ማርቲን ሹልስ ለሶሻል ዴሞክራት ፓርቲ መሪነት በሙሉ ድጋፍ ተመረጡ
ሰኞ፣ መጋቢት 11 2009ማስታወቂያ
የአዉሮጳ ኅብረት ምክር ቤት ፕሬዝደንት በመሆን ያገለገሉት የ61 ዓመቱ ሹልስ፤ ግራ ዘመሙን ሶሻል ዴሞክራት ፓርቲ ለመምራት የአባላቱን መቶ በመቶ ድምጽ ያገኙ የመጀመሪያዉ ፖለቲከኛ መሆናቸዉ ተነግሯል። የፓርቲዉ ጉባኤ በተካሄደባት በርሊን ከ600 ለሚበልጡ የፓርቲዉ ተወካዮች ባደረጉት ንግግር «ፍትህ፣ አክብሮት እና ክብር» የፓርቲያቸዉ የምርጫ ቅስቀሳ መርህ እንደሚሆን ገልጸዋል።
«ማኅበራዊ ፍትህ ከመደብ ትግል መማሪያ መጽሐፍት ላይ የሚገኝ አስተሳሰብ አይደለም፤ ይልቁንም ለሁሉም የጋራ እድል የተሰጠና መከበር የሚገባዉ የአንድ ነፃና እና ወደፊት የተራመደ ማኅበረሰብ መሠረታዊ ሁኔታ ነዉ።»
ሹልስ ፓርቲዉን ወክለዉ ሜርክልን እንደሚፎካከሩ ይፋ ካደረጉበት ጊዜ አንስቶ ሶሻል ዴሞክራት ፓርቲ በሕዝብ አስተያየት መመዘኛዎች የ30 በመቶ የድጋፍ ድምጽ ጭማሪ አሳይቷል። ከአዉሮጳ ኅብረት ኃላፊነታቸዉን አጠናቀዉ ወደሀገራቸዉ ከተመለሱ ወዲህም በተለያዩ የጀርመን ግዛቶች በመገኘት የህዝቡን ፍላጎት ለመረዳት ኅብረተሰቡን ማነጋገራቸዉ ተነግሯል። ማርቲን ሹልዝ ከአሜሪካዉ ፕሬዝደንት ዶናልድ ትራምፕ የምርጫ ቅስቀሳ የተቀሰመዉን ትምህርት መሠረት በማድረግም «አንድ ህዝብ እንዳለ ማዉገዝ በጀርመን ቦታ የለዉም።» ማለታቸዉም ተገልጿል።
ሸዋዬ ለገሠ
አዜብ ታደሰ