ፍራንሲስ በቅዱስ ጴጥሮስ አደባባይ የሰላም መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል
እሑድ፣ ሚያዝያ 8 2009“በተለይ በእነዚህ ቀናት” አሉ ፍራንሲስ “በሶሪያ ሞት እና ሽብርን ባነገሰው ጦርነት ለሰላማዊ ዜጎች መጽናናት እና እርዳታን ለማምጣት በትጋት ለሚሰሩ ጌታ ጥረታቸውን ይደግፍ” ሲሉ መልካም ምኞታቸውን ገልጸዋል፡፡ ፍራንሲስ በትናንትናው ዕለትም በአሌፖ ቢያንስ 126 ሰዎች ያለቁበትን የቦምብ ፍንዳታም አውግዘዋል፡፡
ከዚህ ሌላ ሊቀ-ጳጳስ ፍራንሲስ በሌሎች በጦርነት በተጎሳቆሉ ሀገራት ሰላም እንዲሰፍን ጥሪ አቅርበዋል፡፡ የትውልድ ሀገራቸው በምትገኝበት ደቡብ አሜሪካ ለውይይት እና ዲሞክራሲ የሚደረገውን ጥረት ደግፈዋል፡፡ በሽብር፣ በጦርነት፣ በረሃብ የተጎዱትን እና በጨቋኝ አገዛዝ ስር የሚማቅቁ ሰዎችን አስታውሰዋል፡፡ ደቡብ ሱዳን፣ሱዳን፣ ሶማሊያ እና ዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ያለውንም ችግር በአጽንኦት አንስተዋል፡፡
ከሮማ ካቶሊካውያን እና ፕሮቴስታንቶች በተለየ የፋሲካ በዓልን ዘግይተው ያከብሩ የነበሩ የኦርቶዶክስ ክርስቲያኖችም በዚህ ዓመት በተመሳሳይ ቀን የእየሱስ ክርሰቶስ ትንሳኤ በዓልን እያከበሩ ይገኛል፡፡ በርካታ የኦርቶዶክስ ምዕመናን ባሉባት ሩሲያ ፕሬዝዳንት ቭላዲሚር ፑቲን እና ጠቅላይ ሚኒስትር ዲሜትሪ ሜድቬዴቭ የተገኙበት የጸሎት ስነ-ስርዓት ትላንት አኩለ ሌሊት ላይ ሞስኮ በሚገኝ ካቴድራል ተካሄዷል፡፡
ከሳምንት በፊት በሁለት ቤተክርስቲያኖች በፈነዱ ቦምቦች 45 ሰዎች የሞቱባቸው የግብጽ የኮፕት ኦርቶዶክስ ክርስቲያኖችም በጥብቅ የጸጥታ ቁጥጥር ስር ሆነው የቅዳሜ ሌሊት ሥነ-ስርዓትን አካሂደዋል፡፡በሮማንያ፣ ሰርቢያ እና ሌሎች የምስራቅ አውሮፓ ሀገራት ያሉ የኦርቶዶክስ ሃይማኖት ተከታዮችም በዓሉን በደመቅ ሁኔታ አክብረዋል፡፡
ተስፋለም ወልደየስ
ልደት አበበ