ማብቂያ ያጣው የአፍሪቃ መሪዎች የስልጣን ጥም
ሁለት የስልጣን ዘመናት ለበርካታ የአፍሪቃ መሪዎች በቂ አይደለም። ስለሆነም የስልጣን ጊዜያቸውን ለማራዘም ማንኛውንም መንገድ ይጠቀማሉ። የትኞቹ መሪዎች የትኛውን መንገድ እንደተጠቀሙ ፤ ከስር ተዘርዝሯል።
ሮበርት ሙጋቤ - ዚምባዌ
ሮበርት ሙጋቤ በ 90 ዓመታቸው ፤ ከአፍሪቃ በእድሜ የገፉት መሪ ናቸው። እኢአ በ1980 ዓም የዝምባዌ ፕሬዚዳንት ሆነው ሲመረጡ ትልቅ ተስፋ ተጥሎባቸው ነበር። ይሁንና በሀገሪቷ ከፍተኛው የፋይናንስ እና የምግብ እጦት ቀውስ ተከሰተ። ባለፈው ዓመት ሙጋቤ የአንድ መሪ የስልጣን ዘመን ለአምስት ዓመታት ቢበዛ ሁለት ጊዜ እንዲመረጥ ገደብ ጣሉ። ይሁንና ይህ ገደብ ያለፉትን ዓመታት አይመለከትም። ስለሆነም ሙጋቤ እስከ 97 ዓመታቸው ሀገሪቷን ሊመሩ ይችላሉ።
ቴዎድሮ ኦቢያንግ - ኤኻቶሪያል ጊኒ
እንደ ኦቢያንግ እስካሁን አፍሪቃ ውስጥ ለረዥም ዓመታት የመራ መሪ የለም። እኢአ 1979 ዓም ነበር የዛሬው 72 ዓመት አዛውንት በነዳጅ ዘይት ሀብታም የሆነችውን የኤኻቶሪያል ጊኒ ስልጣን የተቆናጠጡት። ሥልጣን ከያዙ ከ10 ዓመታት በኋላም ህዝቡ በነፃ ምርጫ ለፕሬዚዳንትነት መረጣቸው። ኦቢያንግ 3 ጊዜ ህገ መንግሥቱን በህዝበ ውሳኔ ለውጠዋል። በዚህም ሕግ መሰረት ለአንድ መሪ ሁለት ባለ 7 ዓመት የስልጣን ዘመን ብቻ ይፈቅዳል። ከዚህም ሌላ የአንድ መሪ እድሜን በፊት ከነበረበት ወደ 75 ዓመት ከፍ አድርጓል። የኦቢያንግ የስልጣን ዘመን እኢአ 2016 ያበቃል። ስለ ማቆም ግን ምንም ወሬ የለም።
ሆዜ ኤድዋርዶ ዶስ ሳንቶሽ -አንጎላ
የአንጎላው መሪ በእድሜ ከኦቢያንግ ሁለት ወር ያንሳሉ። እኝኛውም ስልጣን ከጨበጡ 35 ዓመት አልፏቸዋል። ለመጀመሪያ ጊዜ ህገ መንግሥቱ ተገግባራዊ ከሆነ በኋላ የተመረጡት ግን ገና እኢአ በ2012 ዓ ም ነው። በ 2010ሩ ህገ መንግሥት መሰረት አብዛኛውን ድምፅ ያገኘው የፓሪቲ ሊቀመንበር የሀገሪቱ ፕሬዚዳንት ይሆናል። የአንጎላ ጠንካራ ፓርቲ አሁንም የዶስ ሳንቶሽ MPLA ፓርቲ ስለሆነ የ 72 ዓመቱ መሪ አሁንም ለተወሰኑ ዓመታት ስልጣን ላይ የመቆየት እድል አላቸው።
ዮዌሪ ሙሴቬኒ -ዩጋንዳ
እኢአ በ 1986 ሙሴቬኒ አምባገነን የሚሉትን የአቦቴን ስርዓት ገርስሰው ስልጣን ያዙ። በአምባ ገነንነቱም ቀጠሉበት። ህገ መንግሥቱን እየቀየሩ ላለፉት 28 ዓመታት ስልጣን ላይ ናቸው። ሙሴቬኒ « አንደኛውም የአፍሪቃ መሪ ከ10 ዓመት በላይ ስልጣን ላይ መቆየት የለበትም» ቢሉም እኢአ በ 2005 ዓ ም የስልጣን ማብቂያ ጊዜውን ገደብ የለሽ አድርገውታል።
ኢድሪስ ዴቤይ- ቻድ
እኢአ በ1952 ዓ ም የተወለዱት ኢድሪስ ዴቤይ ፖለቲካን የጀመሩት የአማፅያን አባል ሆነው ነው። በ1990ዎቹ መጨረሻ የቀድሞው የጦር ባልደረባቸውን ሂሰኔ ሀብሬን አስወግደው በ1991 የቻድ ፕሬዚዳንት ሆኑ። ስልጣን ላይ ለመቆየትም በ 2004 ዓም ህገ መንግሥቱን አስቀየሩ። በ 2006 እና በ2008 ዓም እሳቸውን ከስልጣን ለማውረድ የተደረጉ የአማፂያን ሙከራ አክሽፈዋል። ከዛም በ2011 ዓም 4ኛውን የስልጣን ዘመናቸው ተጀመረ።
ፓውል ቢያ - ካሜሮን
እኢአ ከ 1982 ዓም አንስቶ ፓውል ቢያ ምዕራብ አፍሪቃዊቷን ሀገር ካሜሮንን ይመራሉ። በህገ መንግሥቱ መሰረት ከ 2011 ዓ ም ጀምሮ ዳግም ለምርጫ መቅረብ አይችሉም ነበር። ስለሆነም አስቀድመው 2008 ዓ ም ህገ መንግሥቱን አስቀየሩ። የህዝቡ ጩኸት እና ተቃውሞ አልተሰማም። ስለሆነም የቢያ በ 2011 ዓም ዳግም መመረጥ ብዙም አላነጋገረም። ተቃዋሚዎች እና የምርጫ ታዛቢዎች ግን መጭበርበር እንደነበር ይገልፃሉ።
ጆሴብ ካቢላ- ኮንጎ ዶሞክራቲክ ሪፖብሊክ
ካቢላ ከሌሎች አቻቸው ጋር ሲነፃፀሩ ወጣት ሊባሉ ይችላሉ። የ 43 ዓመቱ መሪ ስልጣን የጨበጡት እኢአ በ2001 ዓ ም ሲሆን ይህም አባታቸውን ተክተው ነው። አባታቸው ሎራ ዲሴሬ ካቢላ በአንድ አንጋቻቸው ሲገደሉ ፤ ልጃቸው ጊዜያዊ ፕሬዚዳንት ሆነው ተሾሙ። ይሁንና ካቢላ ስልጣኑን ማስረከብ አልፈለጉም። በሌላ በኩል የፕሬዚዳንቱን የስልጣን ጊዜ ለ5 ዓመታት በሁለት ጊዜ ምርጫ እንዲገደብ እና የሕገ መንግሥት እንዲለወጥ ጠይቀዋል።
ዴኒስ ሳሶ ንጉሶ- ኮንጎ
ግትር አቋም አላቸው። እኢአ 1979 ዓም ስልጣን የያዙት ንጉሶ በ1992 በነፃው ምርጫ ተሸንፈዋል። ከዛም ለ 5 ዓመታት ውጭ ሀገር ከቆዩ በኋላ ተመልሰው አገራቸው በመግባት በኃይል ስልጣኑን ተረክበዋል። የ 2002ቱ ህገ መንግሥት የአንድ መሪን የእድሜ ገደብ ቢበዛ 70 ዓመት ላይ ይደነግጋል። በዚህ መሰረት የ 69 ዓመቱ ንጉሶ በ 2016ቱ ምርጫ መሳተፍ አይችሉም። በርግጥ ህጉን ማክበራቸው ግን አጠያያቂ ነው።
ብሌዝ ኮምፓኦሬ
« ይበቃል።» ሲሉ ነበር አደባባይ የወጡት የቡርኪናፋሶ ሰልፈኞች ሰሞኑን የገለፁት። ህገ መንግሥቱን ለመቀየር የፈለጉት ኮምፖኦሬ ህዝቡ እድል አልሰጣቸውም። በዚህ ወር ከስልጣን ወርደዋል። የ 63 ዓመቱ ኮምፖኦሬ እኢአ በ1987 ዓ ም ነው በመፈንቅለ መንግሥት ስልጣን ለመጀመሪያ ጊዜ የያዙት። ከ4 ዓመታት በኋላ በሀገሪቱ የመጀመሪያው ምርጫ ተካሄደ ፤ ከዛን ጊዜ አንስቶ ኮምፓኦሬ ሁሌም ምርጫ እንዳሸነፉ ነው። በ 2000 ዓም ህገ መንግሥቱን ቀይረውም ሁለት ጊዜ የስልጣን ጊዜያቸውን አራዘሙ። እቅዳቸው ግን ባሁኑ አልተሳካም።
ምዋቲ ሳልሳዊ- ስዋዚላንድ
ንጉሱ ያለ ምንም ህገ መንግሥት ለውጥ ነው የመሩት። ለምን ቢባል በስዋዚላንድ ጨርሶ ህገ መንግሥት ስለሌለ። ምዋቲ ሳልሳዊ የአፍሪቃ ብቸኛ ንጉስ ተደርገው ይቆጠራሉ። እኢአ 1986 ከአባታቸው ሶባሁዛ 2ኛ ስልጣኑን ተረክበዋል። ከዚያን ጊዜ ጀምሮ ያለ ምንም የዲሞክራሲ መመሪያ ሀገሪቷን እየመሩ ይገኛሉ። ስዋዚላንድ ከዓለም ድሆች ሀገር አንዷ ናት። ከህዝቧ 26% የኤድስ በሽተኛ ነው።