1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ሕመም ማስታገሻና የራስ ምታት

ማክሰኞ፣ መስከረም 29 2005

መድሐኒት የሚወሰደዉ ከህመም ለመዳን እንደሚሆን ይታመናል። ተገቢዉን የሃኪም ትዕዛዝ በተከተለ አወሳሰድ ማለት ነዉ። ሰሞኑን ለህመም ማስታገሻነት የሚወሰዱ መድሃኒቶች ለራስ ምታት መነሻ ምክንያት እንደሚሆኑ አንዳንዶቹም ጥንቃቄ እንደሚያስፈልጋቸዉ የሚያሳስቡ መረጃዎች እየወጡ ነዉ።

https://p.dw.com/p/16N3P
ምስል Fotolia/Laurin Rinder

መረጃዎች እንደሚጠቁሙት ከ200 በላይ የራስ ምታት አይነቶች አሉ፤  ዋናዎቹና ሃኪሞች ጠቅለል አድርገዉ የሚመለከቷቸዉ ሶስት ሲሆን አንደኛዉ አዘዉትሮ አብዛኛዉን ሰዉ ሊያጋጥም የሚችለዉ የራስ ምታት አይነት ፤ ዉጥረት ያለበት ራስ ምታት ሲሆን ይህ አብዛኛዉ ሰዉ በወር ዉስጥ አብዛኛዉን ጊዜ ሊያመዉ እንደሚችል መረጃዎች ይጠቁማሉ፤ ሁለተኛዉ ሚጊሬይን የሚባለዉ ኃይለኛ የራስ ምታት ዓይነት ነዉ፤ ይህ የራስ ምታት ዓይነት ሲብስም እስከማስመለስ እንደሚደርስ ነዉ የሚገለፀዉ፤ ሌላኛዉ በህክምናዉ ክላስተር ተብሎ የሚገለፀዉ ሲሆን ከባድ ህመምን አይንና በፊት ገፅላይ ሁሉ ያስከትላል፤ አንዳንዴም እብጠት ሊኖር ይችላል፤

08.07.2009 DW-TV Fit und Gesund Kopfschmerz 2

በአራተኛ ደረጃ ሃኪሞች የጠቀሱት የራስ ምታት ዓይነት ዉጥረት ያለበት ራስምታት ዓይነት ወይም የሚግሬይን አይነት ሊሆን ይችላል ነገር ግን ሰዎች በርከት ያለ የህመም ማስታገሻ በመዉሰዳቸዉ የሚመጣ ራስ ምታት ነዉ።

የዓለም የጤና ድርጅት በበኩሉ የራስ ህመም በአብዛኛዉ ከነርቭ ስርዓት መታወክ ጋ የሚገናኝበት ሁኔታ እንደሚያመዝን ይጠቁማል። እንዲያም ሆኖ በርካታ ህዝብን የሚያሰቃየዉ የራስ ምታት መነሻዉ እንዳልተጠናነዉ የድርጅቱ መረጃ የሚያስረዳዉ። BBC ያነጋገራቸዉ አንድ የህክምና ባለሙያ እንደዉም የራስ ምታትን መንስኤ በትክክል ባዉቀዉ ኖሮ ይሄኔ አሁን ከአንድ የባህር ዳር ተዝናንቼ ቁጭብዬ ታገኘን ነበር በማለት ስለመንስኤዉ ለጠየቃቸዉ ጋዜጠኛ የችግሩን ሥርመሠረት ለማግኘት እንዳዳገታቸዉ ጠቁመዋል። ዶክተር ብሬን ሆብ በጥቅሉ ስለራስምታት ያለዉን ሁኔታ ሲገልፁ፤

«የራስምታት አስቸጋሪነት እጅግ ዓለም ዓቀፋዊ የሆነ ምልክት ማሳየቱ ነዉ፤ ጉዳዩ ከሰዎች አካላዊ፤ ማኅበራዊ ስነልቦናዊ ጤና ይዞታ በጥቅሉ ለራስምታት አስተዋፅኦ አላቸዉ። ይህን ከግምት ማስገባት ይኖርብናል። ሌላዉ ዜና ደግሞ አብዛኞቹ የራስ ምታት አይነቶች ለመዳን የሚችሉ፤ አብዛኞቹም እጅግም የማያሳስቡ መሆናቸዉ ነዉ። »

መረጃዎች እንደሚሉት ሰፊ ጥናት የተደረገበት ሚግሬን በመባል የሚታወቀዉ ከጭንቅላት አንድ ወገን ከፍሎ ክፉኛ የሚያሰቃየዉ የራስ ምታት ዓይነት ነዉ።

ይህ ኃይለኛ የራስ ህመም ታማሚዉ ከድምፅ እና ብርሃን ራሱን እንዲሰዉር ግድ ብሎ አንዳንዴም የሚያስመልስበት አጋጣሚ ይኖራል።  ጥናቶች እንደሚጠቁሙት ይህ ዓይነቱ የራስ ምታት አብዛኛዉን ጊዜ የሚያጠቃዉ ከወንዶች ይልቅ ሴቶችን ነዉ።

Mann mit Depressionen
ምስል Bilderbox

ሌላዉ የራስ ምታት ዓይነት ደግሞ በኃይለኛ ትኩሳት ምክንያት የሚከሰት ነዉ። የራስ ህመምን በአራት መደቦች ከፍሎ የሚገልፀዉ ጥናት የዉጥረት ራስምታት የሚለዉ ዓይነት ባደጉት ሀገሮች ደግሞ  ¾ኛዉን ወንዶችና 80 በመቶ የሚሆኑትን ሴቶች እንደሚያሰቃይ ያመለክታል። ይኸዉ የራስ ምታት በየዕለቱ ከ20ሰዎች አንዱን እንደሚያሰቃይም ተገልጿል። ብሪታኒያ ዉስጥ የህመም ማስታገሻ መድሐኒት የሚወስዱና ሃኪሞች መከላከል ይቻላል ባሉት የራስ ህመም የሚሰቃዩት ወገኖች በሚሊየን እንደሚቆጠሩ ሰሞኑን ይፋ ሆኗል።

Teller Messer Gabel Besteck Pillen Medikamente
ምስል Fotolia

ይህ አስመልክቶ BBC ያነጋገራቸዉ ሃኪም ዶክተር ብሬን ሆፕ በአንድ ወር ዉስጥ ከ15ቀናት በላይ በተከታታይ የህመም ማስታገሻ የወሰዱ ሰዎች መድሐኒት ከመጠን በላይ በመዉሰድ ሊከተል ለሚከሰተዉ የራስ ምታት አይነት ይዳረጋሉ ይላሉ።

«ለመናገር የሞከርነዉ የህመም ማስታገሻ መዉሰድ የጀመሩ ሰዎች መድሃኒቱት መዋጣቸዉን ከቀጠሉ፤ ለምሳሌ ሚግሬን የሚያሰቃያቸዉ ሰዎች የህመም ማስታገሻ እናዝላቸዉና መዉሰድ ይጀምራሉ፤ መድሃኒቱን የሙጥኝ በማለት የህይወታቸዉ አንዱ አካል አድርገዉ ግማሹን ወር መዉሰዳቸዉ ከቀጠሉ ያኔ ነዉ መድሃኒት ከመጠን በላይ በመዉሰድ ለሚመጣዉ የራስምታት በሽታ የሚጋለጡት።»=

ሸዋዬ ለገሠ

አርያም ተክሌ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ