1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ለወባ ክትባት ምርምር

ማክሰኞ፣ ነሐሴ 21 2005

በጎርጎሪዮሳዊዉ 2010ዓ,ም በዓለም ዙሪያ በወባ በሽታ 660 ሺ ሰዎች ማለቃቸዉን የዓለም የጤና ድርጅት ያመለክታል። ከእነዚህ መካከል አብዛኛዎቹ ማለትም 90 በመቶ የሚሆኑት የሚገኙት ደግሞ አፍሪቃ ዉስጥ ነዉ። የዛሬ ሶስት ዓመት በወባ በሽታ 220 ሚሊዮን ሰዎች ተይዘዉ እንደነበር የዓለም የጤና ድርጅት መረጃዎች ያመለክታሉ።

https://p.dw.com/p/19WOv
ምስል picture-alliance/dpa

ላለፉት ሁለት ዓመታት አንድ የአሜሪካኑ ኩባንያ ሳናሪያ አንድ ክትባት ለመድሃኒቱ ሙከራ ፈቃደኛ የሆኑ ሰዎችን ከወባ በሽታ ለመከላከል መርዳቱን ይገልጻል። በጥቂት ፈቃደና ሰዎች ላይ ሲሞክር መቆየቱ የተነገረዉ የወባ በሽታ መከላከያ ክትባት የኩባንያዉ ዋና ተመራማሪ ስቴፈን ሆፍማን እንደሚሉት ለጋ የወባ በሽታ ተህዋሲያንን የያዘ ነዉ። ተመራማሪዉ ለሙከራ የተዘጋጀዉ ክትባት PfSPZ እንደሚባልን ለጋዎቹም የበሽታዉ ተህዋሲያን ለህመም የማያጋልጡ መሆናቸዉንም ያስረዳሉ። ለምርምር የተባበሩት ፈቃደኞቹ ሰዎች ክትባቱን በየአንድ ወር ልዩነቶች እንዲወስዱ ተደረገ። መድሃኒቱም ለክትባቱ ሙከራ ከተባበሩት ብዙሃኑን ከበሽታዉ መከላከሉን አሳየ። በዚህም ተመራማሪዎቹ ተስፋ ሰጪ ዉጤት እያዩን ነዉ ይላሉ። በርሊን የሚገኘዉ የማክስ ፕላንክ ተቋም ተመራማሪ ዶክተር ካይ ማቱሼቭስኪ በበኩላቸዉ ያን ያህል ከፍተኛ የሚባል ዉጤት እንዳልተገኘ ያመለክታሉ፤

«ይህ ያን ያህል ትልቅ የሚባል ዉጤት አይደለም ሆኖም ግን ወደተሻለ ዉጤት ግን እየቀረበዉ በእርግጠኝነት ማለት ይቻላል።»

Malaria Impfung Afrika Kenia
የወባ መከላከያ ክትባት ኬንያምስል AP

እንዲያም ሆኖ የሜሪላንዱ የክትባት ምርምር ማዕከል የወባ ተህዋስያንን በክትባት መልክ ወደደምስር እያስገባ ያካሄደዉ ሙከራ በቴክኒዎሎጂዉ ረገድ መሻሻል ያሳየ አንድ ርምጃ መሆኑንም ያስረዳሉ፤

«ይኸዉ ተመሳሳይ ክትባት ከሁለት ዓመታት በፊት አንዴ ተሞክሯል፤ ይህም አንድ ሰዉ ክትባቱን በቆዳዉ ወይም በጡንቻዉ ላይ ቢወስድ ዉጤት እንደማይኖረዉ አሳይቷል። ያም እጅግ የሚያሳቅቅ ሁኔታ ነበር። እንዲህ ባለ ከፍተኛ ክትባት ለበሽታዉ መከላከያ እናበጃለን የሚል ተስፋ ሁሉም ነበረዉ።»

ዶክተሩ በጠቀሱት ምርምር በወቅቱ 44 ፈቃደኞች ክትባቱ ቆዳቸዉ ዉስጥ እንዲገባ ቢደረግም ህክምናዉ ሁለቱን ብቻ ነዉ ከወባ ማዳኑን ያሳየዉ። አዲሱ ግኝት ግን በእርግጥም ለምርምሩ በፈቃደኝነት ከተሳተፉት ብዙሃኑን ከወባ በሽታ መታደጉን አሳይቷል። ክትባቱ ግን በቀጥታ ወደደምስር መግባት ይኖርበታል እንደእነሱ ገለጻ። በአሜሪካዉ የወባ በሽታ ክትባት ምርምር ታማሚዎቹ አደገኛ የሚባለዉን የወባ ተህዋሲ ነዉ እንዲወጉ የተደረገዉ። ስልቱ እሾህን በእሾህ ዓይነት ነዉ። ይህ ዓይነቱ ህክምና አዲስ ሳይሆን ከ1970ዎቹ ጀምሮ የሚታወቅ ነዉ፤ በትንኟ ደጋግመዉ እየተነከሱ ሰዎች በራሳቸዉ ሰዉነት ዉስጥ ወባ በሽታን የሚከላከል አቅም እንዲያዳብሩ ማድረግ። ይህ እንዴት ይሆናል? ወደሁለት መቶ የሚገመቱ የወባ ትንኞች ክዳን ባለዉ አንድ ማጠራቀሚያ ይከተታሉ፤ ዶክተር ማቱሽቪስኪ ሂደቱን እንዲህ ያስረዳሉ፤

«እዚያ ላይ አንድ ሰዉ ክንዱን ያሳርፋል፤ በእርግጥ ያማል፤ ከዚያም አንድ ወር ይቆያል። ከዚያም ማሳከኩ ይቀርና ይድናል። እንደገማ ያንኑ በድጋሚ ያደርጋል። አምስት ጊዜ መደጋገም ከተቻለ ቢያንስ አንድ ሺህ የትንኟ ንክሻ ይኖራል ማለት ነዉ። አሁን እንደዉም ይህ ስልት በጣም ቀልሎ የቀረበ ዓይነት ነዉ።»

Warten auf Malaria Test in Maputo
ለምርመራ ተራ ጥበቃምስል AP

የሜሪላንዱ የቅርቡ የክትባት ምርምር ተመሳሳይ ስልት ነዉ የተጠቀመዉ። ሂደቱም ቢሆን አጭር የሚባል አልነበረም። የመጀመሪያዉ ደረጃ ምርምር 57 ሰዎችን ያካተተ ነበር፤ አንዳቸዉም በወባ በሽታ አለመያዛቸዉ ታይቷል።

በሌላ በኩል 40 ፈቃደኞች ከፍተኛ የክትባት መጠን ሲወስዱ መቆየታቸዉ ሲገለጽ ከመካከላቸዉ 17ቱ አለመታመማቸዉ ተገልጿል። መጠኑ ከፍ ባለ ቁጥርም ለሰዉነት የሚፈጥረዉ የመከላከል አቅም ከፍተኛ መሆኑ ቢታይም ሙከራዉ ቀላል እንዳልሆነ የሞቃት አካባቢ በሽታዎች ምርምር በርናንድ ኖኽት ተቋም ባልደረባ ሮልፍ ሆርትማን ያስረዳሉ፤

«የወባ በሽታዉ ተህዋሲ ወባን ከምታስተላልፈዉ ትንኝ ምራቅ ማመንጫ እጢ ይወሰዳል። ይህም ማለት፤ ትንኞቹ በወባ በሽታ የተበከለ ደም እንዲመጡ ይደረጋል፤ ከዚያም ትንኞቹ ዉስጥ በሽታዉ እየተስፋፋ ይሄድና የበሽታዉ ተህዋሲ ይፈጠራል። የተፈጠረዉ የወባዉ ተህዋሲ ከተዘጋጀ በኋላም ለጨረር እንዲጋለጥ ተደርጎ መልሶ በመርፌ ይሰጣል።»

በአንድ ክትባት ዉስጥ እስከ 135 ሺህ ተህዋሲያን ሊገኙ እንደሚችሉ ነዉ የተገለጸዉ። በይፋ እንደሚታወቀዉ እስከዛሬ በዓለም ገበያ ላይ በየዓመቱ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ሰዎችን የሚያጠቃዉን የወባ በሽታ ለመከላከል የሚዉል ክትባት የለም። ከተለያዩ አካባቢዎች ግን አሁንም ወባ በሽታን ሊከላከሉ ያስችላሉ የተባሉ የክትባት ሙከራዎች ይካሄዳሉ። ባለፈዉ ዓመት የተነገረለት አንድ የክትባት ምርምር ሶስተኛ ደረጃ ላይ ሲደርስ በፈቃደኝነት በምርምሩ ከተሳተፉት 31 በመቶዉን ከወባ በሽታ ማትረፉ ተነግሮለታል። ይህን ምርምር ያካሄደዉ ኩባንያ ያዘጋጀዉ መድሃኒት ቢያንስ ከስድስ እስከ አስር ወራት ያህል በወባ ከመያዝ ያድናል ሲል አፉን ሞልቶ ይናገራል። በሙከራዉ የተደረሰበትም ሁሉንም የወባ በሽታ ዓይነቶች መከላከል እንደሚች ነዉ። ተከታታይ የምርምር ተግባሩም ታንዛኒያ፤ ጀርመንና ዩናይትድ ስቴትስ ዉስጥ እንደሚሠራ ይጠበቃል። የምርምር ዉጤቱ የታየዉ ክትባትም ለገበያ በስፋት እስኪቀርብ ገና አራት ዓመታት ሊፈጅበት እንደሚችል አመልክቷል።

Moskitonetz
መድሃኒት የተነከረ አጎበርምስል Edlena Barros

እስካሁንም ለምርምርና ዝግጅቱ አንድ መቶ አስር ሚሊዮን ዩሮ ማዉጣቱን ይገልጻል። «ዋናዉን ፈተና መወጣት ተችሏል» ብሎ የሚያምነዉ የምርምር ተቋም የወባ በሽታን መቋቋም እንዲችሉ የተደረጉ ወገኖችን ከበሽታዉ መታደግ እንደሚቻል ክትባቱ ዉጤት አሳይቷል የሚል እምነት አለዉ። ሳናርያም እንዲሁ ጥረቱን ከሃርቫርድ ዩኒቨርሲቲ ጋ በማቀናጀት በወባ ተህዋስያን መልሶ የወባ በሽታን የመከላከል ሙከራዉን እንደሚያጠናክር ገልጿል።

የወባ በሽታ ዘርፍ ከፍተኛ ተመራማሪዎች የሚታየዉ የሙከራ ዉጤት አበረታች እንደሆነ ይናገራሉ። ሌሎች ደግሞ የወባ ትንኝ ላይ የሚደረገዉ ምርምር ይባስ በማትዘወተርበት አካባቢ እንዳያራባት ብሎም ወደሌላ ችግርነት እንዳይቀይራት ስጋታቸዉን ይገልጻሉ። እሷን ላንዴና ለመጨረሻ ግዜ ከገጸ ምድር ለማጥፋት መድሃኒት ፍለጋና ምርምሩ ቢቀጥልም ዛሬም የወባ ትንኝ አደገኝነቷ አልቀነሰም። ለወባ በሽታ መከላከያ የሚሆን ክትባትም ምናልባት እስከ ጎርጎሪዮሳዊዉ 2030ዓ,ም ድረስ በእርግጠኝነት ተገኝቶ ስራ ላይ የመዋሉ ነገር አነጋጋሪ እንደሆነ ነዉ። በመኝታ ላይ መድሃኒት የተነከረ አጎበር መጠቀም የወባ ትንኟን ንክሻ ለመከላከል እንደሚረዳ ይታመናል፤ የወባ በሽታን ፈጽሞ ለማጥፋት የሚኖረዉ ሚና ግን ከምኞት አይዘልም።

ሸዋዬ ለገሠ

አርያም ተክሌ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ