መንግሥት ማኅበራዊ ሚዲያዎችን መቆለፉ
ሰኞ፣ ሐምሌ 4 2008
ዛሬ መሰጠት የተጀመረዉ ብሔራዊ ፈተና ደግሞ ሾልኮ እንዳይሰራጭ በሚል ካሳለፍነዉ ቅዳሜ ጀምሮ መንግስት ፌስቡክ፣ትዊቴር፣ ኢንስታግራምና ቫይበር ማኅበራዊ የመረጃና የመገናኛ ዘዴዎችን መቆለፉ ተዘግቦአል። ይህ እስከ ረቡዕ እንደሚዘልቅና ርምጃዉ የተማሪዎችን ሥነ-ልቦና እንዳይረበሽ ለፈተናዉ እንዲዘጋጁ ታስቦ መሆኑን የኢትዮጵያ መንግሥት ቃል-አቀባይ አቶ ጌታቸዉ ረዳ እንደ ምክንያት ለ«AFP» በሰጡት ቃለ-ምልልስ ተናግረዋል።
ኢትዮጵያ ዉስጥ ማኅበራዊ ሚድያን ለሰብዓዊ መብት ማራማጃ የሚጠቀምበት የዞን ዘጠኝ ጻሕፍት አባል በፍቃዱ ኃይሉ ጉዳዩን ሲሰማ ማዘኑን ገልፆአል።
መንግስት የወሰደዉ ርምጃ ምንም የሕግ ማዕቀፍ እንደሌለዉ የሚናገረዉ በፍቃዱ የተማሪዎቹን ሥነ-ልቦና መጠበቅ ነዉ ተብሎ ከተወሰደዉ ርምጃ ጋር የማይገናኝ መሆኑን ተናግሮአል። በኢትዮጵያ ቴሌኮም በኩል ያለዉ በሙሉ ጭፍን ትያትር ነዉ ብዬ እወስዳለሁም ብሏል። በፍቃዱ የኢንተርኔት ተደራሽነት በጣም ደካማ በሆነበት አገር በኢትዮጵያ ማኅበራዊ ሚድያ ለመንግስት አደጋ መሆኑን መንግስት መረዳቱን ተናግሯል። ማኅበራዊ ሚድያ ላይ የሚወጡ ጉዳዩች የአስተዳደራቸዉ ድክምት መሆኑንምን የመንግስት ኃላፊዎች ሊረዱ አልቻሉም እናም መንግስት የህዝቡን ብሶት አልተረዳም ሲል አክሎአል።
ይህን ጉዳይ በተመለከተ በዶይቼ ቬሌ የፌስቡክ ድረገጽ ላይ አስተያየታቸዉን በድምፅ የሰጡንም አሉ። የአፋር ክልል ነዋሪ የሆኑት መሃመድ አዋል መኅበራዊ ሚድያን በመከልከላቸዉ ታፍነናል እናም ማኅበረሰቡ ተበሳጭተዋል ብለዋል።
የዶይቼ ቬለ ተከታታይ ጉተማ ቴስፋዬ በበኩላቸዉ መንግስት የወሰደዉ ርምጃ በከፊልም ቢሆን ተገቢ ነዉ ይላሉ።
ሌሎች አስተያየታቸዉን የሰጡን የዶይቼ ቬለ ተከታታዮች «የኢትዮጵያ መንግሥት የትኛውም የሕግ ማዕቀፍ የፈለገውን ከማድረግ አይገታውም፣ እራሱ ያወጣውን ሕግ እንኳን አያከብርም»፣ እናም ማኅበራዊ የሚድያ መንግስት መዝጋቱ ሌላ አማራጭ ስላጣ ነዉ እንጂ የተማሪዎች ሥነ-ልቦና ለመጠበቅ መፍቴ አይሆንም ስሉ አስተያየታቸዉን ሰጥተዉናል።
መርጋ ዮናስ
አዜብ ታደሰ