 13 የደቡብ አፍሪቃ መንግሥት ወታደሮች መገደላቸውን የደቡብ አፍሪቃ ፕሬዚደንት ጄኮብ ዙማ ቢያስታውቁም ወታደሮቻቸውን ከዚችው ሀገር እንደማያስወጡ ገልጸዋል።  ደቡብ አፍሪቃ የማዕከላይ አፍሪቃ ሬፓብሊክ ፕሬዚደንት ፍራንስዋ ቦዚዜን መንግሥት ከዓማፅያን ጥቃት ለመከላከል ነበር ባለፈው ጥር 200 ወታደሮች ወደዚችው ሀገር የላከችው።   ከሥልጣን የተወገዱት ፕሬዚደንት ቦዚዜ ወደ ካሜሩን የያውንዴ ከተማ መግባታቸውን የካሜሩን መከላከያ ሚንስቴር ባለሥልጣን አረጋግጠዋል። ከሰሜኑ በማዕከላይ አፍሪቃ ሬፓብሊክ መንግሥት አንፃር የተዋጉት ዓማፅያን ባለፈው ታህሳስ ወር ያካሄዱት ዓመፅ ያበቃው በጋቦን ሸምጋይነት በመዲናይቱ ሊብረቪል ባለፈው ጥር ወር ከመንግሥቱ ጋ የስልጣን መጋራት ውል ከፈረሙ በኋላ ነበር።  በዚሁ ውል መሠረት፡ ከዓማፅያኑ፡ ከሲቪል የተቃዋሚ ፓርቲዎች ተወካዮች እና የፕሬዚደንት ቦዚዜ ታማኞች የተውጣጣ በጠቅላይ ሚንስትር ኒኮላ ቲያንጋይ የሚመራ መንግሥት ተቋቁሞ ነበር። ይሁንና፡ ፕሬዚደንት ቦዚዜ ውሉን አላካበሩም በሚል በመውቀስ ዓመፃቸውን ቀጥለው ትናንት መዲናይቱን መቆጣጠር ተሳክቶላቸዋል።

25.03.2013 karte zentralafrikanische republik spa
Zentralafrikanische Republik Seleka Rebellen
ምስል AFP/Getty Images


ጌታቸው ተድላ ኃ/ጊዮርጊስ

ተክሌ የኋላ

ነጋሽ መሀመድ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ